family law

  • ከዳኝነት ስራ ጋር ያልተያያዙ እና የአስተዳደር ስራ ሲያከናውኑ የሚፈፀሙ የወንጀል ጥፋቶች ዳኛውን ከተጠያቂነት የማያስቀሩ ስለመሆኑ፣

    የወ/ህ/ቁ. 402(1) እና (2)

    በትግራይ ክልል ዳኞች እና ሬጂስትራሮችን ለማስተዳደር ተሻሽሎ የወጣው ደንብ ቁጥር 1/2003

    የሰ/መ/ቁ. 98283

     

    መስከረም 26 ቀን 2007 ዓ.ም

     

    ዳኞች፡-አልማው ወሌ

     

    መኮንን ገ/ህይወት ሙስጠፋ አህመድ ተፈሪ ገብሩ ተኸሊት ይመስል

    አመልካች፡- አቶ ሐጐስ ገ/ሄር መኮንን

     

    ተጠሪ፡- የትግራይ ክልል የስነ/ፀ/ሙ/ኮ - ዐ/ሕግ መዝገቡን መርምረን ተከታዩን ወስነናል፡፡

     ፍ ርድ

     

    የአሁኑ አመልካች በወንጀል ህጉ አንቀጽ 407(2) የተመለከተውን በመተላለፍ የማይገባውን ብልፅግና ለራሱ ወይም ለሌላ ሰው ለማስገኘት በማሰብ በትግራይ ክልል በደቡብ ዞን አሰላ ወረዳ ፍ/ቤት ዳኛ ሆኖ ሲሰራ ሥልጣኑን አላግባብ በመጠቀም የመንግስት የአበል አከፋፈል ሥርዓት በመጣስ ለራሱና ለሥራ ባልደረቦች ሊከፈል የማይገባውን ብር 7653.4 እንዲከፈል በማድረጉ በፈፀመው በሥልጣን ያለአግባብ መጠቀም ወንጀል ተከሷል ሲል የአሁን ተጠሪ  ክስ አቅርቦበታል፡፡

     

    ጉዳዩን በቅድሚያ የተመለከተው የአላማጣ ማዕከላዊ ፍ/ቤት የግራ ቀኙን ክርክር እና ማስረጃ ከሰማ በኋላ አመልካች በተዘዋዋሪ ችሎት ስም ከሥራ ቦታዬ ወደ ቀበሌዎች ሄጃለው በማለት በተሞክሮ ልውውጥ ስም፤ በመሀበራዊ ፍ/ቤትና የመሬት ዳኞች ሥልጠና ስም አበል አላግባብ መውሰዱ ፤ዳኞች ስልጠና ሰጥተዋል በማለት በፔሮል ወደ ቀበሌ እንደወጡ አሰመስሎ አበል መክፈሉ ፤ የሂሳብ መደብ በማይፈቅድበት ሁኔታ በራሱ ስም አበል ወጪ በማድረግ የፅሕፈት መሣሪያ መግዛት እና ከፋይናንስ ደንብ እና መመሪያ ውጭ ስለመስራቱ በራሱ በዝርዝር የተመለከተውን እና የቀረበበትን የሰውም ሆነ የሰነድ ማስረጃ ማስተባበል ባለመቻሉ እንደ ክሱ አቀራረብ ጥፋተኛ ነው በማለት የቅጣት ማቅለያ ምክንያቶችን ተቀብሎ በ1(አንድ) ዓመት ፅኑ እስራት እና በብር 2000 /ሁለት ሺህ /መቀጮ እንዲቀጣ ወስኗል፡፡

     

    ጉዳዩ በይግባኝ የቀረበለት የክልሉ ጠቅላይ ፍ/ቤትም ሆነ የሰበር አቤቱታ የቀረበለት የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ውሳኔው የሚነቀፍበት ምክንያት የለም በማለት ቅሬታውን ውድቅ አድርገዋል፡፡


    የሰበር አቤቱታው ለዚህ ፍ/ቤት የቀረበው ይህን ውሳኔ በመቃወም ነው፡፡ አመልካቹ የካቲት 24 ቀን 2ዐዐ6 ዓ.ም በተፃፈ 5 (አምስት) ገጽ ዝርዝር ቅሬታ ያቀረቡ ሲሆን ተጠቃሎ ሲታይ የፍርድ ቤቱ ሥራ እንዳይጐዳ ብሎ የፈፀምኩት መሆኑ እየታወቀ፤በአግባቡም ሣይጣራ ተድበስብሶ የታለፈ በመሆኑ፤የቀረቡት ማስረጃዎች ከሚመለከታቸው ህጐች ሳይገናዘብ የተሰጠ ውሳኔ በመሆኑና ፤ የፌዴራሉ ጠቅላይ ፍ/ቤት በሰበር መዝገብ ቁጥር 33075 ባሳለፈው ውሳኔ የዳኝነት ሥራ በሚያከውኑበት ጊዜ የሚፈፅሙ ጥፋቶች እና ስህተቶች ዳኞች በስልጣን ያለ አግባብ መጠቀም በሚል ወንጀል ሊከሠሱ አይገባም በማለት የሰጠው ውሳኔ ተሻሽሎ ተተርጉሞ የሥር ፍ/ቤቶች ውሣኔ ተሽሮ በነፃ ልሰናበት ብለዋል፡፡

     

    ቅሬታቸው ተመርምሮ ፈፀሙት የተባለው ድርጊት ጥፋተኛ በተባሉበት የህግ አንቀጽ ሥር የሚወድቅ መሆኑን ወይም ጉዳዩ ከዳኝነት ሥነ ምግባርና ዲሲፕሊን አኳያ የሚታይ መሆኑን ለማጣራት ተብሎ ተጠሪ መልስ እንዲሠጡበት ተደርጓል፡፡

     

    ተጠሪ ሚያዚያ 9/2ዐዐ6 ዓ.ም በተፃፈ መልስ በወ/ህ/ቁ.407(2) መከሰሱ እና ጥፋተኛ መባሉ የህግ ስህተት የሌለበት በመሆኑ፤አስቀድሞ በሰ/መ/ቁ. 33075 የተሰጠው ውሳኔም የዳኝነት ሥራ በመከናወን ላይ እያለ የሚፈፀሙ ጥፋትና ሥህተትን እንጅ መሠል ተግባርን የሚመለከት ባለመሆኑ የሥር ፍ/ቤቶች ያሳለፉት ውሳኔ መሠረታዊ የህግ ስህተት አልተፈፀመበትም ተብሎ እንዲፀና ጠይቀዋል፡፡ አመልካቹም ግንቦት 2/2006 ዓ.ም የተፃፈ ክርክራቸውን የሚያጠናክር የመ/መልስ አቅርበዋል፡፡

     

    ከላይ ባጭሩ ለመግለፅ የሞከርነው የጉዳዩን አመጣጥ ሲሆን የሰበር አቤቱታው ያስቀርባል የተባለበትን ጭብጥ ይዘን መዝገቡን መርምረናል፡፡

     

    እንደመረመርነው ፍሬ ነገሩን የማጣራት እና ማስረጃ ለመመዘን ሥልጣኑ የተሰጠው የሥር ፍ/ቤት አመልካቹ መንግስት የፋይናንስ ህጐች እና ደንቦች ከተፈቀደው ውጭ በአጠቃላይ ብር 7,650.40 እንዲወጣ በማድረግ ለራሱም ሆነ ለሥራ ባልደረቦቹ መጠቀሚያ በማድረግ በኃላፊነቱ አላግባብ መገልገሉን አረጋግጧል፡፡

     

    ይኸው በማስረጃ ተረጋግጧል የተባለው አድራጐት በመንግስት ሥራ ላይ የተፈፀመ ከዳኝነት ሥራ ጋር ተቀላቅሎ ሊታይ የማይገባ የወንጀል ጥፋት ነው፡፡

     

    አመልካቹ በዳኝነት ተሹመው በቋሚት የዳኝነት የመንግሰት ሥራን የሚሰሩ የመንግስት ሠራተኛ በመሆናቸው እና ይሠሩበት የነበረው የወረዳ ፍ/ቤትም በመንግስት በጀት ተመድቦለት የዳኝነት መንግስታዊ ሥራ የሚከናወንበት መስሪያ ቤት በመሆኑ በመንግስት ሥራ ላይ የሚፈፀሙ ወንጀሎችን የሚመለከቱ የወንጀል ህጉ ድንጋጌዎች በመሠል ጥፋቶች ላይም በተመሳሳይ ተፈፃሚነት የሚሆኑ ናቸው፡፡ /የወ/ህ/ቁ. 402(1) እና (2) ይመለከታል፡፡

     

    ሌላው መከራከሪያ እና የሰበር አቤቱታው ያስቀርባል ለመባሉ ምክንያት የሆነው ጉዳዩን ከዳኝነት ሥነ ምግባር እና ዲሲፕሊን አኳያ የሚታይ መሆኑን የተመለከተ ነው ፡፡

     

    በትግራይ ክልል ዳኞች እና ሬጅስትራሮችን ለማስተዳደር ተሻሽሎ የወጣው ደንብ ቁጥር 1/2003 በመንግስት  ገንዘብ  ወይም  ንብረት  በዳኞች  የሚፈፀምን  ያላግባብ  መጠቀም  እና መውሰድ


    የዲስፒሊን ጥፋት አድርጐ ይዟል፡፡ ነገር ግን የዲስፒሊን ደንቡ መሠል ድንጋጌ መያዙ በወንጀል ገረድ የሚኖረን ኃላፊነት የሚያስቀር አይደለም፡፡

     

    የዲስፕሊን ጉዳዩች የሚቋቋሙበት፣ የሚመሩበት ሥርዓት እና ከሚሠጠው ውሳኔ የወንጀል ጥፋቶች ከሚቋቋሙበት፣ከሚመሩበት ሥርዓት እና ከሚሰጠው ውሣኔ ተለይቶ ሊታይ ይገባል፡፡ ስለሆነም የተፈፀመው ጥፋት የወንጀል ተጠያቂነት የሚያስከትል መሆን አለመሆኑ ከዲስፒሊን ጉዳዩ ጋር ሊያታይ አይገባም፡፡

     

    የፌዴራሉ ጠቅላይ ፍ/ቤት ሰበር ችሎት በሰበር መዝገብ ቁጥር 33075 ዳኛ ብርቁ ባላዬ እና የአማራ ክልል ስነ ምግባር እና ፀረ ሙስና ኮሚሽን በተከራከሩበት ጉዳይ ጥር 13/2001 ዓ.ም ባሳለፈው ውሳኔ የዳኝነት ሥራን በሚያከናውኑበት ወቅት የሚፈፅሙ ስህተቶች እና ጥፋቶች ሁሉ ዳኛን በሥልጣን አላግባብ መገልገል ወንጀል ሊያስጠይቁ  የማይችሉ ስለመሆናቸው መወሠኑ የዳኞችን ህገ መንግስታዊ የውሳኔ ነፃነት ለማጠናከር እንጅ በእጃችን እንዳለው ጉዳይ ከዳኝነት ሥራ ጋር ያልተያያዙ እና የአስተዳደር ስራ ሲያከናውኑ የሚፈፀሙ የወንጀል ጥፋቶች ሁሉ ተጠያቂነትን የሚያስቀር ትርጉም የሚሠጠው ባለመሆኑ አመልካቾች ይኸው ውሳኔ በማመሳሰል ለተያዘው ጉዳይ ተፈፃሚ እንዲሆን ያቀረቡት ጥያቄ በህጉ ተቀባይነት የለውም ብለናል፡፡

     

    በአጠቃላይ አመልካቾች በነበራቸው የሥራ ኃላፊነት ምክንያት ሊጠብቅ እና ሊከላከሉት የሚገባን የህዝብ እና የመንግስት ንብረት ከህግ ውጭ ሥልጣናቸውን አላግባብ በመጠቀም ለፈፀሙት ጥፋት በስር ፍ/ቤቶች የተላለፈባቸው ውሣኔ የህግ ሥህተት የተፈፀመበት አይደለም ብለናል ተከታዩንም ወስነናል፡፡

     

     ው ሳኔ

    የትግራይ ክልል ጠቅላይ ፍ/ቤት ሰበር ችሎት በሰጠው መ/ቁ. 6111/06 ታህሳስ 3 ቀን 2006 ዓ.ም ያሳለፈው ትዕዛዝ ፤የጠቅላይ ፍ/ቤቱ ይግባኝ ሰሚ ችሎት በመ/ቁ.58434 ግንቦት 13 ቀን 2005 ዓ.ም ያሳለፈው ትዕዛዝ እና በደቡባዊ ዞን ማዕከላዊ ፍ/ቤት የአላማጣ ምድብ ችሎት በወ/መ/ቁ.02867/05 የካቲት 26/2005 ዓ.ም የሰጠው ፍርድ በወ/መ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ.195(2)(ለ)(2) መሠረት ፀንቷል፡፡

    መዝገቡ ተዘግቷል ወደ መ/ቤት ይመለስ፡፡

     


     

    ብ/ግ


    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

  • የባህር ላይ የእቃ ማጓጓዝ ውልን በተመለከተ የዕቃው ርክክብ ከተፈፀመበት ወይም የማስረከቡ ጉዳይ ሳይፈፀም ቀርቶ እንደሆነ እቃውን ማስረከብ ከሚገባበት ቀን አንስቶ በአንድ አመት ውስጥ ክስካልቀረበ በይርጋ የሚታገድ ስለመሆኑ፡-

     

    የባህር ህግ ቁጥር 203፤180፤162

    የሰ/መ/ቁ. 98358

     

    ጥር 05 ቀን 2007 ዓ.ም

     

    ዳኞች፡-አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሱልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመሰል

    አመልካች፡- አንበሳ ኢንሹራንስ ኩባንያ -ነገረ ፈጅ ኃይሉ ተሰማ ቀረቡ

     

    ተጠሪ፡- የኢትዩጵያ የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ድርጅት ጠበቃ ማረን ወንዴ

    - ቀረቡ

     

    መዝገቡ ተመርምሮ ተከታዩ ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     

                 

     

    ጉዳዩ የመድን ውልን መሠረት አድርጎ የቀረበውን የገንዘብ ይተካልኝ ጥያቄ የሚመለከት ሲሆን ክርክሩ የተጀመረው የአሁኑ አመልካች በአሁኑ ተጠሪ ላይ በፌዴራሉ መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በመሰረተው ክስ መነሻ ነው፡፡የክሱ ይዘትም ባጭሩ፡- የአሁኑ አመልካች ለደንበኛው ለነፃ ኃላፊነቱ የተ.የግል ማህበር ከቱርክ ሀገር ለሚያስመጣቸው 246 ጥቅል ብረቶች ከተጫኑበት ሀገር ተጓጉዞ እስኪመጣ ድረስ ለሚያጋጥም ጉዳት በፖሊሲ ውል ቁጥር 01/ኤም አር ኦኤ/00001/07 የባህር ላይ የጉዞ መድን ሽፋን መስጠቱን፣ተጠሪ የመድን ሽፋን የተሰጣቸውን 246 ጥቅል ብረቶችን ተረክቦ ሆውማ ቤሊ ቪ.ኢኤስቲአር53  በሚባለው  መርከብ ከሊአጋ ኢዝሚር ቱርክ አጓጉዞ ጅቡቲ ለማድረስ በባህር እቃ መጫኛ ሰነድ ቁጥር 305/ኤስሲ ግዴታ መግባቱን፣ተጠሪ ጅቡቲ ለማድረስ ግዴታ ከገባባቸው 246 ጥቅል ብረቶች ውስጥ እቃው ጅቡቲ ወደብ ደርሶ ሲራገፍ 11(አስራ አንድ) ጥቅል ብረቶች መጥፋታቸውን፣ ከተጓጓዘው 246 ጥቅል ብረቶች ውስጥ የአመልካች ደንበኛ በ11/04/2004 ዓ/ም 226 ጥቅል አዲስ አበባ ላይ በእቃ መረከቢያ ሰነድ ቁጥር 10431 መረከቡን፣ቀሪው 20 ጥቅል ብረት ውስጥ 9 ጥቅል ደግሞ ዘግይቶ በ05/06/2004 ዓ/ም በእቃ መረከቢያ ሰነድ ቁጥር 10999 መረከቡን፣ይህ የተጫነ እቃ መጥፋትና መጉደሉ በጅቡቲ የሰርቬየር ስራ በሚሰራው ገልፍ ኤጄንሲ አገልግሎት የሚባል ሰኔ 24 ቀን 2004 ዓ/ም ማረጋገጡን ገልጾ አመልካች ለደንበኛው የከፈለውን ካሳ ብር 289,527.23 ተጠሪ እንዲተካለት ይወሰን ዘንድ ዳኝነት መጠየቁን የሚያሳይ ነው፡፡የአሁኑ ተጠሪ ለክሱ በሰጠው መልስም፡-የመጀመሪያ ደረጃ መቃወሚያዎችን ያስቀደመ ሲሆን በዚህም መሰረት የአመልካች ክስ እቃው በጅቡቲ ወደብ ላይ መራገፉ ከተረጋገጠበት ከጳጉሜ 03 ቀን 2003 ዓ/ም ጀምሮ በሚታሰብ በአንድ አመት ይርጋ ጊዜ ውስጥ የሚታገድ መሆኑን የባህር ሕግ ቁጥር 203(1) ድንጋጌ እንደሚያሳይ እንዲሁም አመልካች ክስ ለማቅረብ መብት ወይም ጥቅም የሌለው መሆኑን ገልፆ ክሱ ውድቅ ሊሆን ይገባል ሲል ተከራክሯል፡፡


