101736 labor law dispute/ pension/ termination of contract of employment

አንድ ሠራተኛ በህግ የተቀመጠው የጡረታ መዉጫ ዕድሜው ደርሶ በስራው ገበታ ላይ ቢቆይና በኋላ የስራ ውሉ ቢቋረጥ በአሰሪው ላይ የተለየ ግዴታ የሚጥል ስላለመሆኑና የማስጠንቀቂያ ጊዜ አልሰጠህም ተብሎ የማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ ክፈል ተብሎ ሊገደድ የማይችል ስለመሆኑ፣

 

አዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀፅ 24(3)

 

አዋጅ ቁጥር 715/2003 አንቀፅ 17(1)

የሰበር/መ/ቁ 101736

 

መጋቢት 18 ቀን 2007 ዓ/ም

 

 

 

ዳኞች፡-አልማው ወሌ

 

ዓሊ መሐመድ ሡልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመሰል

አመልካች፡- ግዮን ኢንዱስትሪያልና ኮሜርሻል ኃ/የተ/የግል ማህበር ነገረ ፈጅ በዛዬ ሲያምረኝ ተጠሪ፡- አቶ አዲስ አለም ሀ/ኪሮስ ጠበቃ ውቤ አለነ አልቀረቡም

መዝገቡ መርምረን ተከታዩን ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

 

 ፍ ርድ

 

ጉዳዩ ከአሠሪና ሰራተኛ የስራ ውል መቋረጥ ጋር የተያያዘ ሲሆን የተጀመረው በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ተጠሪ ከሳሽ አመልካች ተከሳሽ በመሆን ነው። አመልካች በሥር የፌዴራል የመጀመሪያ እና ከፍተኛ ፍርድ ቤት የተሰጡ ውሳኔዎች መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈጸመባቸው ስለሆነ ይታረምልኝ በማለት ያቀረበውን አቤቱታ አጣርቶ ለመወሰን የቀረበ ነው፡፡

 

የአሁኑ ተጠሪ በሥር ፍርድ ቤት በአመልካች ላይ ያቀረቡት ክስ አጭር ይዘት፡- በአመልካች ድርጅት ከመጋቢት 23/2005 ዓ/ም ጀምሮ በወር 2650 ብር እየተከፈላቸው በአሽከርካሪነት የስራ መደብ ሲሰሩ እንደ ነበር፣ አመልካች ያለ ምንም ጥፋትና ማስጠንቀቂያ የሥራ ውላቸውን ያቋረጡ በመሆኑ ስንበቱ ሕገ ወጥ ነው ተብሎ በሕግ የተፈቀዱ ልዩ ልዩ ክፍያዎች እንዲወስንላቸው ማመልከታቸውን የሚያሳይ ነው፡፡

 

አመልካች በሥር ፍርድ ቤት ያቀረበው መልስ የመጀመሪያ ደረጃ መቃወሚያ ያቀረበ  ሲሆን በፍሬ ነገሩም ተጠሪ በጡረታ የተገለሉ በመሆኑ ስንብቱ ሕጋዊ ነው እንዲባልለት፤ የፕሮቪደንት ፈንድ ተጠቃሚ ስለሆነ የሥራ ስንብት ክፍያ የመጠየቅ መብት እንደሌላቸው የካሳ እና ወደ ሥራ ልመለስ ጥያቄ በይርጋ የታገደ ነው በማለት ተከራክሯል፡፡

 

የሥር ፍርድ ቤትም የግራ ቀኙ ክርክር እና ማስረጃ ከመረመረ በኃላ በተጠሪ የቀረበው ወደ ሥራ ልመለስ ካሳም ይከፈልኝ ጥያቄ በይርጋ የታገደ ስለመሆኑ፤ የፕሮቪደንት ፈንድ ተጠቃሚ በመሆናቸው የሥራ ስንብት ክፍያ እንደ ማይገባቸው፤ የዘገየ ክፍያ ጥያቄ በተመለከተም በአመልካች የታመነው የፕሮፊደንት ፈንድ እና የዓመት እረፍት ወደ ገንዘብ  ተቀይሮ የተከፈላቸው  መሆኑ  በመረጋገጡ  በዚህ  ረገድ  ያቀረቡት  ክርክር  ተቀባይነት እንደሌለው፤