    የስር ፍርድ ቤትም በዚህ መልክ የቀረበውን የይርጋ ክርክር በጭብጥነት ይዞ ጉዳዩን በመመርመር እቃው በጅቡቲ ወደብ የተራገፈው ጳጉሜ 03 ቀን 2003 ዓ/ም መሆኑን መነሻ አድርጎ ይርጋውን በመቁጠር የካቲት 05 ቀን 2005 ዓ/ም የቀረበው የአመልካች ክስ በባህር ሕግ ቁጥር 203(1) መሰረት በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ያልቀረበ በመሆኑ በይርጋ የታገደ ነው በማለት መዝገቡን ዘግቶታል፡፡በዚህ ብይን የአሁኑ አመልካች ቅር በመሰኘት ይግባኙን ለፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቢያቀርብም ተቀባይነት አላገኘም፡፡የአሁኑ የሠበር አቤቱታ የቀረበውም ይህንኑ ብይን በመቃወም ለማስቀየር ነው፡፡የአመልካች የሰበር አቤቱታ መሰረታዊ ይዘትም፡- የመጨረሻ ርክክብ የተደረገው የካቲት 05 ቀን 2004 ዓ/ም ሁኖ እያለና የደንበኛው እቃ መጉደሉም የተገለጸው ሰኔ 24 ቀን 2004 ዓ/ም ሁኖ እያለ የእቃው ርክክብ ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ይርጋው ሊቆጠር ይገባል ተብሎ የአመልካች ክስ ውድቅ መደረጉ ያላግባብ ነው የሚል ሲሆን አቤቱታው ተመርምሮም በዚህ ችሎት ሊታይ ይገባዋል ተብሎ ተጠሪ ቀርቦ ግራ ቀኙ በፅሁፍ እንዲከራከሩ ተደርጓል፡፡

     

    የጉዳዩ አመጣጥ አጠር ባለመልኩ ከላይ የተገለፀው ሲሆን ይህ ችሎትም የግራ ቀኙን ክርክር ለሰበር አቤቱታው መነሻ ከሆነው ውሳኔ እና አግባብነት ካላቸው ድንጋጌዎች ጋር በማገናዘብ በሚከተለው መልኩ መርምሮታል፡፡እንደመረመረውም የዚህን ችሎት ምላሽ የሚያስፈልገው ነጥብ የአመልካች ክስ በይርጋ የታገደ ነው ተብሎ ውድቅ መደረጉ ባግባቡ ነው? ወይስ አይደለም? የሚለው ነው፡፡

     

    አመልካች በተጠሪ ላይ ክስ ሊመስርት የቻለው ለደንበኛው ለነፃ ኃላፊነቱ የተ.የግል ማህበር ከቱርክ ሀገር ለሚያስመጣቸው 246 ጥቅል ብረቶች ከተጫኑበት ሀገር ተጓጉዞ እስኪመጣ ድረስ ለሚያጋጥም ጉዳት በፖሊሲ ውል ቁጥር 01/ኤም አር ኦኤ/00001/07 የባህር ላይ የጉዞ መድን ሽፋን መስጠቱን መሰረት አድርጎ ሲሆን በዚህ ጉዞ ሂደት ጠፉ ለተባሉት 11 ጥቅል ብረቶች ለደንበኛው ከፈልኩ የሚለውን ገንዘብ እቃዎቹን የማጓጓዝ ግዴታ አለበት የሚለው ተጠሪ እንዲተካለት ነው፡፡ስለሆነም ለጉዳዩ ቀጥተኛ አግባብነት ያለው ሕግ የባህር ህግ ሲሆን ለተያዘው ጉዳይ ተፈፃሚነት ያለውን የይርጋ ጊዜ የሚያስቀምጠው የህጉ ድንጋጌ ቁጥር 203 ሲሆን ድንጋጌው ሁለት ንዑስ ቁጥሮችን የያዘ ሁኖ የመጀመሪያው ንዑስ ቁጥር ከማመላለሻው ውል ውስጥ የተገኙ መብቶች በይርጋ የሚታገዱት የንግድ እቃውን ከተረከበበት ቀን ጀምሮ ወይም የማስረከቡ ጉዳይ ሳይፈፀም ቀርቶ እንደሆነ እቃውን ማስረከብ ከሚገባበት ቀን አንስቶ የአንድ አመት ጊዜ ካለፈ በኋላ ነው በማለት አስገዳጅነት ባለው ሁኔታ አስቀምጧል፡፡የተጠቃሹ ቁጥር ንዑስ ቁጥር ሁለት ድንጋጌ ደግሞ ከሂሳብ አከፋፋል ጋር ተያይዞ የሚነሳው ክርክር የሚታገድበትን አግባብ የሚያስቀምጥ ነው፡፡ የባህር ህግ ቁጥር 203 ድንጋጌ የሚገኘው በጭነት ማስታወቂያ የተረጋገጠ ደረሰኝ የማመላለሻ ውልን የሚመለከቱ ልዩ ድንጋጌዎች በሚገዛው ክፍል ሲሆን የድንጋጌዎችን ወሰን በተመለከተ በቁጥር 180 ስር ሕግ አውጪ  አስቀምጧል፡፡ይህ ድንጋጌ በንዑስ ቁጥር አንድ ስር በክፍሉ ላይ የተመለከቱት ድንጋጌዎች የሚፀኑት በተለይ በመርከብ ላይ በተጫኑት የንግድ እቃዎች የጭነት ማስታወቂያ ደረሰኝ ወይም ይህን በመሰለ ሌላ አይነት ሰነድ በተረጋገጡ የጭነት ማመላለሻ ውሎች ላይ ብቻ መሆኑን ሲያስቀምጥ የድንጋጌው ንዑስ ቁጥር ሁለት እና ሶስት ደንጋጌዎች ደግሞ እንደቅደም ተከተላቸው የመርከብ መከራየት ውል ሰነድ ባለው ጉዳይ ላይ ተፈፃሚ ሊሆኑ እንደማይችሉና በዚህ ጊዜም ድንጋጌዎቹ ተፈፃሚ ሊሆኑ የሚችሉበትን ልዩ ሁኔታዎችን የሚያስቀምጡ ናቸው፡፡


    ወደ ተያዘው ጉዳይ ስንመለስም ተጠሪ ጅቡቲ ለማድረስ ግዴታ ከገባባቸው 246 ጥቅል ብረቶች ውስጥ እቃው ጅቡቲ ወደብ ደርሶ የተራገፈው ጳጉሜ 03 ቀን 2003 ዓ/ም ሁኖ በዚህ ጊዜ ከተጓጓዘው 246 ጥቅል ብረቶች ውስጥ የአመልካች ደንበኛ በ11/04/2004 ዓ/ም 226 ጥቅል አዲስ አበባ ላይ በእቃ መረከቢያ ሰነድ ቁጥር 10431 መረከቡን፣ቀሪው 20 ጥቅል ብረት  ውስጥ 9 ጥቅል ደግሞ ዘግይቶ በ05/06/2004 ዓ/ም በእቃ መረከቢያ ሰነድ ቁጥር 10999 መረከቡን

    ፣ይህ የተጫነ እቃ መጥፋትና መጉደሉ በጅቢቲ የሰርቬየር ስራ በሚሰራው ገልፍ ኤጄንሲ አገልግሎት የሚባል ሰኔ 24 ቀን 2004 ዓ/ም ማረጋገጡንና አመልካች ክስ የመሰረተው የካቲት 05 ቀን 2005 መሆኑን የክርክሩ ሂደት ያሳያል፡፡አሁን ግራ ቀኙን እያከራከረ ያለው ጉዳይ በባህር ህጉ ቁጥር 203(1) የተመለከተው የአንድ አመት የይርጋው ጊዜ መቆጠር የሚጀምረው ከመቼ ጀምሮ ነው? የሚለው ነው፡፡አመልካች የበታች ፍርድ ቤቶች የይርጋ ጊዜ አቆጣጠር ስህተት ነው በማለት የሚከራከረው የእቃዎቹ ርክክብ ጊዜ በማስጫኛ ውሉ ላይ አልተገለፀም፣በመጀመሪያው ዙር 226፣ቀጥሎ ደግሞ 9 ጥቅል ብረቶች የተላኩ መሆኑንና ለክሱ መነሻ የሆኑት ቀሪዎቹ 11 ጥቅል ብረቶች መጥፋታቸው የተረጋገጠው ሰኔ 24 ቀን 2004 ዓ/ም ነው በሚል ነው፡፡እንግዲህ ከክርክሩ ይዘት በግልጽ መረዳት የሚቻለው እቃው በባህር ላይ ተጉዞ ጅቡቲ የተራገፈበት አግባብ በአንድ የማስጫኛ ሰነድ ያለመሆኑን ነው ፡፡በአንድ የማስጫኛ ሰነድ እቃዎቹን ተጠሪ ባልተረከበበት ሁኔታ የመጀመሪያው የማራገፊያ ቀን ማለትም ጳጉሜ 03 ቀን 2003 ዓ/ም ከይርጋው መቆጠር መነሻ ቀን የሚሆንበት አግባብ የለም፡፡እንዲሁም ይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት የመጀመሪያ የርክክብ ቀን የሆነው ታህሳስ 11 ቀን 2004 ዓ/ም ለይርጋው መነሻ ተደርጎ ሊወሰድ ይገባል ማለቱ እቃው በሙሉ አንድ አይነት፣በአንድ የጭነት ሰነድ በአንድ የማጓጓዣ ውል የተጓጓዘ መሆኑን ከክሱ መረዳት ይቻላል በሚል ነው፡፡ይሁን እንጂ ከዚሁ ከመጀመሪያው ርክክብ በኋላ 9 ጥቅል ብረትን የአመልካች ደንበኛ የካቲት 05 ቀን 2004 ዓ/ም መረከቡ ያልተካደ ፍሬ ነገር ነው፡፡ስለሆነም ርክክቡ የቆመው ከዚህ ከየካቲት 05 ቀን 2004 ዓ/ም በኋላ በመሆኑ የአመልካች ደንበኛ እቃዎቹ መጥፋታቸውን እርግጠኛ ሊሆኑ ይችላሉ ተብሎ የሚታሰበው ከዚህ ቀን በኋላ እንጂ የመጀመሪያው ርክክብ ከተደረገበት ጊዜ ጀምሮ አይደለም፡፡ተጠሪ የባህር ህግ ቁጥር 180(2) ድንጋጌን መሰረት አድርጎ የሚያቀርበው ክርክርም እቃዎቹ ከመርከቡ ላይ ከተጫኑበት አንስቶ አስከሚራገፉበት ጊዜ ብቻ የበህር ህግ ቁጥር 203 ድንጋጌ ተፈፃሚ መሆኑን የሚያስቀምጥ ሲሆን ይህም እቃዎቹ ሙሉ በሙሉ ተጭነው ባልተቆራረጠ ሁኔታ ርክክቡ የሚፈፀምበትን አግባብ ግንዛቤ ውስጥ በማስገባት የተቀመጠ ድንጋጌ ነው ከሚባል በስተቀር በመርከብ ላይ የተጫኑት እቃዎች በተግባር በተለያዩ ጊዜያት እየተራገፉ ርክክቡም በተለያዩ ጊዜያት ሲደረግ የነበረበትን ሁኔታ ለመግዛት ታስቦ የተቀመጠ ነው ለማለት የሚቻል አይደለም፡፡የአመልካች ደንበኛ እቃዎቹን በተለያዩ ጊዜያት ሲረከቡ የነበሩ መሆኑ በፍሬ ነገር ደረጃ ከተረጋገጠ እቃዎቹ የተራገፉበትን ቀን ወይም የመጀመሪያ ርክክብ የተደረገበትን ቀን መነሻ አድርጎ ክሳቸው በይርጋ እንዲታገድ ማድረግ ከይርጋ ፅንሰ ሃሳብም ውጪ መሆኑ የሚታመን ነው፡፡

     

    የይርጋ ህግ መሰረታዊ አላማ ተገቢውን ጥረት የሚያደርጉ ገንዘብ ጠያቂዎችን ወይም መብት አስከባሪዎችን መቅጣት ሳይሆን መብታቸውን በተገቢው ጊዜ ለመጠየቅ ጥረት የማያደርጉትን ሰዎች መቅጣት መሆኑ ይታመናል፡፡ስለሆነም የአመልካች ደንበኛ መብታቸውን ማስከበር ሲችሉ ያላግባብ የዘገዬበት ሁኔታ መኖሩን የክርክሩ ሂደት አያሳይም፡፡በባህር ህግ ቁጥር 162  ድንጋጌ ስር የይርጋ አቆጣጠር ጊዜ የሚጀምርበትን አግባብ ያስቀመጠ ሲሆን ለተያዘው ጉዳይ ግን ድንጋጌው ሙሉ በሙሉ አግባብነት አለው ለማለት የሚቻል ሁኖ አልተገኘም፡፡ምክንያቱም


    ድንጋጌው በንኡስ ቁጥር አንድ ስር ለመጫን ወይም ለማራገፍ የተወሰነው ጊዜ መቆጠር የሚጀምረው ካፒቴኑ መርከቡን ሊጫን ወይም ሊራገፍ ተዘጋጅቷል ብሎ ካስታወቀበት  ጊዜ ጀምሮ መሆኑን ሲያስቀምጥ የድንጋጌው ንዑስ ቁጥር ሁለት ደግሞ ጊዜም የሚታሰበው ካፒቴኑ ማስታወቂያውን ሰጥቶ ስራው ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ መሆኑን ያሳያል፡፡በሌላ አገላለፅ ይህ ድንጋጌ ተፈጻሚ የሚሆነው የመጫኛና የማራገፊያ ጊዜ የሚጀምርበት ጊዜ በግልጽ በታወቀበት ሁኔታ ነው እንጂ እቃዎቹ በተለያዩ ጊዜያት በተጫኑበትና በተራገፉበት ግንኙነት ውስጥ አይደለም፡፡የአመልካች ደንበኛ እቃዎች ሙሉ በሙሉ የተጫኑበት ቀንም ሆነ የሚራገፉበት ቀን ያለመታወቁን የክርክሩ ሂደት ያሳያል፡፡

     

    አመልካች በእርግጥም መብቱን ማስከበር የሚችልበት ጊዜ የካቲት 05 ቀን 2004 ዓ/ም ከተባለ ይኼው ጊዜ በፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1848(1) ድንጋጌ መሰረት ግንዛቤ ውስጥ ገብቶ በባህር ህጉ አንቀጽ 203(1) የተቀመጠው የአንድ አመት ጊዜ የሚያበቃው ከየካቲት 06 ቀን 2005 ዓ/ም ጀምሮ ሲሆን አመልካች ግን ይሄው ጊዜ ከማለፉ በፊት የካቲት 05 ቀን 2005 ዓ/ም ክሱን ያቀረበ በመሆኑ ክሱ በይርጋ የሚታገድ ሁኖ አልተገኘም፡፡ሲጠቃለልም የበታች ፍርድ ቤቶች የአመልካች ክስ በአንድ አመት ይርጋ የሚታገድ ነው በማለት የሰጡት ብይን ተገቢውን የይርጋ መቁጠሪያ ጊዜ መነሻ ያላደረገ ከመሆኑም በላይ የባህር ህግ ቁጥር 162 ድንጋጌን ይዘቱንና መንፈሱን ከተያዘው ጉዳይ ልዩ ባህርይ ጋር ባላገናዘበ መልኩ በመሆኑ ብይኑ መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት ያለበት ሁኖ ተገኝቷል፡፡ በዚህም መሰረት ተከታዩን ወስነናል፡፡

     

     ው ሳኔ

     

    1. በፌዴራሉ መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በመ/ቁጥር 203024 ግንቦት 06 ቀን 2005 ዓ/ም ተሰጥቶ በፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በመ/ቁጥር 137802 ታህሳስ 08 ቀን 2006 ዓ/ም በትእዛዝ የፀናው ብይን በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1)መሰረት ተሸሯል፡፡

    2.  የአመልካች ክስ በይርጋ የታገደ አይደለም ብለናል፡፡

    3. የፌዴራሉ መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ክርክሩን በመ/ቁጥር 203024 ቀጥሎ በሌሎች የግራ ቀኙ የክርክር ነጥቦች ተገቢውን የክርክር አመራር ስርዓት ተከትሎ ተገቢውን ዳኝነት እንዲሰጥበት ጉዳዩን በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 341(1) መሰረት መልሰን ልከንለታል፡፡ይፃፍ፡፡

    4.  በዚህ ችሎት ለተደረገው ክርክር የወጣውን ወጪና ኪሳራ የየራሳቸውን ይቻሉ ብለናል፡፡

    መዝገቡ ተዘግቷል፤ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ ብለናል፡፡

     


     

    ት/ጌ


    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

  • የዲፕሎማቲክ ግንኙነቶችን ስምምነት ልምድን ለማክበር ሲባል የውጭ ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖችና ኢትዮጲያዊያን ሠራተኞቻቸው የሚያደርጉት የቅጥር ግንኙነት ላይ የአሠሪና ሠራተኛ ሕግ ተፈፃሚ የማይሆን ስለመሆኑ፡-

     

    የተባበሩት መንግስታት አካል የሆነ ድርጅት የተባበሩት መንግስታት ጥቅምና የተለየ ከለላን በተመለከተ በተደነገገ ሥምምነት በማንኛውም የመንግስት ፍ/ቤቶች ተከሶ መቅረብ የሌለበት ሥለመሆኑ፡-

     

    አፈፃፀም በፍርድ ቤት የተሰጠ ውሳኔ ትርጉም እንዲኖረው በማድረግ ውጤት ያለውና በተገቢው መንገድ መፈፀም ያለበት መሆኑ የሚታወቅ ቢሆንም ለማንኛውም ጉዳዮች ይሰራል ተብሎ ድምዳሜ ላይ መድረስ የማይቻል ስለመሆኑ፡-

     

    አዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀፅ 3/3(ሀ) የተባበሩት መንግስታት ቻርተር አንቀፅ 105

    ከተባበሩት መንግስት ጥቅምና የተለየ ከለላን በተመለከተ የተደነገገው ሥምምነት አንቀፅ 2/2/ እና 3

     

    የፍ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 212

    የሰ/መ/ቁ/ 98541

     

    ህዳር 10 ቀን 2007 ዓ.ም

     

    ዳኞች፡-አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሡልጣን አባተማም መስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመሰል

    አመልካች፡- አቶ አለማየሁ ኦላና - ቀረቡ

     

    ተጠሪ፡-የተባበሩት መንግስታት የልማት ድርጅት (UNDP) ታልፏል ፡፡

     

    መዝገቡ ተመርምሮ ተከታዩ ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     

     ፍ ርድ

     

    ይህ የሰበር ጉዳይ የቀረበው አመልካች በተጠሪ ላይ የአሠሪና ሰራተኛ ጉዳይ አዋጅ ቁጥር 377/1996 ድንጋጌዎችን መሰረት አድርገው ያቀረቡት ክስ ተጠሪ በሌለበት ታይቶ በክርክሩ ከተረጋገጠበት የፍሬ ነገር ጉዳዮች በመነሳት የአሁኑ አመልካች የተለያዩ ክፍያዎች በተጠሪ እንዲከፍሏቸው በወረዳው ፍርድ ቤት በተወሰነው መሰረት የአፈጻጸም መዝገብ ከፍተው ክርክሩ በመታየት ላይ እያለ ተጠሪ የመከሰስ መብት የለውም ተብሎ የአፈጻጸም መዝገቡ በሁሉም የበታች ፍርድ ቤቶች መዘጋቱ ተገቢ መሆን ያለመሆኑን ለመመርመር ተብሎ ነው፡፡

     

    የአሁን አመልካች ተጠሪ ከህግ ውጪ ከስራ አሰናብቶኛል በማለት ካሳና የተለያዩ ክፍያዎች እንዲከፍሏቸው ይወሰን ዘንድ በያበሎ ወረዳ ፍርድ ቤት በአሁኑ ተጠሪ ላይ ክስ መስርተው የአሁኑ ተጠሪ በሌለበት ጉዳዩ እንዲታይ ተደርጎ ፍርድ ቤቱ ጉዳዩን መርምሮ ስንብቱ ሕገ ወጥ መሆኑን በመደምደም ለአመልካች ካሳና የተለያዩ ክፍያዎች እንዲከፈሉ በማለት ወስኗል፡፡አመልካች ይህንኑ ውሳኔ ለማስፈፀም በወረዳው ፍርድ ቤት የአፈጻጸም ክስ ከፍተው ጉዳዩ መታየት ከጀመረ በኋላ የወረዳው ፍርድ ቤት ጉዳዩን መርምሮ የተባበሩት መንግስታት ኮንቬንሽንን አንቀፅ 2(3) በዋቢነት ጠቅሶ ፍርድ ቤቱ ጉዳዩን ለማየት ስልጣን የለውም በማለት የአፈጻጸም መዝገቡን ዘግቶታል። በዚህ ትዕዛዝ አመልካች ቅር በመሰኘት ይግባኛቸውን  ለቦረና ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቢያቀርቡም ተቀባይነት አላገኙም፡፡አመልካች ለክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት አቤቱታቸውን አቅርበውም ችሎቱ ጉዳዩን መርምሮ ተጠሪን ያስቀርባል የሚል ትዕዛዝ ሰጥቶ


    ተጠሪ ሊቀርብ ባለመቻሉ መልስ መስጠቱ የታለፈ ሲሆን ችሎቱ ጉዳዩን መርምሮ ጉዳዩ የአሰሪና ሰራተኛ ጉዳይ ሁኖ አመልካች የሚከራከሩት የተባበሩት መንግስታት አካል ከሆነው ድርጅት ጋር መሆኑን፣ ከእንደዚህ አይነት ድርጅቶች ጋር የሚደረግ ግንኙነት በአዋጅ ቁጥር 377/1996 የማይገዛ መሆኑ በተጠቃሹ አዋጅ አንቀጽ 3(ሀ) ስር መመልከቱን፣ተጠሪና መሠል አካላት በሕግ የተለየ ከለላ ያላቸው መሆኑ በተባበሩት መንግስታት ቻርተር አንቀጽ105፣በተባበሩት መንግስታት ጥቅምና የተለየ ከለላን በተመለከተ ለመንደንገግ በወጣው ስምምነት አንቀጽ 2(2) እና 3 ስር መደንገጉን፣ኢትዩጵያም ይህንኑ ስምምነት መፈረሟን በዋቢነት ጠቅሶ ከመነሻውም ተጠሪ በወረዳው ፍርድ ቤት መከሰሱ ተገቢነት እንደሌለው፣አመልካች ያላቸው መፍትሔም በ"United Nations Commission on International Trade Law (UNCITRAL)" ደንቦች  መሰረት ከተጠሪ ጋር ባላቸው ስምምነት መሰረት በእርቅ መጨረስ መሆኑን፣በዋናው ጉዳይ ስልጣን የሌለው ፍርድ ቤት ጉዳዩን አይቶ መወሰኑን ከተጠሪ ጥቅምና ከባለ መብቶች አንፃር ሲታይ ዋናውን ውሳኔ ሕጋዊ የማያደርገው መሆኑን ዘርዝሮ የበታች ፍርድ ቤቶች ጉዳዩን የማየት ስልጣን የለንም በማለት የአፈጻጸም መዝገብ መዝጋታቸውን በመቀበል የአመልካችን የሰበር አቤቱታ ውድቅ አድርጎታል፡፡የአሁኑ የሰበር አቤቱታ የቀረበውም ይህንኑ ውሳኔ በመቃወም ለማስለወጥ ነው፡፡የአመልካች የሰበር አቤቱታ መሰረታዊ ይዘትም በዋናው ጉዳይ ላይ ተጠሪ ቀርቦ ባልተከራከረበት ሁኔታ በአፈጻጸም መዝገብ የተጠሪን ያለመከሰስ ከለላ በመጥቅስ ዋናውን ውሳኔ ውድቅ ማድረግ ሥነ ሥርዓታዊና የሕግ የበላይነት እንዲሁም አመልካች እንደ ዜጋ ፍትህ የማግኘት መብት ያላቸው መሆኑን ያላገናዘበ ነው በማለት መከራከራቸውን የሚያሳይ ነው፡፡አቤቱታው ተመርምሮም በዚህ ችሎት እንዲታይ በመደረጉ ለተጠሪ ጥሪ ተደርጎለት ባለመቅረቡ በጽሑፍ መልስ መስጠቱ ታልፏል፡፡

     

    የጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለመልኩ ከላይ የተገለፀው ሲሆን ይህ ችሎት ጉዳዩን ከበታች ፍርድ ቤቶች ውሳኔ እና አግባብነት ካላቸው ድንጋጌዎች ጋር በማገናዘብ እንደሚከተለው መርምሮታል፡፡

     

    በመሰረቱ በአመልካችና በተጠሪ መካከል የተነሳው ግንኙነት የቅጥር ውልን መሰረት  ያደረገ ሲሆን ዋናው ክርክር በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አግባብ ታይቶ ዳኝነት ማግኘቱን የክርክሩ ሂደት ያሳያል፡፡ የተለያዩ ዓይነት በቅጥር ላይ የተመሰረቱ የስራ ግንኙነቶች የሚኖሩ ሲሆን ግንኙነቶቹ የሚገዙበት የሕግ አግባብም ይለያያል፡፡ አዋጅ ቁጥር 377/1996 ተፈፃሚ የማይሆንባቸው ግንኙነቶች ያሉ ሲሆን ከነዚህ ውስጥ ይህ አዋጅ በየትኞቹ ላይ ተፈጻሚነት ሊኖረው እንደሚችል በዋነኝነት የሚመራው የአዋጁን የተፈጻሚነት ወሰን የደነገገው አንቀጽ 3 ነው፡፡ለዚህ ጉዳይ ቀጥተኛ አግባብነት ያለው የአንቀጹ ድንጋጌ በንዑስ ቁጥር ሶስት በፊደል "ሀ" ስር የተመለከተው ሲሆን በዚህ ንዑስ ድንጋጌ ስር የስራ ግንኙነቱ በንዑስ አንቀጽ ሁለት ስር የሚወድቁ ባለመሆናቸዉ በአዋጁ አንቀጽ 1 መሰረት በቀጥታ ሊፈጸምባቸው የሚችል ቢሆንም በንኡስ አንቀጽ 3 ስር በተገለጹት ሁኔታዎች መሰረት ከአዋጁ ሽፋን ውጭ ሊደረጉ የሚችሉ የስራ ግንኙነቶችን የሚመለከት ነው፡፡በዚሁ መሰረት ኢትዮጰያ ውስጥ የሚሰሩ የዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖች ወይም አለም አቀፍ ድርጅቶች ከኢትዮጵያውያን ጋር የሚመሰርቱት የስራግንኙነት የሚኒስትሮች ምክር ቤት በሚያወጣው ደንብ መሰረት ወይም ኢትዮጵያ በምትፈርማቸው አለምዓቀፍ ስምምነቶች መሰረት በአዋጁ ሊሸፈኑ እንደማይችሉ ተመልክቷል፡፡በመሆኑም በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጽ 3 ድንጋጌዎች ሲታዩ አዋጁ በአጠቃላይ በአሰሪና ሰራተኛ መካካል በሚቋቋም በቅጥር ላይ በተመሰረተ የስራ ግንኙነት ላይ ተፈጻሚነት የሚኖረው ቢሆንም በአዋጁ


    በግልጽ በተደነገጉ ሌላ ህግ በሚገዛቸው ግንኙነቶች ላይ ተፈጻሚነት  እንደማይኖረው ያስገነዝባሉ፡፡ በተጨማሪም አሁንም አዋጁ የሚሸፍናቸው የስራ ግንኙነቶች ሊሆኑ ቢችሉም ነገርግን የሚኒስትሮች ምክርቤት ወይም ኢትዮጵያ የምትፈርማቸው አለምአቀፍ ስምምነቶች በሚወስኑት መሰረት ከአዋጁ ሽፋን ውጭ ሊደረጉ የሚችሉ መሆኑን ተመልክቷል፡፡ከእነዚህ ድንጋጌዎች ይዘትና መንፈስ የምንረዳው ሕግ አውጪው የዲፕሎማቲክ ግንኙነቶችን ስምምነትና ልምድን ለማክበር ሲባል የውጭ ዲፕሎማቲክ ሚስዮኖቹና ኢትዩጵያውን ሠራተኞቻቸው የሚያደርጉት የቅጥር ግኙነት ላይ የአሰሪና ሰራተኛ ሕግ ተፈጻሚ እንዳይሆን ያደረገ መሆኑን ነው፡፡በመሆኑም በሕጉ በተሰጠው ስልጣን መሰረት የሚኒስትሮች ምክር ቤት በሚያወጣው ደንብ ወይም ኢትዩጵያ ከውጭ ድርጅቶች ጋር በምትፈራረምባቸው አለም አቀፍ ስምምነቶች መሰረት አዋጅ ቁጥር 377/1996 ተፈፃሚ እንዳይሆን የሚደረግበት አግባብ መኖሩን ሕግ አውጪ በግልፅ ያስቀመጠው ጉዳይ ነው፡፡የአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጽ 3(3((ሀ)) መሰረታዊ አላማ የውጭ አገር መንግሥታት ተወካዮችን ሉአላዊነት እና አለምአቀፍ ስምምነቶችን ለማክበር ተብሎ ነው ተብሎ የሚታሰብ ሲሆን በተጨባጭ ባለው ሁኔታ ደግሞ የውጪ ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖችና አለም አቀፍ ድርጅቶች ከኢትዩጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መስሪያ ቤት ጋር ስምምነት ተፈራርመው ይኼው የመንግስት አካል በእነዚህ ተቋሞች ተቀጥረው የሚሰሩት ኢትዩጵያውንን መብትና ጥቅም ለማስከበር የሚያስችል ስርዓት ዘርግቶ በአለም አቀፍ ስምምነቶች በተካተተው አግባብ የተፈጠረው አለመግባብት ሰላማዊ በሆነ መንገድ በማግባባትና በድርድር እንዲፈታ በማድረግ ላይ እንደሚገኝ የሚታወቅ ነው፡፡

     

    ወደተያዘው ጉዳይ ስንመለስም አመልካች ክርክር ያቀረቡት ግንኙነቱ በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጽ 3(3(ሀ)) መሰረት ሊገዛ ከማይችል አካል ጋር ነው፡፡ተጠሪ የተባበሩት መንግስታት አካል ሲሆን የተባበሩት መንግስታት ጥቅምና የተለየ  ከለላን በተመለከተ በተደነገገ ስምምነትም በማንኛውም መንግስት ፍርድ ቤቶች ተከሶ መቅረብ የሌለበት መሆኑን በተባበሩት መንግስታት ቻርተር አንቀፅ 105 እንዲሁም ከተባበሩት መንግስታት ጥቅምና የተለየ ከለላን በተመለከተ በተደነገገው ስምምነት አንቀጽ 2(2) እና 3 ስር በግልጽ ተመልክቷል፡፡አመልካች በዚህ ረገድ የሚያቀርቡት ክርክር የሌለ ቢሆንም አሁን አጥብቀው የሚከራከሩት በዋናው ጉዳይ ውሳኔ ከአረፈ በውሳኔው መሰረት ከሚፈጸም በስተቀር የተጠሪ በሕግ ያለው የተለየ ከለላ እንደ አቢይ ምክንያት ተወስዶ አፈፃጸሙ ሊቆም የሚችልበት አግባብ የለም በሚል ነው፡፡በሕግ አግባብ የተሰጠ ፍርድ ዋጋ እንዳይኖረው የሚደረገው የአፈጻጸም ትዕዛዝ ተገቢነት እንደሌለው ከፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 378 ድንጋጌዎች ይዘትና መንፈስ የምንገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡በሕግ አግባብ ታይቶ የተሰጠን ውሳኔ በሕጉ አግባብ ማስፈፀም በኢ.ፌ.ዲ.ሪፐብሊክ ሕገ መንግስት አንቀጽ 78(1) እና 79(1) እና (4) ስር የተረጋገጠውንና የተከበረውን የነጻ ፍርድ ቤት መኖርንና የዳኝነት ስልጣን በአግባቡ ተግባራዊ የሚያደርገው እና በሕገ መንግስቱ አንቀጽ 37 ስር የተረጋገጠው የዜጎች ፍትህ የማግኘት መብትም ውጤት ባለው መልኩ ተግባራዊ የሚሆንበት መንገድ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡አፈጻጸም በፍርድ ቤት የተሰጠ ውሳኔ ትርጉም እንዲኖረው የማድረግ ውጤት ያለውና በተገቢው መንገድም መፈፀም ያለበት መሆኑ የሚታወቅ ነው፡፡ይህ ግን ለማንኛውም ጉዳዮች ሁሉ ይሰራል ብሎ ድምዳሜ ላይ መድረስ ተገቢ ያልሆነ ሕጋዊ ውጤት የሚያስከትል መሆኑ እሙን ነው፡፡በእርግጥ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 212 ድንጋጌ ስር በስነ ስርዓት ጉድለት አንድ ፍርድ ውድቅ ሊሆን እንደማይችል የተመለከተ ሲሆን ይህ ግን የሚሰራው የፍትሓ  ብሔር ስነ ስርዓት ሕጉ ተፈፃሚነት ወስንን መሰረት በማድረግ በሌላ አኳኃን እንዲፈፀም በሕግ