አመልካች ተጠሪን በጡረታ የተገለሉ ናቸው ይበል እንጂ ከግል ድርጅቶች ማህበራዊ ዋስትና ኤጀንሲ በተገኘው መረጃ መሰረት በጡረታ መገለላቸው አናውቅም በማለት መልስ በመስጠቱ እና ያለ ማስጠንቀቂያ ከሥራ በመሰናበታቸው ምክንያት የ3 ወር ደመወዝ ብር 7950 እንዲከፈለቸው ወስኗል፡፡

 

አመልካች እና ተጠሪ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ አቅርበው ፍርድ ቤቱም የግራ ቀኙ ክርክር ከመረመረ በኃላ የስር ፍርድ ቤቱ ውሳኔ በማጽናት ወስኗል፡፡ የአመልካች የሰበር አቤቱታ መነሻም ይህንን ውሳኔ በመቃወም ለማስለወጥ የቀረበ ነው፡፡ ግራ ቀኙ በዚህ ችሎት የጽሑፍ ክርክር ተለዋውጠዋል፡፡ አመልካች በሰበር አቤቱታው የጠቀሰው መሰረታዊ ነጥብ ተጠሪ በጡረታ የተገለሉ በመሆናቸው ሰንብቱ በሕግ አግባብ የተከናወነ መሆኑ እየታወቀ የማስጠንቀቂያ ጊዜ 3 ወር ደመወዝ እንዲከፈል መወሰኑ መሠረታዊ የህግ ስህተት የተፈጸመበት ነው የሚል ሲሆን ተጠሪ በበኩላቸው 60 ዓመት ካለፈባቸው በኃላ በአመልካች ድርጅት ይሰሩ እንደነበር ለስንብቱ ምክንያት ጡረታ ሳይሆን በግብታዊ መንገድ የተወሰደ እርምጃ በመሆኑ የስር ፍ/ቤት ውሳኔ እንዲጸና አመልክቷል፡፡ የአመልካች የመልስ መልስም የሰበር አቤቱታው የሚያጠናክር ነው፡፡

 

የሥር የጉዳዩ አመጣጥ እና የክርክር ይዘት ከላይ የተመለከተው ሲሆን ይህ ችሎትም ለሰበር አቤቱታ መነሻ የሆነው ውሳኔ፤ ግራ ቀኙ በጽሑፍ ያደረጉት ክርክር አግባብነት ከላቸው ድንጋጌዎች እና ጉዳዩ ለሰበር ሲቀርብ ከተያዘው ጭብጥ አንፃር እንደሚከተለው መርምሮታል፡፡

 

እንደመረመረነውም አመልካች አጥብቆ የሚከራከረው የተጠሪ የቅጥር ውል በጡረታ በመገለላቸው ምክንያት በሕጉ አግባብ መቋረጡን መሠረት በማድረግ ሲሆን ተጠሪ በበኩላቸው ዕድሜያቸው 60 ዓመት ከሞላ በኋላም በሥራ መደባቸው ላይ መቀጠላቸውን እና ስንብቱ ግብታዊ መሆኑን ነው፡፡ የሥር የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤትም ለተጠሪ ማስጠንቀቂያ አልተሰጣቸውም ለማለት እንደ መነሻ የወሰደው የግል ድርጅት ማህበራዊ ዋስትና ኤጀንሲ በጡረታ የተገለሉ ስለመሆኑ አናውቅም የሚል መልስ በመስጠቱ ምክንያት ነው ተጠሪ 60 ዓመት የሞላቸው ስለመሆኑ የተካደ ጉዳይ አይደለም፡፡ የስራ ውል በሕግ ከሚቋረጥባቸው መንገዶች እንደ ሠራተኛው አግባብ ባለው ሕግ መሰረት በጡረታ ሲገለል እንደሆነ በአዋጅ ቁጥር 377/ 1996 አንቀጽ  24 (3)  በግልጽ ተደንጓል፡፡  የግል ሠራተኞች  የጡረታ አዋጅ    ቁጥር

715/2003 አንቀጽ 17(1) የሠራተኛው የጡረታ መውጫ ዕድሜ 60 ዓመት መሆኑን ተመልክቷል፡፡ በተያዘው ጉዳይ ተጠሪ 60 ዓመት የሞላቸው ቢሆንም የቅጥር ውሉ እስከ ቀጠለ ድረስ ከሥር ለማሰናበት ማስጠንቀቂያ ሊሰጣቸው እንደሚገባ እየተከራከሩ ነው፡፡

 