    ባልተደነገገበት ሁኔታ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡በመሆኑም ከመነሻውም ኢትዩጵያ በፈረመችው አለም አቀፍ ስምምነት መሰረት በኢትዩጵያ ፍርድ ቤቶች ላለመዳኘት ነገር ግን ከኢትዩጵያ ዜጎች ጋር ለመሰረተው ግንኙነት በሌላ አግባብ ጉዳዩን ለመጨረስ የሚያስችል ስርዓት ያለው ወገን በዋናው ክርክር ጊዜ ቀርቦ ባለመከራከሩና በይግባኝ ጉዳዩን ባለማሳረሙ ምክንያት ብቻ ስልጣን የሌለው ፍርድ ቤት የሰጠውን ውሳኔ እንዲፈጽም የሚገደድበት አግባብ የለም፡፡ስለዚህ ከዚህ ጉዳይ የተለየ ባሕርይ ስንነሳ የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 212 እና 4 ድንጋጌዎች አንድ ላይ ተጣምረው ሲታዩ አፈፃጸሙ ዋጋ ያለውን ፍርድ መሰረት ያደረገ ነው፣ጉዳዩ ከስነ ስርዓት ጉድለት ጋር የተያያዘ ነው ለማለት የሚቻል ሁኖ አላገኘነም፡፡ተጠሪ በሕግ የተጠበቀለት የከለላ መብትና ጥቅም እያለው ስልጣን የሌለው ፍርድ ቤት የሰጠውን ውሳኔ እንዲፈጽም ማድረግ ሕግ አውጪው የዲፕሎማቲክ ግንኙነቶችን ልምድን ለማክበር ሲባል በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጽ 3(3(ሀ)) ስር ያስቀመጠውን ድንጋጌ  ዋጋ የሚያሳጣው እና በዲፕሎማቲክ ግንኙነቱም አሉታዊ ውጤት የሚያስከትል በመሆኑ ተመራጭ ሁኖ አላገኘነውም፡፡ሲጠቃለልም የጉዳዩ ልዩ ባህርይ ሲታይ የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 212 ድንጋጌን ጠቅሶ አፈፃጸሙን ማስቀጠል የሚቻልበት አግባብ ስለሌለና አመልካችም እንደዜጋ መንግስት በውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት በኩል በዘረጋው ስርዓት መሰረት መብትና ጥቅማቸውን የሚያስከበሩበት ሁኔታ ያለ በመሆኑ የሕግ የበላይነት አልተከበረም፣ የዜጋ ፍትህ የማግኘት ሕገ መንግስታዊ መብት ተጥሷል ለማለት ስላልተቻለ የክልሉ ፍርድ ቤቶች የሰጡት ውሳኔ መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት የለበትም በማለት ተከታዩን ወስናል፡፡

     

     ው ሣኔ

     

    1.  በኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በመ/ቁጥር

    163639 ታህሳስ 07 ቀን 2006 ዓ/ም የበታች ፍርድ ቤቶችን ትዕዛዝ በማፅናት የተሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰረት ፀንቷል፡፡

    2. የአመልካች የአፈጻጸም ክስ መዘጋቱ ተገቢ ነው ብለናል፡፡አመልካች አለኝ የሚሉትን መብትና ጥቅም በሌላ አግባብ ከመጠየቅ ይህ ውሳኔ አያግዳቸውም ብለናል፡፡

    3. በዚህ ችሎት ለተደረገው ክርክር የወጣውን ወጪና ኪሳራ አመልካች የራሳቸውን ይቻሉ ብለናል፡፡

    መዝገቡ ተዘግቷል፤ወደ መዝገብ ቤተ ይመለስ ብለናል፡፡

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት::

     

     

     

     

    መ/ብ

  • አንድ ባለሙያ በአሠሪው ቁጥጥር ሳይሆን በራሱ የሙያ ኃላፊነት የሙያ አገልግሎት ለመስጠት ከአንድ አሠሪ ጋር ውል ሲኖረው ጉዳዩ የሚገዛው በአሠሪና ሠራተኛ ህግ ስላለመሆኑ፣

    -ከአንድ ባለሙያ ጋር የሙያ ግልጋሎት ውል ያለው አሠሪ ውሉን በማናቸውም ጊዜ ማፍረስ ሥለመቻሉ፣

    አዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 3 ንዑስ አንቀስ /1//2/ የፍ/ህ/ቁ. 2140፣2646/1/፣ 2638/1/

     

    የሰ/መ/ቁ. 101396

     

    ታህሳስ 21 ቀን 2007 ዓ.ም

     

    ዳኞች፡- አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሱልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኸሊት ይመሰል

    አመልካች፡- አዲስ አጠቃላይ ሆስፒታል ጠበቃ አብደላ ዓሊ ቀረቡ ተጠሪ፡- ዶ/ር ምስራቅ ጥላሁን ጠበቃ አቶ ስመኘው አራጌ ቀረቡ

    መዝገቡን መርምረን የሚከተለውን ፍርድ ሰጥተናል

     

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ የቀረበው አመልካች የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 42275 ሐምሌ 9 ቀን 2005 ዓ.ም የሰጠው ውሣኔና የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 135997 ግንቦት 18 ቀን 2006ዓ.ም የሰጠው ውሳኔ መሠረታዊ የሕግ ስህተት ያለበት ስለሆነ በሰበር ታይቶ ይታረምልኝ በማለት ያቀረበውን የሰበር አቤቱታ አጣርቶ ለመወሰን ነው፡፡ ጉዳዩ የሥራ ውል ከሕግ ውጭ በአሠሪው ተቋርጣል በማለት ያቀረቡትን ጥያቄየሚመለከት ነው፡፡

    1. የክርክሩ መነሻ ተጠሪ ያቀረበው የክስ ማመልከቻ ነው፡፡ተጠሪ በአመልካች ድርጅት ውስጥ በወር ብር 8000,/ስምንት ሺ ብር/ እየተከፈለው በራዲያሎጅስት ሙያ ከጥር 1 ቀን 2000ዓ.ም ጀምሮ ሲያገለግሉ የቆዩ መሆኑን ገልፀው፤አሰሪው አመልካች ከሕግ አግባብ ውጭ ያቋረጠ ስለሆነ በአዋጅ ቁጥር 377/96 ድንጋጌዎች መሠረት የተለያዩ ክፍያዎች እንዲከፍል ውሣኔ ይሰጥልኝ በማለት አመልክተዋል፡፡

    አመልካች ተከሣሽ ሆኖ ቀርቦ ከከሳሽ/ተጠሪ/ጋር የሥራ ቅጥር ውል ግንኙነት የለንም፡፡ከሳሽ ጋር ያለን ግንኙነት፣ከሳሽ በትርፍ ሠዓታቸው የሙያ ግልጋሎት እየሰጡ ክፍያ የሚያገኙበት የውል ግንኙነት ነው፡፡ተከሳሽ ይህንን በትርፍ ሠዓት የሚሰጥ የሙያ ግልጋሎት ውል አላቋረጠም፡፡ ከሳሽ የሙያ ፈቃዳቸውን ከጤና ጥበቃ ሚኒስትር ያላሳደሱ በመሆኑ ፈቃዳቸውን አድሰው ሲቀርቡ ሥራ የሚጀምሩ ፤መሆኑን ተገልፆላቸዋል ከሳሽ በድርጅታችን ውስጥ በቀን ሁለት ሰዓት የሚሠራ ሲሆን በጡረታ የተገለሉ በመሆኑ ከከሳሽ ጋር ቋሚ የሆነ የአሠሪና የሠራተኛ ግንኙነት የላቸውም በማለት ተከራክረዋል፡፡

    2. የሥር ፍ/ቤት ግራ ቀኙ ያቀረቡትን ክርክር ከመረመረ በኃላ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የከሳሽን ስም በመጥቀስ ጥቅምት 5 ቀን 2002 ዓ.ም የፃፈው ደብዳቤና ሌሎች የፅሑፍ ሰነዶች በማስረጃነት ያቀረቡለት መሆኑን ጠቅሶ በከሳሽ እና በተከሳሽ መካከል የአሠሪና ሰራተኛ ግንኙነት አለ ከሳሽ የተከሳሽን የሥራ ውል ያቋረጠው ከሕግ አግባብ ውጭ ነው


    በማለት ከሳሽ ለተከሳሽ የሥራ ስንብት ክፍያ የማስጠንቀቂያ ክፍያ የካሣ ክፍያና ክፍያ ለዘገየበት ክፍያና የፅሁፍ ክፍያ እንዲከፍል ውሳኔ ሰጥቶበታል፡፡ አመልካች በዚህ ውሳኔ ቅር በመሰኘት ይግባኝ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቅርቧል፡፡ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኃላ የሥር ፍርድ ቤት የሰጠውን ውሣኔ አፅንቶታል፡፡

    3. አመልካች ግንቦት 28 ቀን 2005 ዓ.ም በተፃፈ የሰበር አቤቱታ ተጠሪ ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ተሰጥቷቸው ከአመልካች ዘንድ በቀን ሁለት ሠዓት ብቻ የሚያገለግሉራዲዮሎጂስት ናቸው፡፡ ይህ ፍሬ ጉዳይ በተጠሪ አልተካደም ይህም በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀፅ 3 ንዑስ አንቀጽ 2(1) የሚሸፈንና በአመልካች እና በተጠሪ መካከል የአሠራና እና ሠራተኛ ግንኙነት የሌለ መሆኑን የሚያሳይ ሆኖ እያለ የበታች ፍርድ ቤቶች የሥራ ውል አላግባብ ተቋርጧል በማለት የተለያዩ ክፍያዎች እንድከፍል መወሰናቸው መሠረታዊ የሕግ ስህተት ያለበት ስለሆነ በሰበር ታይቶ እንዲታረምልኝ በማለት አመልክቷል፡፡ ተጠሪ ሐምሌ 17 ቀን 2005 ዓ.ም በተፃፈ መልስ እኔ በራሴ ኃላፊነት ሳይሆን በአመልካች ኃላፊነትና ቁጥጥር ሥር ሆኜ ሥራ የምሠራ ሠራተኛ ነኝ፡፡ ሬዲዮሎጅስት አገልግሎት የሚሰጥበት የሙያ ዘርፍ ነው፡፡ አመልካች ከሚገኘው ደመወዝ በየወሩ የሥራ ግብር 2,433.65(ሁለት ሺ አራት መቶ ሰላሣ ሶስት ብር ከስልሣ አምስት ሣንቲም ) እየቀነሰ ያስቀራል እንጅ በቀን ሁለት ሰዓት መስራት የአመልካችና የእኔን የስራ ውል ስምምነት  የሚያሳይ  እንጂ የአመልካች ሰራተኛ አለመሆኔን የሚያሳይ አይደለም፡፡ ስለዚህ የበታች ፍርድ ቤቶች የሰጡት ውሣኔ ይጽናልኝ በማለት ተከራክረዋል፡፡ አመልካች ሐምሌ 29 ቀን 2006 ዓ.ም የተፃፈ የመልስ መልስ አቅርበዋል፡፡

    4. ከሥር የክርክሩ አመጣጥና በሰበር የቀረበው ክርክር ከላይ የተገለፀው ሲሆን  እኛም የበታች ፍርድ ቤቶች በአመልካችና በተጠሪ መካከል በአዋጅ ቁጥር 377/1996 የሚሸፈን የአሠሪና ሠራተኛ ግንኙነት አለ፣ አመልካች ከሕግ አግባብ ውጭ የሥራ ውሉን አቋርጧል በማለት የተለያዩ ክፍያዎች አመልካች ለተጠሪ እንዲከፍል የሰጠው የሕግ መሠረት ያለው ነው ወይስ አይደለም የሚለውን ጭብጥ በመያዝ ጉዳዩን መርምረናል፡፡

    5. ጉዳዩን እንደመረመርነው ተጠሪ “በሬድዮሎጂ” የሕክምና ሙያ የስልጠና በቂ ዕውቀትና ክህሎት ያለውና የደንብ ቁጥር 76/1994 አንቀፅ 20 በሚደነግገው መሠረት በሕግ ሥልጣን ከተሰጠው አካል በሙያው የሕክምና አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችለው የሙያ ብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት የተሰጠው ባለሙያ መሆኑ በግራ ቀኙ ክርክርና ማስረጃ ተረጋግጧል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ተጠሪ ከጥር 1 ቀን 2000 ዓ.ም ጀምሮ በአመልካች ድርጅት በቀን ለሁለት ሠዓት ያህል በመገኘት ከአመልካች ጋርበፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2641 በሚደነግገው መሠረት የሆስፒታል ውል ከተዋዋሉ የአመልካች ደንበኞች የሙያ አገልግሎት ሲሰጥ የቆየ መሆኑና ተጠሪ ለሚሰጠው አገልግሎት አመልካች በየወሩ ብር 8000 /ስምንት ሺ ብር/ክፍያ ሲከፍለው  የኖረ መሆኑ በግራ ቀኙ ክርክርና ማስረጃ ተረጋግጧል፡፡

    6. አመልካች እና ተጠሪ ከላይ የተገለፀው አይነት የውል ግንኙነት የነበራቸው መሆኑ አያከራክርም፡፡ አከራካሪው ጉዳይ ይኽ በአመልካችና በተጠሪ መካከል ፀንቶ የኖረው ግንኙነት የአሠሪና ሠራተኛ ግንኙነት ነው ወይስ የዕውቀትና የሙያ ሥራ ለማከራየት የተደረገ የውል ግንኙነት ነው? የሚለው ነጥብ ነው፡፡ ይህንን ጭብጥ ለመወሰን በአመልካች ተጠሪና የሕክምና አገልግሎት በሚሰጣቸው ህሙማን /የአመልካች ደንበኞች


    መካከል የሚኖረውን ግንኙነት መመልከት ያስፈልጋል፡፡ ከላይ እንደተገለፀው አመልካች በደንብ ቁጥር 76/94 አንቀጽ 20 እና ተከታይ ድንጋጌዎች መሠረት በሙያው የሕክምና ግልጋሎት ለመስጠት የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት ያለው ባለሙያ ነው፡፡ከዚህ በተጨማሪ አመልካች የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2140 በሕክምና ባለሙያዎች ላይ የሚጥለው ግዴታና በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2646(1) መሠረት ለሚሰጠው አገልግሎት የአመልካች ደንበኛ ከሚከፍለው ክፍያ ተጠሪ ምን ያህል ገንዘብ በወር ሊከፈለው እንደሚችል በውል በመስማማት፣ሙሉ በሙሉ በአመልካች ተቆጣጣሪነትና አሠሪነት እየተመደበ ሳይሆን ፣በቀን ለሁለት ሠዓቶች ሙያዊ አገልግሎትየሚሰጥ ባለሙያ መሆኑን የግራ ቀኙ ክርክርና በበታች ፍርድ ቤቶች የተረጋገጡት ፍሬ ጉዳዮች ያሳያሉ፡፡

    7. የአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ የተፈፃሚነት ወሰን በዝርዝር የሚደነግገው በአዋጅ ቁጥር 397/96 አንቀፅ 3 ፣ንዑስ አንቀፅ (1) አዋጅ በአሠሪና ሠራተኛ መካከል በሚደረግ በቅጥር ላይ የተመሠረተ የሥራ ግንኙነት ላይ ተፈፃሚ እንደሚሆን በመርህ ደረጃ ደንግጓል፡፡ አዋጅ በዚህ ጠቅላላ መርህ የማይካተቱና የቅጥር ላይ የተመሰረቱ የሥራ ግንኘነቶች በአዋጅ ቁጥር 377 አንቀጽ 3 ንዑስ አንቀጽ 2 በልዩ ሁኔታና በዝርዝር ደንግጓል፡፡ የአዋጅ አንቀፅ 3 ንዑስ አንቀፅ 2 ድንጋጌ ቃል በቃል ሲነበብ ‹‹ይህ አዋጅ ከዚህ በታች በተዘረዘሩት በቅጥር ላይ በተመሠረቱ የሥራ ግንኙነቶች ላይ ተፈፃሚ አይሆንም ›› የሚል ይዘት ያለው ሲሆን በአዋጅ አንቀጽ 3 ንዑስ አንቀጽ 2 በዝርዝር ከተደነገጉ አዋጅ ተፈፃሚነት ከማይሆንባቸው ግንኙነቶች ውስጥ፤አንድ ተዋዋይ ወገን ዋጋ እየተከፈለው በራሱ የንግድ ሥራ ወይም በራሱ የሙያ ኃላፊነት የሚሠራ ስራ የሚያከናውን ሲሆን፣አዋጅ ቁጥር 377/96 ድንጋጌዎች ተፈፃሚነት የሌላቸው መሆኑ በአዋጅ አንቀጽ 3 ንዑስ አንቀጽ 2(1) ተደንግጓል፡፡