በመሰረቱ አንድ ሰራተኛ በሕግ የተቀመጠው የጡረታ መውጫ ዕድሜ ካለፈ በኃላ ሥራ ቢቀጥል ወይም እንደገና ተቀጥሮ ቢሰራ ያለው ሕጋዊ ውጤት ምንድነው? የሚለውን ማየቱ ተገቢ ይሆናል፡፡ አመልካች ለሰንብቱ መነሻ ያደረገው ተጠሪ 60 ዓመት የሞላቸው በመሆኑ በጡረታ ተገለዋል በሚል ነው፡፡ ክፍያ በተመለከተም በአመልካች የታመነው የፕሮፊደንት ፈንድ እና የአመት ዕረፍት በገንዘብ ተቀይሮ የተከፈላቸው ስለመሆኑ ያከራከረ ጉዳይ አይደለም፡፡ አንድ ሠራተኛ የጡረታ መውጫ ዕድሜ ከለፈበት በኋላ በሥራው ቢቀጥል አሰሪው በሕጉ አግባብ ሠራተኛውን ማስናበት እንደሚችል በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጽ 24(3) ተመልክቷል፡፡ አሰሪው ምርታማነቱ እና የገበያ ተዋዋዳሪነቱ ለማስቀጠል የሚችለው በጡረታ የተገለሉ ሠራተኞች በሕጉ አግባብ እያሰናበተ በአዲስ ኃይል እየተካ ሲሄድ መሆኑ የምንገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡ በጡረታ የተገለለ ሰው ስራ መስራት አይችልም የሚባል ባይሆንም አንድ አሰሪ   በጡረታ


የተገለለን ሠራተኛ በድጋሚ ላልተወሰነ ጊዜ ቀጥሮ ያሰራል ለማለት እንደማይቻል የሰበር ሰሚ ችሎት በሰ/መ/ቁ 18832 ህዳር 3 ቀን 2000 ዓ/ም አስገዳጅ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ ይህ አሰገዳጅ ውሳኔ ደግሞ በሁሉም ደረጃ ላይ በሚገኙ ፍርድ ቤቶች ተፈፃሚነት እንዳለው በአዋጅ ቁጥር 454/1997 አንቀጽ 2(1) ስር ተደንግጓል፡፡

 

በተያዘው ጉዳይ ተጠሪ ዕድሜያቸው ከ60 ዓመት በላይ መሆኑ ተረጋግጧል፡፡ አመልካች ድርጅት ከተጠሪ ጋር የነበረው ግንኙነት በሕጉ አግባብ አቋርጠዋል፡፡ ይህ ከሆነ ደግሞ ለተጠሪ ማስጠንቀቂያ መስጠት ይገባው ነበር ለማለት አይቻልም፡፡ ምክንያቱም አመልካች ከተጠሪ ጋር የነበረው የቅጥር ውል ሕጉ በደነገገው የጡረታ መውጫ ዕድሜ መሰረት የተቋረጠ በመሆኑ ነው፡፡ በሕጉ አግባብ የተቋረጠው የቅጥር ውል ደግሞ አሰሪ የማሰጠንቀቂያ ጊዜ አልሰጠህም በሚል ምክንያት የማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ እንዲከፈል አይገደድም፡፡ ተጠሪ 60 ዓመት ከሞላቸው በኃላ በሥራ ገበታቸው መቆየታቸው በአመልካች የተለየ ግዴታ የሚጥል አይደለም፡፡

 

በዚህ መሠረት የስር ፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ የ3 ወር ደመወዝ ብር 7950 እንዲከፈላቸው መወሰኑ እና በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት መጽናቱ መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈጸመበት በመሆኑ ተከታዩን ወስነናል፡፡

 

 ው ሳኔ

 

1. የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በመ/ቁ 31577 በ27/10/2005 ዓ/ም የሰጠው ፍርድ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመ/ቁ. 136076 በ18/09/2006 ዓ/ም የሰጠው ፍርድ ተሸሯል፡፡

2. አመልካች የተጠሪ የቅጥር ውል ያቋረጠው በሕጉ አግበብ ነው ብለናል፡፡ አመልካች ለተጠሪ የማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ የ3 ወር ደመወዝ ብር 7950 ሊከፈል አይገባም በማለት ወስነናል፡፡

3.  ወጪና ኪሳራ የየራሳቸው ይቻሉ ብለናል፡፡

 

 ት ዕ ዛዝ

1.  በዚህ ፍ/ቤት የተሰጠው የዕግድ ትዕዛዝ ተነስቷል፡፡ ይፃፍ፡፡

2.  የሥር ፍርድ ቤት መዝገብ ይመለስ፡፡ መዝገቡ ተዘጋ ወደ መ/ቤት ይመለስ፡፡

 


 

ሩ/ለ


የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