    8. ከላይ እንደተገለፀው ተጠሪ ሙሉ በሙሉ በአመልካች መሪነትና ቁጥጥር ሣይሆን በአመልካች ድርጅት ውስጥ በቀን ለሁለት ሠዓት ያክል ከአመልካች ጋር የሆስፒታል ውል ለተዋዋሉ የአመልካች ደንበኞች የራድዮሎጅ የሙያ ግልጋሎት በራሱ የሙያ ኃላፊነት የሚሰጥ ነው፡፡ አመልካች ተጠሪ ይህንን የሙያ ግልጋሎቱን ሌላ ቦታ የሚገኝ የህክምና ተቋም ወይም ከአመልካች ጋር ምንም አይነት የሆስፒታል ውል ግንኙነት ለሌላቸውና የአመልካች የህክምና ካርድ ላልያዙ ሰዎች እንዲሰጥናየሥራ ስምሪት መስጠትና አመልካችን ተቆጣጥሮ ማሠራት አይችልም፡፡ ከዚህ  በተጨማሪ ተጠሪ የአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀፅ 61 እና ተከታታይ ድንጋጌዎች መሠረት በቀን ሥምንት ሠዓት በሣምንት አርባ ሥምንት ሠዓት ከሥራ ቦታ እንዲገኝ ለማስገደድና ተቆጣጥሮ ማሰራት እንደማይችል የግራ ቀኙ ክርክርና ከበታች ፍርድ ቤቶች ውሣኔ ተረድተናል፡፡

    9. የሥር ፍ/ቤት ተጠሪ በቀን ለሁለት ሠዓት ብቻ አገልግሎት መስጠቱ፤ ከአመልካች ጋርበአዋጅ ቁጥር 377/96 የሚሸፈን የአሠሪና ሠራተኛ ግንኙነት ከመመስረት አይገድበውም በማለት ውሣኔ ሰጥቷል፡፡ ሆኖም ይህ የስር ፍርድ ቤት የሰጠው የሕግ ትርጉምና ውሳኔ የአዋጅ ቁጥር 377/1996 ከአንቀፅ 61 እስከ አንቀፅ  64 የተደነገጉትን ድንጋጌዎች ይዘትና ውጤት ያገናዘበ ካለመሆኑም በላይ ፣በአዋጅ አንቀጽ 65 ልዩ ድንጋጌ ያገናዘበ ሆኖ አላገኘነውም፡፡ በአዋጅ አንቀጽ 65 መሠረት በሥራ ውሉ  ወይም በህብረት ስምምነት በሌላ አኳኃን ካልተወሰነ በስተቀር ፣የአዋጁ የስራ ሰዓት የሚመለከቱት ከአንቀጽ 61 እስከ አንቀጽ 64 የተደነገጉት ድንጋጌዎች ተፈፃሚነት የማይኖራቸው በንግድ መልዕክተኞች በንግድ ወኪሎች ላይ እንደሆነ በግልፅ ተደንግጎአል፡፡ ከዚህ አንፃር


    የሥር ፍርድ ቤት የአዋጅ የሥራ ሠዓት ድንጋጌዎች ተጠሪ የአመልካች ቅጥር ሰራተኛ ነው ብሎ ለመወሰን ተፈፃሚነት እንደሌላቸው በመግለፅ የሰጠው ትርጓሜ የአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀፅ 65 ልዩ ድንጋጌ ያላገናዘበና መሠረታዊ የሕግ ስህተት ያለበት ሆኖ አግኝተነዋል፡፡

    10. ከላይ በዝርዝር የተገለፁት ምክንያቶች ተጠሪ በአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 3 ንዑስ አንቀፅ 2/1) መሠረት ከአመልካች ቁጥጥርና የሥራ አለመረዳት ሣይገደብ በራሱ የሙያ ኃላፊነት በቀን ለሁለት ሠዓት የራዲዮሎጅ የሙያ አገልግሎት የሚሰጥ ባለሙያ እንጅ የአመልካች ሠራተኛ አይደለም፡፡ ተጠሪ ለአመልካች የሚሰጠው የእውቀት  ግልጋሎት እና ሥራ ውል በመሆኑ አመልካች በማናቸውም ጊዜ ውሉን ለማፍረስ የሚችል መሆኑን በፍትሐብሔር ህግ ቁጥር 2638 ንዑስ አንቀጽ 1 ተደንግጓል፡፡ ይህም በመሆኑ አመልካች አግባብነት ያለውንና ተፈፃነሚነት ያለውን የህግ ድንጋጌ መሠረት በማድረግ አለኝ የሚለውን መብትና ጥቅም ከሚጠይቅ በስተቀር ተጠሪ የአዋጅ ቁጥር 377/1996 ድንጋጌዎች መሠረት የተለያዩ ክፍያዎች እንዲከፍለው የመጠየቅ መብት የለውም ። በመሆኑም የበታች ፍ/ቤቶች የሰጡት ውሳኔ ከላይ በዝርዝር የጠቀስናቸውን የሕግ ድንጋጌዎች የሚጥስና መሠረታዊ የሕግ ስህተት ያለበት ነው በማለት ወስነናል፡፡

     ው ሣ ኔ

     

    1. የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤትና የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሰጡት ውሳኔ ተሸሯል ፡፡

    2. ተጠሪ በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጽ 3 ንዑስ 2(1) መሠረት በራሱ የሙያ ኃላፊነት በቀን ለሁለት ሠዓት የሙያ አገልግሎት የሚሠጥ በመሆኑ የአመልካች ቅጥር ሠራተኛ ሣይሆን የዕውቀት ሥራና ግልጋሎት ለመሰጠት የተዋዋለ ባለሙያ ነው በማለት ወስነናል፡፡

    3. አመልካች ከተጠሪ ጋር የነበረውን የሙያ (ዕውቀት)ሥራ ግልጋሎት ውል ያቋረጠው በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2637 ንዑስ አንቀፅ 1 መሠረት ነው በማለት ወስነናል፡፡

    4. ይኽ ውሣኔ ተጠሪ የሙያ ግልጋሎት ውሉ በመቋረጡ ምክንያት አለኝ የሚለውን የመብት ጥያቄ ከማቅረብ የሚገድበው አይደለም ብለናል፡፡

    5.  በዚህ ፍርድ ቤት የወጣውን ወጭና ኪሣራ ግራ ቀኙ ለየራሳቸው ይቻሉ፡፡

     

     

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት ፡፡

  • አንድ አሠሪ ለሙከራ የቀጠረውን ሠራተኛ በቀጠረው በ46ኛው ቀን ለስራው ብቁ አይደለም ብሎ የስንብት ደብዳቤ ቢጽፍለት ድርጊቱ ህገ ወጥ ነው ሊባል የማይችል ስለመሆኑ፣

     

    አዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 11(2)፣(3)

    የሰ/መ/ቁ. 101890

    ጥቅምት 24 ቀን 2007 ዓ.ም.


     

    አመልካች፡- የኢትዮጵያ አየር መንገድ- ጠበቃ አውላቸው  ደሣለኝ ቀረቡ፡፡ ተጠሪ፡- ወ/ት ፍጹም ኃይሉ - የቀረበ የለም፡፡

    መዝገቡ ተመርምሮ የሚከተለው ፍርድ ተሰጥተናል፡፡

     ፍ ር ድ

     

    በዚህ ጉዳይ የቀረበው ክርክር የሥራ ውሉ ማቋረጡን የሚመለከት ነው፡፡ ለዚህ ሰበር አቤቱታ መነሻ የሆነው ተጠሪ ያቀረቡት ክስ ነው፡፡ የተጠሪ የዳኝነት ጥያቄ አመልካች ከግንቦት 3ዐ ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ በዕቃ ግምጃ ቤት ተቆጣጣሪነት በቋሚ ደመወዝ ብር 2,639 የቀጠራቸው መሆኑና ያለማስጠንቀቂያ በ12/11/2005 የተፃፈ የቅጥር ውል ማቋረጫ ደብዳቤ በ15/11/2005 እንዲሰጣቸው በሕገወጥ መንገድ ከሥራ ሰለአሰናበታቸው የተለያዩ ክፍያዎች ተከፍሏቸው ወደ ሥራ እንዲመለሱ እንዲወሰን የሚል ነበር፡፡ የአሁኗ ተጠሪ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ በትብብር በሚሰራ ድርጅት ተቀጥረው ሲሰሩ ስለነበር የተቀጠሩት በቋሚነት ነው በማለት ያቀረቡት ክርክር ከቀረበው ማስረጃ አንፃር ተገቢነት የለውም በማለት የታለፈ ሲሆን በግራ ቀኙ የነበረው የሥራ ውል ግንኙነት በ29/09/2005 ዓ.ም በተፃፈው ደብዳቤ ከግንቦት 7 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ ለ45 ቀናት የሙከራ ቅጥር ተቀጥረው ሲሰሩ እንደነበር መሠረት በማድረግ ታልፏል፡፡

    አመልካች በሥር ፍርድ ቤት በተደረገው ክርክር ተጠሪ ሊመደቡበት ላቀደው የዕቃ ግምጃ ቤት የስራ መደብ ተስማሚ መሆናቸውን ለመመዘን ለ45 ቀናት የሙከራ ግዜ ተቀጥረው ለታቀደው ሥራ ተስማሚ ያለመሆናቸውን በማረጋገጥ ሕጉ በሚፈቅደው አግባብ የሥራ ውል ማቋረጡን ገልጿል፡፡ የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት የግራ ቀኙ ክርክር እና ማስረጃ በማገናዘብ በሰጠው ውሣኔ ተጠሪ በሰጡት የምስክርነት ቃል የሥራ ውል ማቋረጫ ደብዳቤ የተሰጣቸው እ.ኤ.አ ጁላይ 22/2013 ወይም ወደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር ሲመለስ ሐምሌ 15/11/2005 መሆኑን ፤ የአመልካች ምስክርም ደብዳቤው የተሰጣቸው ጁላይ 19 ቀን 2013 ወይም ሐምሌ 15 ቀን 2005 ዓ.ም ነው በማለታቸው የተጠሪ የሥራ ውል ማቋረጫ ደብዳቤ የተሰጣቸው በ46ኛው ቀን ሐምሌ 15/11/2005 ዓ.ም በመሆኑ ስንብቱ የሕግ መሠረት የለውም፡፡ አመልካች ለተጠሪ ያልከፈላቸው የ22 ቀናት ቀሪ ደመወዝ እንዲሁም የካሣ ክፍያ እንዲከፍላቸው የሥራ ልምድ ማስረጃም እንዲሰጣቸውበማለት ወስኗል፡፡ በይግባኝ ሥልጣኑየተመለከተው ከፍተኛ ፍ/ቤትም የአመልካችን ይግባኝ ሰርዞታል፡፡

    አመልካችም በሥር ፍ/ቤቶች ፍርድ ላይ ቅር በመሰኘት የሰበር አቤቱታ ያቀረቡ ሲሆን የቅሬታ ነጥቡም ሲጠቃለል፡- በአመልካች እና ተጠሪ የነበረው የሥራ ግንኙነት ሕጉ በሚፈቅደው አግባብ ጁላይ 19 ቀን 2013 እ.ኤ.አ በተፃፈ ደብዳቤ መቋረጡ፤ ይህ ደግሞ ወደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር ሲመለስ ሐምሌ 12 ቀን 2ዐዐ5 ዓ.ም መሆኑን እየታወቀ የውል መቋረጫ ደብዳቤ በ43ኛው  ቀን


    ተድፎ ሳለ ስንብቱ በ46ኛው ቀን የተደረገ በመሆኑ ሕገ ወጥ ነው ተብሎ በሥር ፍርድ ቤት መወሰኑ ያላግባብ ነው የሚል ነው፡፡ ተጠሪ በበኩላቸው በሰጡት መልስ ከአሁን በፊት ለ5ወር ከ6 ቀን በማቴሪያል ኢንቨንተሪ ኮንትሮል ሥራ በአመልካች መስሪያ ቤት መሥራታቸው እየታወቀ ድጋሚ በዚያው ሥራ በሙከራ የቅጥር ውል መሥራታቸው ሕጋዊ አለመሆኑን

    ፤የሥር ፍ/ቤት ማስረጃዎች በመመዘን ውሣኔ መስጠቱ ፤የተጠሪ ምስክሮች የሥራ ውል ማቋረጫ ደብዳቤ እ.ኤ.አ ጁላይ 22 ቀን 2013 እንደተሰጣቸው ማስረዳታቸውአመልካች በሕግ የተቀመጠውን 45 ቀን አሳንሶ በ43ኛው ቀን የስንብት ደብዳቤ መስጠት እንደማይችል፤ ደብዳቤውም ከሥራ ሰዓት ውጭ የተሰጣቸው መሆኑንበመግለጽ የሥር ፍ/ቤት እንዲፀና አመልክቷል፡፡ አመልካችም ተጠሪ ላቀረቡት መልስ የመልስ መልስ በማቅረብ አቤቱታውን በማጠናከር ተከራክሯል፡፡

    የጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለ መልኩ ከላይ የተገለፀው ሲሆን ይህ ችሎትም የግራ ቀኙክርክር ለሰበር አቤቱታ መነሻ ከሆነው ውሳኔ እና አግባብነት ካላቸው ድንጋጌዎች ጋር በማዛመድ ጉዳዩ ለሰበር ችሎት ሲቀርብ ከተያዘው ጭብጥ አንፃር በሚከተለው መልኩ መርምሮታል፡፡

    ከሥር ፍርድ ቤት መዝገብ መረዳት እንደተቻለው በአመልካች እና ተጠሪ በሙከራ ጊዜ ላይ የተመሰረቱ የሥራ ቅጥር ውል መፈፀሙን ነው፡፡ ተጠሪ ከድርጅቱ ጋር ግንኙነት ባለው ሌላድርጅት በዚህ የሥራ መደብ ላይ ሲሰሩ እንደነበር በድጋሚ በተመሳሳይ የሥራ መደብ ለሙከራ መቀጠራቸው ሕጋዊ አለመሆኑን በመጥቀስ ቢከራከሩም የሥር ፍርድ ቤት  ለሙከራ የተቀጠሩበት ደብዳቤ በማስረጃነት በመውሰድ ክርክራቸው አግባብነት የሌለው መሆኑን በውሣኔው አስፍሯል፡፡ ተጠሪ ይህንን ውሣኔ በመቃወም ያቀረቡት ይግባኝ ይሁን መስቀለኛ አቤቱታ የለም፡፡ በዚህ ረገድ በሰበር አቤቱታቸው በሥር መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት ውድቅ የተደረገው ክርክር በሰበር ደረጃ ማቅረባቸው ሥነ-ስርዓታዊ አካሄድ የተከተለ አይደለም፡፡

    አንድ ሠራተኛ ሊመደብበት ለታቀደው ቦታ ተስማሚ መሆኑና አለመሆኑን ለመመዘን ለሙከራ ጊዜ ሊቀጠር እንደሚችል፤ ይህ የግራ ቀኙ ስምምነትም በጽሑፍ መደረግ እንዳለበት፤ የሙከራ ጊዜውም ከ45 ተከታታይ ቀናት መብለጥ እንደሌለበት ከአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 11(1) ፣(2) እና (3) አጠቃላይ ይዘትና መንፈስ የምንገነዘበው ነው፡፡ አመልካች ተጠሪን ለሙከራ ጊዜ መቅጠሩ በሥር ፍ/ቤት የታመነበት ጉዳይ ነው፡፡ አመልካች ተጠሪን በግዜ ገደቡ ውስጥ ማሰናበቱን ሲከራከር ተጠሪ ደግሞ በ46ኛው ቀን የተሰናበቱ መሆናቸው በመግለፅ ስንብቱ ህገ ወጥ እንዲባልላቸው አመልክተዋል፡፡ በስር ፍ/ቤት የአመልካች ምስክሮች ስንብቱ እ.ኤ.አ. ጁላይ 19 ቀን 2013 መሆኑን ይህ ደግሞ ወደ ኢትዮጵያ የጊዜ አቆጣጠር ሲመለስ ሐምሌ 15 ቀን 2005 ዓ.ም መሆኑን በሥር ፍርድ ቤት መዝገብ ሰፍሯል፡፡ ተጠሪ በሰጡት የምስክርነት ቃል የስንብት ደብዳቤው እ.ኤ.አ. ጁላይ 22 ቀን 2013 መሆኑ፤የጊዜ ስሌቱ ሲሰራ ከተቀጠሩበት ጊዜ ጀምሮ በ46ኛው ቀን መሆኑን ገልጿል፡፡ የሥር ፍርድ ቤቱ የአመልካች ድርጊት ሕገወጥ ነው ለማለት እንደመነሻ የወሰደው ተጠሪን በ46ኛው ቀን ከሥራ አሰናብቷል በሚል ነው፡፡ አመልካች ተጠሪን ያሰናበታቸው በ43ኛ ቀን ነው?ወይስ በ46ኛው ቀን?በ46ኛው ቀን ሲሰናበቱ ሕጋዊ ውጤቱስ የተለየ ሊሆን ይችላል? የሚለው መመልከቱ ተገቢ ነው፡፡ የሥር ፍ/ቤት በአመልካች ተሰጠ የተባለው ደብዳቤ እ.ኤ.አ አቆጣጠር ጁላይ 19 ቀን 2013 ዓ.ም የተጻፈ መሆኑ ወደ ኢትዮጵያ የጊዜ አቆጣጠር ሲመለስ                         ደግሞ ሐምሌ 15 ቀን 2ዐዐ5 ዓ.ም  መሆኑን በውሣኔው አስፍሯል፡፡ የሥር ፍርድ ቤት እ.ኤ.አ. ጁላይ 19 ቀን 2013 ወደ ኢትዮጵያ የጊዜ አቆጣጠር ሲመለስ  ሐምሌ  15  ቀን 2ዐዐ5  ዓ.ም  በማለት በውሣኔ  የተጠቀሰው  ተቀባይነት

    /conventional/ ካልሆነው የጊዜ አቆጣጠር ቀመር አኳያ ሲታይ አግባብነት ያለው አይደለም፡፡ ከላይ የተገለፀው ጁላይ 19 ቀን 2ዐ13 ወደ ኢትዮጵያ የጊዜ አቆጣጠር ሲመለስ ሐምሌ 12  ቀን


    2ዐዐ5 ዓ.ም መሆኑን ተቀባይነት ካለው የጊዜ አቆጣጠር /ካላንደር/ አንፃር በማዛመድ በቀላሉ ግንዛቤ የሚወሰድበት ነው፡፡ በመሆኑም የሥር ፍርድ ቤት ጁላይ 19 ቀን 2ዐ13 እ.ኤ.አ ወደ ኢትዮጵያ የጊዜ አቆጣጠር ሲመለስ ሐምሌ 15 ቀን 2ዐዐ5 ዓ.ም ነው፡፡ በማለት ማስፈሩ አግባብነት ያለው ሆኖ አልተገኘም፡፡ አመልካች ተጠሪን ሐምሌ 12 ቀን 2ዐዐ5 ዓ.ም በፃፈው ደብዳቤ የሙከራ ግዜ ቅጥር ውል እንዲቋረጥ የተደረገ ከሆነ በ45 ቀን ጊዜ ገደብ ውስጥ የተፃፈ ደብዳቤ መሆኑ መረዳት ይቻላል ፡፡ አመልካች ተጠሪ ሊመደቡበት ለታቀደው ቦታ ተስማሚ መሆኑን አለመሆናቸው በ45 ቀን ውስጥ ውሣኔ ማስተላለፍ ለዚህ ጉዳይ አግባብነት ካለው ሕግ ጋር የሚቃረን ውሣኔ አይደለም፡፡

    የሥር ፍርድ ቤት የአመልካች ድርጊት ሕገወጥ ነው በማለት ለመወሰን እንደ መነሻ የወሰደው ስንብቱ በ46ኛው ቀን ተከናውኗል በሚል ነው፡፡አንድ አሠሪ የሙከራ ጊዜ ውል ያለአግባብ በማሳጠር ይሁን ከሚገባው በላይ ጊዜው በማራዘም የሠራተኛው የተረጋጋ የሥራ ዋስትና እንዳይኖር ማድረግ እንደሌለበት ከአጠቃላይ የአሠሪና ሠራተኛ አዋጅቁ. 377/96 ድንጋጌዎች የምንገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡ ይሁንና አሠሪው በ45ኛው ቀን መጨረሻ ይሁን በ46ኛው ቀን መጀመሪያ ሠራተኛው ለተመደበበት የሥራ ቦታ ተስማሚ አይደለም በማለት ከወሰነ የፈጠነ ወይም በጣም የዘገየ ውሣኔ ነው ለማለት አይቻልም፡፡ የሙከራ ግዜው በ45ኛው ቀን መጨረሻ የሚጠናቀቅ ከሆነ በ46ኛው የመጀመሪያ ቀን የስንበት ደብዳቤ መፃፉ የሠራተኛው የሥራ ዋስትና አደጋ ውስጥ አስገብቷል ለማለት የሚያስችል አሳማኝ ምክንያት የለውም፡፡ በሥር ፍ/ቤት ተረጋግጧል የተባለው ፍሬ ነገር ተወስዶ ደብዳቤው በ46ኛው ቀን ነው የተፃፈው ቢባል እንኳ የአሠሪው የማሰናበት መብትና ሥልጣን ዘግይቶ ተግባራዊ የተደረገ ነው ሊባል አይችልም፡፡ የሙከራ ጊዜ ውል ለ 45 ተከታታይ ቀናት የሚቀጥል ከሆነ ግለሰቡ በመጨረሻው ቀን በመገምገም ለታቀደው ቦታ ተስማሚ ነው ወይስ አይደለም የሚለውን ውሣኔ ለማስተላለፍ የመጨረሻ ቀን የሥራ አፈፃፀም ውጤት ጭምር ታሳቢ መደረግ ያለበት በመሆኑ በ46ኛው ቀን የስንብት ደብዳቤ መፃፉ የሕጉን ይዘትና መንፈስ የሚቃረን አይደለም፡፡ ስለሆነም የሥር ፍ/ቤቶች ግራ ቀኙ እያከራከረ ያለውን ጉዳይ በአግባቡ ሳያገናዝቡ የሙከራ ጊዜ ከ45 ቀናት መብለጥ የለበትም የሚለውን የሕጉ ይዘት ከአጠቃላይ የሕጉ ዓላማና ግብ ሳያገናዝቡ መወሰናቸው በአግባቡ አይደለም ብለናል፡፡ በዚህ ሁሉ ምክንያት የሥር ፍ/ቤቶች የአመልካች ድርጊት ሕገወጥ ነው በማለት መወሰናቸው መሠረታዊ የሕግ አተረጓጐም ስህተት ፈጽመዋል፡፡ በመሆኑም ተከታዩን ወስነናል፡፡

     ት ዕ ዛ ዝ

    1. የፌዴራል የመ/ደ/ፍ/ቤት በኮ.መ.ቁ.85529 በ18/07/2006 ዓ.ም እንዲሁም የፌ/ከ/ፍ/ቤት በኮ.መ.ቁ. 139947 በ19/07/2006 የሰጡት ፍርድ እና ትዕዛዝ ተሽሯል፡፡

    2.  አመልካች ተጠሪ ያለማስጠንቀቂያ ማሰናበቱ በአግባቡ ነው ብለናል፡፡

    3. ለዚህ ወጪና ኪሳራ ግራ ቀኙ የየራሳቸው ይቻሉ፡፡ መዝገቡ ተዘግቷል፡፡ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ፡፡

     

    ብ/ግ                                     የማይነበብ   የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

  • በገጠር መሬት ላይ የሚኖረው መብት የመጠቀም መብት ሲሆን ይህንን መብት ለ3ኛ ወገን /ለሌላ/ ሰው ለረጅም ጊዜ ሰጥቶ ተጠቃሚነቱ የተቋረጠበት ባለመብት መልሶ መጠየቅ የማይችል ስለመሆኑ፣ የኦሮሚያ ክልለ የገጠር መሬት አጠቃቀም አዋጅ ቁጥር 130/1997 አንቀፅ 9(5)

     

    የሰ/መ/ቁ. 113973

    ቀን 21/04/2008 ዓ/ም

    ዳኞች፡- ተሻገር ገ/ስላሴ

     

    ሙስጠፋ አህመድ ተፈሪ ገብሩ

    ሸምሱ ሲርጋጋ ፈይሳ ወርቁ

    አመልካች፡- ወ/ሮ ጠጅቱ ኡርጋ - ቀረቡ ተጠሪ፡- አቶ ገመዳ ሬባ - አልቀረቡም

    መዝገቡን መርምረን ተከታዩን ፍርድ ሰጥተናል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ የባልና ሚስት ንብረት ክርክርን የሚመለከት ሲሆን ክርክሩ የጀመረው በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ሜታ ሮቢ ወ/ፍ/ቤት ነው፡፡ አመልካች በዚህ ወረዳ ፍ/ቤት ባለቤታቸው በነበሩት አቶ አሰፋ ገመዳ ላይ ክስ የመሰረቱት ኤዴ ከተባለ አከባቢ የሚገኝ ሁለት የበሬ መዋያ  መሬት እና ሰምንተኛ ተብሎ ከሚጠራው አካባቢ ግማሸ የበሬ መዋያ ይዞታ መሬታችንን እኩል እንደንካፈል ይወሰንልኝ የሚል ሲሆን ተከሳሽ በበኩላቸው የተጠቀሰው ይዞታ መሬት የጋራ ይዞታችን አይደለም ሊካፈል አይገባም ብለዋል፡፡ የአሁኑ ተጠሪ ወደ ክርክሩ ጣልቃ ገብተው ግራ ቀኙ የሚከረከሩበት መሬት የግል ይዞታዬ ነው በስሜ ተለከቶ የሚገኝ እና በስሜ የምግብርበት ነው ከሳሽና ተከሳሽ በዚህ መሬት ላይ አንዳችም መብት የላቸውም ብለው ተከራካረዋል፡፡

     

    ከሳሽ (የአሁኑ አመልካች) በበኩላቸው ለክርክር ምክንያት የሆነውን መሬት በ1994 ዓ/ም ከተከሳሽ ጋር ስንጋባ የተከሳሽ አባት የሆኑት ጣልቃ ገብ ሰጥተውን በጋብቻ ውላችን ላይም ተጠቅሶ ከ1994 ዓ/ም ጀምሮ በይዞታችን ስር ሆኖ ስንጠቀምበት ቆይተናል፡፡ ሰሞንኛ ተብሎ ከሚታወቀው አካባቢ ባለን ይዞታ ላይ ቤት ያለን ሲሆን በመ/ቁ. 15710 እና 14792 በሆኑ መዝገቦች በዚህ ቤት ውስጥ ሆኜ ልጆችን እንደሳደግ ፍ/ቤት አዞልኛል የጣልቃ ገብ አቤቱታ ውድቅ ይደረግልኝ ብለው ተከራከረዋል፡፡


    ፍ/ቤቱ የግራ ቀኙ ምስክሮችን ሰምቶ ክርክራቸው ከቀረበው ማስረጃ ጋር በማገናዘብ መርምሮ ለክርክር ምክንያት የሆነው መሬት በጋብቻ ውሉ ላይ የተመዘገበ እና ከሳሽና ተከሳሽ ይዘውት ሲጠቀሙበት የቆዩ በመሆኑ ጣልቃ ገብ የመሬቱ ይዞታ በስማቸው የሚገኝና ግብር በስማቸው የሚገብርብት ቢሆንም ከሳሽና ተከሳሽ ይዘው የሚጠቀሙበትን መሬት ጣልቃ ገብ መጠየቅ አይችሉም ለክርክር ምክንያት የሆነውን መሬት ከሳሽና ተከሳሽ እኩል ይካፈሉ በማለት ወስኗል፡፡

     

    ጣልቃ ገብ (የአሁኑ ተጠሪ) በዚህ ውሳኔ ላይ ቅሬታቸውን ለምዕራብ ሸዋ ዞን ከፍ/ፍ/ቤት አቅርበዋል፡፡ ፍ/ቤቱ ግራ ቀኙን አከራክሮ ለክርክር ምክንያት የሆነውን መሬት የስር ከሳሽና ተከሳሽ ሲጋቡ ይ/ባይ (የስር ጣልቃ ገብ) የሰጠው መሆኑን የስር ከሳሽ ምስክሮች ያስረዳ ቢሆንም መሬት የሚሰጠው በቃል ሳይሆን በጽሁፍ ማስረጃ ሆኖ ስልጣን ባለው አካል መመዝገብ እንዳለበት ከገጠር መሬት አዋጅና ከፍ/ብ/ህ/ቁ. 1723 መረዳት ይቻላል፡፡ መሬቱ የጣልቃ ገብ መሆኑ ተረጋግጧል፡፡ ለይግባኝ መልስ ሰጭ ከባለቤታቸው ጋር በህጋዊ  መንገድ የተሰጠ ስለመሆኑ ሳይረጋገጥ የጋብቻ ውሉም ለወደፊቱ ከአባታችን ላይ የምናገኛው መሬት የሚል በመሆኑ እና ከዚያ ወዲህም የተደረገ ስጦታ የሌለ በመሆኑ ክርክር ያስነሳው መሬት የይግባኝ ባይ (የስር ጣልቃ ገብ) ይዞታ ነው በማለት የስር ፍ/ቤትን ውሳኔ በመሻር ወስኗል፡፡

     

    የአሁኑ አመልካች በዚህ ውሳኔ ላይ ቅሬታቸውን ለኦሮሚያ ክልል ጠ/ፍ/ቤት በይግባኝ አቅርበው ፍ/ቤቱ ግራ ቀኙን አከራክሮ በሰጠው ውሳኔ ክርክር ያስነሳውን መሬት ይ/ባይ ከስር ተከሳሽ ጋር በሚጋቡበት ጊዜ በጋብቻ ውላቸው ላይ የተገለጸ እና ከዚያ ወዲህ ይ/ባይ ከባለቤታቸው ጋር እየተጠቀሙበት የቆዩ መሆኑ ተመስከሯል የቀበሌው አስተዳደር ለወረዳ ፍ/ቤት በጻፈው ሪፖርት ላይም መሬቱን ተጋቢዎቹ በጋራ ሲጠቀሙበት የቆዩ መሆኑን ገልጿል፡፡ የመሬት እና አካባቢ ጥበቃ ጽ/ቤት ለወ/ፍ/ቤት በጻፈው ደብዳቤ መሬቱ በመልስ ሰጭ (በስር ጣልቃ ገብ) ስም የተለካ መሆኑን ነገር ግን እየተጠቀሙበት ያሉት ተጋቢዎቹ መሆናቸውን ገልጿል፡፡ መሬቱ በጋብቻ ውል ላይ የተጠቀሰ መሆኑን ግራ ቀኙ አልተካካዱም ከዚያ ወዲህም ተጋቢዎቹ ሲጠቀሙበት የቆዩ መሆኑ በማስረጃ ተረጋግጧል፡፡ መ/ሰጭ በስሙ በመመዝገቡ ብቻ እስካሁን ያልተጠቀሙበትን መሬት በስሜ ተለክቷል በማለት ያቀረቡት መከራከሪያ ተቀባይነት የለውም፡፡ ቤት የሰሩበትን መሬት ይ/ባይ ቀደም ሲል እንደኖርበት በፍ/ቤት ተውስኖልኛል ብለው ያቀረቡትን መከራካሪያ መ/ሰጭ አላስተባበሉም ክርክር ያስናሳውን መሬት ይ/ባይ ከባለቤታቸው ጋር ሊካፈሉ ይገባል በማለት የከፍ/ፍ/ቤቱን ውሳኔ በመሻር ወስኗል፡፡ የአሁኑ ተጠሪ በዚህ ውሳኔ ላይ ያላቸውን ቅሬታ ለማስረም ለኦሮሚያ ክልል ጠ/ፍ/ቤት ሰበር ችሎት አቤቱታ አቅርበዋል፡፡ ሰበር ችሎቱም የግራ ቀኙን ክርክር እና የስር ፍ/ቤቶችን ውሳኔ በማገናዘብ መርምሮ ለክርክሩ ምክንያት የሆነውን መሬት ተጠሪዋ ከባለቤቷ አባት (ከአመልካች) ያገኙትና ለ9 ዓመት ሲጠቀሙበት የቆዩ መሆኑ  በምስክሮች  ተረጋግጧል፡፡  ይሁን  እንጂ  የገጠር  መሬት  አጠቃቀም  ደንብ    እና


    ፍ/ብ/ህ/ቁ.1723 መሰረት የገጠር መሬት ስጦታ በጽሁፍ መሆንና መመዝገበ አለበት ተጠሪ መሬቱን በጋብቻ ወቅት በስጦታ ያገኙ ስለመሆኑ አግባብነት ያለው ማስረጃ አቅርበው ያላረጋገጡ በመሆኑ ክርክር ያስነሳው መሬት የአመልካች (የስር ጣ/ገብ) ይዞታ ነው በማለት ወረዳ እና የጠቅላይ ፍ/ቤት ይ/ሰሚ ችሎት ውሳኔን በመሻር ወስኗል፡፡

     

    አመልካች በዚህ ውሳኔ ላይ ያላቸውን ቅሬታ በመዘርዘር እንዲታረምላቸውን አቤቱታ አቅርበዋል፡፡ አቤቱታው ተመርምሮ አመልካች አከራካሪውን 2 ጥማድ እርሻ መሬት ከ1994 ዓ/ም ጀምሮ ከስር ተከሳሽ ጋር እስከተፋቱበት ጊዜ 2003 ዓ/ም ድረስ በጋራ ሲጠቀሙ መቆየታቸው ተረጋግጦ እያለ መሬቱን ልትካፈል አይገባም ተብሎ ጥያቄዋ በክልሉ ሰበር ችሎት  ተቀባይነት የማጣቱን አግባብነት ለመመርመር ተጠሪ መልስ እንዲሰጡበት ተደርጓል፡፡ ግራ ቀኙ በጽሁፍ ክርክራቸውን አቅርበዋል፡፡

     

    የግራ ቀኙን ክርክር ለሰበር አቤቱታ መነሻ ከሆነው የስር ፍ/ቤት ውሳኔ ጋር በማገናዘብ አቤቱታው እንዲመረመር ከተያዝው ጭብጥ አንጻር የስር ፍ/ቤት ውሳኔ ላይ መሰረታዊ የሆነ የህግ ስህተት የተፈጸመ መሆን አለመሆኑን መርምረናል፡፡

     

    እንደመረመርነውም ክርክር ያስነሳውን መሬት አመልካች የስር ተከሳሽ ከነበሩበት  ባለቤታቸው ጋር በ1994 ዓ/ም ሲጋቡ የባለቤታቸው አባት የሆኑት ተጠሪ ሰጥተዋቸው በጋብቻ ውላቸው ላይም ተጠቅሶ ጋብቻ ከመሰረቱበት ከ1994 ዓ/ም ጀምሮ ጋብቻው በፍቺ እስከፈረሰበት 2003 ዓ/ም ድረስ ተጋቢዎቹ በጋራ ሲጠቀሙበት የነበረ መሆኑ ፍሬ ነገርን ለማጣራት እና ማስረጃ ለመመዘን በህግ ስልጣን በተሰጣቸው የስር ፍ/ቤቶች ውሳኔ ላይ ተረጋግጧል፡፡ ክርክር ያስነሳው መሬት ተመዝግቦ የሚገኘው እና ግብር የሚከፈልበት በተጠሪው ስም ቢሆንም ይህን መሬት ለአመልካቹ እና ለባለቤታቸው ሰጡ ከተባለበት ከ1994 ዓ/ም ጀምሮ እስከ 2003 ዓ/ም ድረስ ተጠሪ ተጠቅመውበት የማያውቁ መሆኑና ሲጠቀሙበት የቆዩት አመልካች ከባለቤታቸው (የስር ተከሳሽ) ጋር መሆኑ በስር ፍ/ቤቶች ተረጋግጧል፡፡ ማንኛውም አርሶአደር በመሬት ይዞታው የመጠቀም መብቱን በዚያ መሬት ገቢ ለሚተዳደሩ ወይም ሌላ ገቢ ለሌላቸው የቤተሰብ አባላት ወይም መሬት ለሌላቸው ልጆቹ በስጦታ ማስተላለፍ እንደሚችል በኦሮሚያ የገጠር መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም አዋጅ ቁጥር 130/1997 አንቀጽ 9(5) ላይ ተመልክቷል፡፡

     

    በተያዘው ጉዳይ በጽሁፍ የተደረጉ የስጦታ ውል ባይኖርም ለክርክር ምክንያት የሆነውን መሬት በተጠሪ ስም ተመዝግቦ ያለ መሆኑን ነገር ግን እየተጠቀሙበት ያሉት አመልካች  እና ባለቤታቸው መሆኑን ገልጻ ለሜታ ሮቢ ወ/ፍ/ቤት መልስ የሰጠ ሲሆን የቀበሌው አስተዳደርም ለስር ፍ/ቤት በጻፈው ደብዳቤ ለክርክር ምክንያት በሆነው መሬት አመልካች ከባለቤታቸው ጋር ሲጠቀሙበት የቆዩ መሆኑን ገልጿል፡፡ ስር ፍ/ቤት ቀርበው የተሰሙ የአመልካች ምስክሮችም


    መሬቱን ተጠሪ ሰጥተዋቸው አመልካችና ባለቤታቸው ሲጠቀሙበት የቆዩ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ተጠሪ ለከርክር ምክንያት በሆነው መሬት ላይ የነበራቸውን የመጠቀም መብት ልጃቸው የሆነው የአመልካች ባለቤት ከአመልካች ጋር ጋብቻ ሲፈጽሙ በዚህ መሬት እንዲተዳደሩ በአባትነታቸው አስልፈው ሰጥተው ከ1994 ዓ/ም ጀምሮ አመልካች ከባለቤታቸው ጋር በፍቺ ውሳኔ እስከተለያዩበት 2003 ዓ/ም ድረስ ሲጠቀሙበት የቆዩ በመሆኑ በመሬቱ የነበራቸውን የተጠቃሚነት መብት ካስተላለፉ በኋላ መሬቱ ተመዝግቦ የሚገኘው እና ግብርም የሚከፈለው በተጠሪው ስም ብቻ በመሆኑ መሬቱ ለተጠሪ ሊመለስላቸው ይገባል ማለት የሚቻል አይደለም፡፡ ለክርክር ምክንያት የሆነውን መሬት እንደቤተሰብ በእኔ ስር ሆነው አመልካች ባለቤቷ ተጠቀሙ እንጂ በግላቸው ስር ሆኖ አንድም ቀን አልተጠቀሙበትም በማለት ተጠሪ ለዚህ ችሎት ባቀረቡት መልስ የተጠቀሱ ቢሆንም ይህን ስር ፍ/ቤት በነበረው ክርከራቸው አላስረዳም፡፡ በስር ፍ/ቤቶች ውሳኔ ላይ የተረጋገጠው መሬቱን ተጠሪ ለአመልካች ከሰጡ በኃላ ሲጠቀሙበት የቆዩት አመልካች እና ባለቤታቸው መሆናቸውን ነው፡፡ በገጠር መሬት ላይ የሚኖረው መብት የመጠቀም መብት ሲሆን ተጠሪ ይህን መብታቸውን ለአመልካችና ባለቤታቸው አሳልፈው ሰጥተው ለረጀም ጊዜ በዚህ መሬት ላይ ተጠቃሚነታቸው በተቋረጠበት ሁኔታ የምዕራብ ሸዋ ዞን ከፍ/ፍ/ቤት እና የኦሮሚያ ክልል ጠ/ፍ/ቤት ሰበር ችሎት በጽሁፍ የተደረገ ስጦታ ውል አለመኖሩን ብቻ መሰረት በማድረግ በክርክሩ ከተረጋገጠው ፍሬ ነገር ውጪ የሰጡት ውሳኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈጸመበት ሆነ በመገኘቱ የሚከተለው ውሳኔ ተሰጥቷል፡፡

     

     ው ሳ ኔ

     

    1. የኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ከፍ/ፍ/ቤት በመ/ቁ. 55478 በቀን 3/03/2006 ዓ/ም በዋለ ችሎት የሰጠው ውሳኔ እና የኦሮሚያ ጠ/ፍ/ቤት ሰበር ችሎት በመ/ቁ.186326 በቀን 26/08/2007 ዓ/ም በዋለ ችሎት የሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 348(1) መሰረት ተሽሯል፡፡

    2. በኦሮሚያ  ክልል   ምዕራብ   ሸዋ  ዞን  ሜታ   ሮቤ   //ቤት በመ/ቁ.15357   በቀን

    10/01/2006 ዓ/ም በዋለ ችሎት የሰጠው ውሳኔ እና የኦሮሚያ ክልል ጠ/ፍ/ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በመ/ቁ. 170790 በቀን 8/11/2006 ዓ/ም በዋለ ችሎት የሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ስ/ስ/ቁ.348(1) መሰረት ጸንቷል፡፡

    3. ለክርክሩ ምክንያት የሆነው መሬት የአመልካች እና ባለቤታቸው የነበሩተ የስር ተከሳሽ የጋራ ይዘት ነው ብለናል፡፡

     

    4. ግራ ቀኙ በዚህ ችሎት ላደረጉት ክርክር ያወጡትን ወጪ የየራሳቸውን ይቻሉ ብለናል፡፡ መዝገቡ ዕልባት ያገኘ በመሆኑ ወደ መ/ቤት ይመለሰ፡፡የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት

  • በስራ ክርክር የተከራካሪ ወገኖች ማንነት የፍርድ ቤቶችን ስልጣን (የክልል ወይም የፌዴራል)ብሎ ለመወሰን እንደወሳኝ  መለኪያ ሊወሰድ የማይገባ ስለመሆኑ፤

     

    የአሰሪው እርምጃ ህገ ወጥነት የተረጋገጠ እንደሆነ  የክፍያ መጠኑ ሊሰላ የሚገባው አዋጁ ባስቀመጠው ስሌትና በማስረጃ በተረጋገጠ የደመወዝ መጠን መሆን ያለበት ስለመሆኑ፣

     

    አዋጅቁጥር377/1996አንቀፅ 35(1(ለ))፣39(1(ለ))፣40(1)(2)፣43(4(ሀ)፣68፣71

    የሰ/መ/ቁጥር 95638

     

    መስከረም 29 ቀን 2007 ዓ/ም

     

    ዳኞች፡-አልማው ወሌ ሡልጣን አባተማም መኮንን ገ/ሕይወት ሙስጠፋ አህመድ ተፈሪ ገብሩ

    አመልካች፡-ኢስት ሲሜንት አክሲዩን ማህበር - ጠበቃ ዓለሙ ደነቀው - ቀረቡ ተጠሪ፡-አቶ ዘላለም ታደሰ  - ጠበቃ ገናናው ተሾመ ቀረቡ

    መዝገቡ ተመርምሮ ተከታዩ ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     

     ፍ  ር ድ

     

    ጉዳዩ በአዋጅ ቁጥር 377/1996 መሰረት የቀረበውን የግል የስራ ክርክርን የሚመለከት ሲሆን ክርክሩ የተጀመረበት ፍርድ ቤት የሂደቡ አቦቴ ወረዳ ፍርድ ቤት ነው፡፡በዚህ ፍርድ ቤት ከሳሽ የአሁኑ ተጠሪ ሁኖ የክሱ ይዘትም፡-በተጠሪ ድርጅት በአስተዳደር ኃላፊነት እና ጉዳይ አስፈፃሚነት አምስት አመት ከዘጠኝ ወር ብር 6,410.90 በወር እየተከፈላቸው ማገልገላቸውንና የስራ ውሉ ከሕግ ውጪ መቋረጡን ገልጸው ልዩ ልዩ ክፍያዎች እንዲከፈላቸው ይወሰን ዘንድ ዳኝነት መጠየቃቸውን የሚያሳይ ነው፡፡የአሁኑ አመልካች ተከሳሽ የነበረ ቢሆንም መጥሪያ ደርሶታል፣ግን አልቀረበም ተብሎ በሌለበት ጉዳዩእንዲታይ ተደርጓል፡፡የሥር ፍርድ ቤትም ጉዳዩን መርምሮ የአሁኑ አመልካች ለክሱ ኃላፊ ነው ተብሎ ለከሳሽ ብር 277,294.00 ( ሁለት መቶ ሰባ ሰባት ሺህ ሁለት መቶ ዘጠና አራት) ብር እንዲከፈል ወሰኗል፡፡

     

    የአሁኑ አመልካች በሌለሁበት ታይቶ የተወሰነው ውሳኔ ተነስቶ ባለሁበት ይታይልኝ በማለት ጥያቄ ያቀረበ ሲሆን ከዚሁ ጋር በተጨማሪ ከሳሹ የአሰሪ ወገን ስለሆነ በአሰሪና ሰራተኛ ጉዳይ አዋጅ ሊዳኙ አይገባም፣በአዋጁ መሰረት ሊዳኝ ይገባል ከተባለም የስራ ውሉ የተቋረጠው በሕጋዊ መንገድ ስለሆነ ሊፈጸም የሚገባ ክፍያ የለም፣ክፍያ ሊፈፀም ይገባል ከተባለም ከሳሽ ደሞዜ ነው ብሎ ያቀረበው መጠን ትክክል አይደለም፣በትክክል ደመወዙ ላይ ተመስርቶ ሊከፈል የሚገባውም የደመወዙን

         ኛውን ያህል ብቻ ነው ብሎ ተከራክሯል፡፡የስር ፍርድ ቤት በአመልካች በሌለሁበት ታይቶ

     

    የተወሰነው ውሳኔ ይነሳልኝ ጥያቄ ላይ የአሁኑ ተጠሪ (የስር ከሳሽ) አስተያየት እንዲሰጡበት  ያደረገ

    ሲሆን ተጠሪው በሰጡት አስተያየትም ለአመልካች መጥሪያውን ባቀረቡት የቃለ መሓላ አቤቱታ የተዘረዘሩ ምስክሮች የሚያረጋገጡ መሆኑን እና የተለያዩ ክፍያዎች እንዲከፈሏቸው የተወሰነውም በአግባቡ ነው በማለት ተከራክረዋል፡፡የወረዳው ፍርድ ቤት ጉዳዩን መርምሮ አመልካች ጉዳዩ ባለሁበት ይታይልኝ በማለት ያቀረበው ጥያቄ ተቀባይነት የለውም፣በቃለ መሐላ ተረጋግጧል በማለት ውሳኔ ሰጠ ፡፡ በዚህ ውሳኔ የአሁኑ አመልካች ቅር በመሰኘት ይግባኙን ለሰሜን ሸዋ ዞን ከፍተኛ


    ፍርድ ቤት አቅርቦ ተቀባይነት አላገኘም፡፡ከዚህም በኋላ አመልካች የሰበር አቤቱታውን ለክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት አቅርቦ ችሎቱ ግራ ቀኙን ከአከራከረ በኋላ ጉዳዩን መርምሮ መጥሪያው በሕጉ መሰረት ለአሁኑ አመልካች የደረሰው መሆንያለመሆኑን የግራ ቀኙን ምስክሮችእንዲሰሙና ተገቢው እንዲወሰን በማለት ጉዳዩን ለወረዳው ፍርድ ቤት መልሶታል፡፡ በዚህ አግባብ ጉዳዩ የተመለሰለት የወረዳው ፍርድ ቤትም በ18/03/2004 ዓ/ም የአሁኑ ተጠሪ ለወረዳው ፍርድ ቤት ባቀረቡት ቃለ መሃላ ላይ ያሉትን ምስክሮችን ከሰማ በኋላ የአሁኑ አመልካች ደግሞ የቀረቡት ምስክሮች ይበቁናል ስላለ ፍርድ ቤቱ ጉዳዩን መርምሮ መጥሪያው ለአመልካች መድረሱ ተረጋግጧል በማለት በጉዳዩ ላይ የሰጠውን ውሳኔ አይነሳም ሲል በ24/05/2005 ዓ/ም በዋለው ችሎት ወሰኗል፡፡በዚህ ውሳኔ ላይ ለሰሜን ሸዋ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት የአሁኑ አመልካች ይግባኙን አቅርቦ ፍርድ ቤቱም ግራ ቀኙን ከአከራከረ በኋላ ጉዳዩን መርምሮ መሰማት የሚገባቸው ምስክሮች በ18/03/2004 ዓ/ም በተጻፈ የተጠሪ ቃለ መሃላ ላይ ያሉት ምስክሮች ሳይሆኑ በ26/03/2004 ዓ/ም በተጻፈ ቃለ መሃላ ላይ ያሉት ምስክሮች ናቸው በማለት በክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት መመሪያ መሰረት የወረዳው ፍርድ ቤት አልፈጸመም ሲል በዚህ ረገድ የተሰጠውን ውሳኔ በ28/06/2005 ዓ/ም በዋለው ችሎት ሽሮ በ26/03/2004 ዓ/ም በተጻፈ ቃለ መሃላ ላይ ያሉት ምስክሮች እንዲሰሙ ሲል ጉዳዩን ለወረዳው ፍርድ ቤት መልሶ ልኮለታል፡፡.የአሁኑ ተጠሪ በዚህ የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ውሳኔ ቅር በመሰኘት የሰበር አቤቱታውን ለክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት አቅርበው ችሎቱም የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኋላ ችሎቱ መሰማት የሚገባቸው በ18/03/2004 ዓ/ም በተፃፈ ቃለ መሃላ ላይ የተዘረዘሩት ምስክሮች ናቸው? ወይስ በ26/03/2004 ዓ/ም በተጻፈ ቃለ መሃላ ላይ የተገለፁት ምስክሮች ናቸው? የሚለውን ጭብጥ ይዞ ጉዳዩን በመመርመር የወረዳው ፍርድ ቤት በ12/03/2004 ዓ/ም የሰጠው ትዕዛዝ የተከሳሽን መልስ ለመቀበል ብሎ ለ18/03/2004 ዓ/ም መቅጠሩን፣በዚህ ቀን ከሳሽ ለተከሳሽ መጥሪያ ማድረሱን በመግለፅ በቃለ መሃላ የተከሳሽ መልስ የመስጠት መብት መታለፉን፣በ26/03/2004 ዓ/ም ደግሞ ከሳሽ ደመወዝ ሲበላበት የነበረ ፔሮል ለተከሳሽ ድርጅት እንዲያቀርብ የታዘዘ መሆኑን ከመዝገቡ መረዳቱን ጠቅሶ መሰማት ያለባቸው ምስክሮች በ18/03/2004 ዓ/ም በተፃፈው ቃለ መሃላ ያሉት ምስክሮች እንጂ በ26/04/2004 ዓ/ም በተጻፈ ቃለ መሃላ የተገለፁ ምስክሮች አይደሉም በማለት የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በዚህ ረገድ በ20/01/2006 ዓ/ም በዋለው ችሎት የተሠጠውን ውሳኔ ሽሮ የወረዳ ፍ/ቤት ውሳኔን አጽንቷል፡፡

     

    የአሁኑ የሰበር አቤቱታ የቀረበውም በዚሁ የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ሲሆን የአመልካች የሠበር አቤቱታ ቅሬታ መሰረታዊ ነጥቦችም፡-የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ጉዳዩን ለወረዳው ፍርድ ቤት የመለሰው በ26/03/2004 ዓ/ም በተፃፈ ቃለ መሃላ የተገለፁትን ምስክሮች እንዲሰሙ ሁኖ እያለ መልሶ መሰማት ያለባቸው በ18/03/2004 ዓ/ም በተጻፈ ቃለ መሃላ የተገለፁትን ምስክሮች ናቸው ማለቱ ተገቢነት የለውም፣የተጠሪው ደመወዝ ተጠሪው እንደገለፀው ብር 6,410.00 ሳይሆን ብር 3,230.70 ብቻ መሆኑ ከተረጋገጠ በኋላ የስራ ስንብት ክፍያ ብር 47,383.60 እንዲሆን መወሰኑ ያላግባብ ሲሆን የስራ ስንብት ክፍያው ብር 8,348.00 ብቻ ነው፣የካሳ ክፍያ ብር 19,384.00 መሆን ሲገባው ብር 25,849.60 መሆኑ ያላግባብ ነው፣የሳምንት የእረፍት ክፍያ ሊተመን በማይችል ስሌት ብር 188,784.57 ሁኗል፣የአምስት አመት በዓል በማለት ብር 16,357.00 እንዲከፍል መወሰኑ ያላግባብ ነው፣የአመልካች እርምጃ ሕገ ወጥ ነው የሚባል ከሆነም ሊከፈሉ የሚገባቸው ክፍያዎች፤- የአገልግሎት ክፍያ ብር 8,384.30፣የሁለት ወር ማስጠንቀቂያ ብር 6,461.40፣የካሳ ክፍያ ብር 19,384.20 በድምሩ ብር 34,229.90 እንጂ ብር 277,294.00 እንዲከፈል መወሰኑ ያለአግባብ ነው በማለት በዚህ ችሎት እንዲወሰን የጠየቀው ዳኝነትም የአመልካች የመከራከር መብቱ እንዲጠበቅለት፣ይህ  የሚታለፍ  ከሆነ  በአዋጁ  መሰረት  ክፍያዎቹ  መወሰን  አለባቸው  የሚል


    ነው፡፡የሠበር አቤቱታው ተመርምሮም በዚህ ችሎት ጉዳዩ እንዲታይ የተደረገው ከአመልካች ማንነት አንፃር ይህንኑ ጉዳይ የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ተቀብሎ ማየቱ ተገቢ መሆን ያለመሆኑን ለመመርመር ተብሎ ሲሆን ተጠሪ ቀርበው በሰጡት መልስም ጉዳዩ የአሰሪና ሰራተኛ ስለሆነ አዋጁ ከወጣበት ጊዜ አንጻር በክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት የማይታይበት ምክንያት የለም፣ጉዳዩ የማስረጃ ምዘና ጉዳይ ስለሆነ በዚህ ችሎት የሚታይ አይደለም፣በሌለበት በታየ ጉዳይ በስንብቱ እና በደመወዝ መጠኑ ሊከራከርአይችልም፣ተጠሪ የአሰሪ የአስተዳደር አካል ያለመሆናቸው በማስረጃ ተረጋግጧል፣በቃለ መሃላ ጉዳይ ላይ ማስተባበያ ማስረጃ አላቀረበም፣የተጠሪ ምስክሮች የእኔም ምስክሮች ናቸው በማለት መግለፁን የስር ፍርድ ቤት መዝገብ ያሳያል፣የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ራሱ የሰጠውን ውሳኔ አልሻረም፣በ26/03/04 በተጻፈ ቃለ መሃላ የተገለጹት ምስክሮች የሚሰሙበት ምክንያት የለም፣በዚህ ቀን የቀረበው ቃለ መሃላ የስር ተከሳሽ ከሳሽ የሚበላውን ደመወዝ መዝገቡን እንዲያቀርብ በ22/03/2004 ዓ/ም በዋለው ችሎት ፍርድ ቤቱ አዞት ስለነበር ተከሳሹ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ አልፈፀመም፣የፍርድ ቤቱን መጥሪያአልወስድም ማለቱን ለማረጋጋጥ ነው፣ በማለት ዘርዝሮ የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት በመ/ቁጥር 163369 በ20/01/2006 ዓ/ም የሰጠው ውሳኔ እንዲፀናላቸው ዳኝነት መጠየቃቸውን የሚያሳይ ነው፡፡የአሁኑ አመልካችም ያስቀርባል የተባለበትን ነጥብ በመደገፍና በሰበር አቤቱታው ላይ የተዘረዘሩትን ነጥቦችን በማጠናከር የመልስ መልሱን ሰጥቷል፡፡

     

    ከዚህም በኋላ ይህ ችሎት ጉዳዩን መርምሮ አመልካች መጀመሪያ በሌለበት ታይቶ የተሰጠው ውሳኔ እንዲነሳለት ለወረዳው ፍርድ ቤት አመልክቶ ተቀባይነት ካጣ በኋላ ለዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኙን ሲያቀርብ በፍሬ ጉዳዩ ላይ ስርዓቱን ጠብቆ እስከ ክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት መከራከሩን ለማወቅ ይረዳ ዘንድ የወረዳው ፍርድ ቤት መጀመሪያ በፍሬ ጉዳዩ ላይ የሰጠው ውሳኔ ግልባጭ፣አመልካች ለዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት እና ለክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ያቀረበው የይግባኝ እና የሰበር አቤቱታ ግልባጮችን እንዲያያይዝ ትዕዛዝ ሰጥቶ አመልካችአሉኝ ያላቸውን ውሳኔዎችን አያይዟል፡፡

     

    የጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለመልኩ ከላይ የተገለጸው ሲሆን ይህ ችሎትም የግራ ቀኙን ክርክርና ለሰበር አቤቱታው መነሻ የሆነውን ውሳኔ አግባብነት ካላቸው ድንጋጌዎች ጋር በማገናዘብ ጉዳዩን በሚከተለው መልኩመርምሮታል፡፡እንደመረመረውም የዚህን ችሎት ምላሽ የሚያስፈልጋቸው አበይት ነጥቦች፡-

     

    1.  የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ጉዳዩን ለማየት ስልጣን አለው ወይስ የለም?

    2.  የአመልካች የመከራከር መብት የታለፈው በሕጉ አግባብ ነው ወይስ አይደለም?

    3. የአመልካች እርምጃ ሕገ ወጥ ነው ተብሎ የተለያዩ ክፍያዎችን ለተጠሪ እንዲከፍል በተሰጠው ውሳኔ መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት አለ ለማለት ይቻላል ወይስ አይቻልም?

     የ መጀ መሪያ ውን ጭ ብጥበተመለከተ፡-በመሰረቱ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ በፌዴራል መንግስትና በክልሎች መዋቀሩን መሰረት በማድረግ የዳኝነቱም ሥልጣን በፌዴራል መንግስቱ እና በክልል መንግስታት መካከል እንደተከፋፈለ በህገ መንግስቱ አንቀጽ 5ዐ እና 51 ሥር ተመለክቷል፡፡በኢ.ፌ.ዲ.ሪሕገ መንግስት በአንቀጽ 8ዐ “የፍ/ቤቶች ጣምራነትና ሥልጣን” በሚል ርዕስ በፌዴራል ጉዳዩች ላይ የበላይና የመጨረሻየዳኝነት ሥልጣኑ በፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት፤በክልል ጉዳዮች ላይ በክልሉ መንግስት ጠቅላይ ፍ/ቤት ሥልጣኑ የተደነገገ ሲሆን የክልል ፍ/ቤቶች በህገ- መንግስቱ በተሰጣቸው የውክልና ሥልጣን መሠረት ካልሆነ በቀር የፌዴራልን ጉዳይ ለማየት፤እንዲሁም የፌዴራል ፍ/ቤቶች የክልልን ጉዳይ ለማስተናገድ የሚያስችል  ሥልጣን የሌላቸው  መሆኑን  በዚሁ  ድንጋጌ  ስር  የተቀመጡት  ንዑስ  ድንጋጌዎች  ይዘትና    መንፈስ


    ያሳያል፡፡አንድ ጉዳይ የፌዴራል ነው? ወይስ የክልል? የሚለውን ለመለየትም መሰረቱ የአዋጅ ቁጥር 25/88 ሲሆን፤በዚሁ ህግ አንቀጽ 5 ሥር በተመለከቱት ጉዳዮች ላይ ብቸኛ ሥልጣን ያላቸው የፌዴራል ፍ/ቤቶች ናቸው፡፡ በእነዚህ ጉዳዮች ላይ የክልል ፍ/ቤቶችስልጣን የሚኖራቸው በህገመንግስቱ በተሰጣቸው የውክልና ሥልጣን አግባብ ብቻ ነው፡፡ይህ በግልፅ የሚያሳየው በአዋጅ ቁጥር 25/1988 አንቀጽ 5 መሰረት የፍርድ ቤቶች ስልጣን በጉዳዩ ባለቤትነት (Subject matter) የሥልጣን ክፍፍል እንደተጠበቀ ሆኖ ክሱም መቅረብ ያለበት ጉዳዩን አይቶ ለመወሰን የሥረ-ነገር ሥልጣን ላለው ፍ/ቤት ስለመሆኑ ነው፡፡የፌደራል ፍ/ቤቶችን ለማቋቋም በወጣው አዋጅ ቁጥር 25/88 አንቀጽ 8፣11፣14 እና 15 ድንጋጌዎች ይዘትና መንፈስ ደግሞ አንዳንድ ጉዳዮች ሊያስነሱ በሚችሉት የክርክር ባህርይ ምክንያት ለተወሰኑ ፍ/ቤቶች እንዲቀርቡ በህግ ተለይተው ከተመለከቱት በቀር የሥረ-ነገር ሥልጣን የተደለደለው በክሱ በተመለከተው የገንዘብ ወይም የንብረት ግምት መነሻ እንደሆነ ከፍ/ብ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ 14 እና 15 ስር ከተመለከቱት ድንጋጌች ጣምራ ንባብ እና የክልል መንግስታት ፍርድ ቤቶች ማቋቋሚያ ሕጎች ያስረዳሉ፡፡ይህ በእንዲህ እንዳለ ግን አዋጅ ቁጥር 25/1988"ን" ያወጣው የፌዴራል መንግስት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የስራ ክርክሮች የሚመሩበትን ስርኣት የዘረጋውን አዋጅ ቁጥር 377/1996 ከየካቲት 18 ቀን 1996 ዓ/ም ስራ ላይ ያዋለ ሲሆን በዚህ አዋጅ የስራ ክርክር ስልጣን ድልድል የተደረገው የግል የስራ ክርክርና የወል የስራ ክርክር የሚሉትን ጉዳዮችን መሰረት በማድረግ ሲሆን የተከራካሪ ወገንን ማንነትን ግንዛቤ ውስጥ ባስገባ መልኩ አይደለም፡፡በመሆኑም ክርክሮቹ ክልል የተነሱ ቢሆንም ጉዳዩን የክልል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ወይም አግባብነት ያላቸው የቋሚ ወይም ጊዜአዊ ቦርዶች ሊመለከቱ እንደሚችሉ አድርጎ ሕጉን ሕግ አውጪው አውጥቷል፡፡ይህ አዋጅ ከአዋጅ ቁጥር 25/1988 በኋላ ከመውጣቱም በላይ ለስራ ክርክሮች ልዩ ሕግ ነው፡፡እንዲህ ከሆነ አዋጅ ቁጥር 377/1996 ለስራ ክርክሮች ከሕገ መንግስቱ በመለስ ባሉት ማናቸውም ሕጎች የበላይ ተፈፃሚነት ያለው ስለመሆኑ ተቀባይነት ያላቸው የሕግ አተረጓጎም ደንቦች የሚያስረዱን ጉዳይ ነው፡፡በመሆኑም በስራ ክርክር ተከራካሪ ወገኖች ማንነት የፍርድ ቤቶችን ስልጣን (የክልል ወይም የፌዴራል) ብሎ ለመወሰን እንደወሳኝ መለኪያ ሊወሰድ የሚገባው አይደለም፡፡ከዚህ አንጻር ሲታይ ደግሞ የኦሮሚያ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ጉዳዩን ተቀብሎ ማየቱ ከላይ የተመለከተውን የህጉን ማዕቀፍ እና በዚህ ረገድ ይህ ችሎት በመ/ቁጥር 95298 እና በሌሎች በርካታ መዛግብት በአዋጅ ቁጥር 454/1997 አንቀጽ 2(1) መሰረት በአከራካሪው የህግ ነጥብ ላይ ከሰጠው አስገዳጅ የሕግ ትርጉም ጋር የተጣጣመ ነው ከሚባል በስተቀር የሚነቀፍበትን አግባብ አላገኘንም፡፡

     

     ሁ ለተ ኛ ውን ጭብጥ በተ መለ ከተ፡- በመሰረቱ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር94 ስር እንደተመለከተው መጥሪያ በቅድሚያ መድረስ ያለበት ለተከሰሰው ሰው ሲሆን የተከሰሰው ሰው የንግድ ድርጅት ከሆነ ደግሞ ከድርጅቱ ጸሃፊ ወይም ለድርጅቱ ኃላፊ መሰጠት ያለበት መሆኑ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 97(1) ስር ተመልክቷል፡፡ሕጉ መጥሪያ አሰጣጥ ዘዴና ቅደም ተከተሉ እንዲሁም መጥሪያው ለማን እንደሚሰጥ የሚመለከተው የፍትሐ ብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ክፍል ዓይነተኛ ዓላማ ከሆኑት መካከል አንዱ ተካራካሪ ወገኖችን እኩል የመከራከር መብት እንዲኖራቸው በማድረግ ጉዳዩን ፍትሐዊ በሆነ አኳኋን ለመወሰንማስቻል መሆኑን ይታወቃል፡፡በመሆኑም ፍርድ ቤቱ መጥሪያ የሚደርስበትን ተገቢ መንገድና ለማን መድረስ እንዳለበት ማረጋገጥ ይገባዋል፡፡

     

    መጥሪያ በተገቢው መንገድ ደርሶት ተከራካሪ ወገን ካልቀረበ ወይም መጥሪያን አልቀበልም ካለ ፍርድ ቤቱ ሊከተለው የሚገባው ስርዓትም በሕጉ በግልጽ ተመልክቷል፡፡ ከእነዚህም ድንጋጌዎች መካከል በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 70(ሀ)፣103፣104፣105፣ 106 እና 107 ስር የተመለከተው ሊጠቀሱ


    የሚችሉ ሲሆን በእነዚህ ድንጋጌዎች መሰረት ተከሳሽ በሌለበት ክርክሩ ታይቶ ውሳኔ ሊሰጥ የሚችለው መጥሪያው በአግባቡ የደረሰው መሆኑ ሲረጋገጥ ወይም መጥሪያውን ለመቀበል ፈቃደኛ አለመሆኑ ወይም ሊገኝ ያልቻለ መሆኑ ሲረጋገጥ ስለመሆኑ ተመልክቷል፡፡ ድንጋጌዎቹ መጥሪያው በትክክል ያልደረሰው መሆኑ ከተረጋገጠ ጉዳዩ ተከሳሽ በሌለበት እንዲታይ የማይታዘዝ ስለመሆኑ ያስገነዝባሉ፡፡በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 70(ሀ) ድንጋጌ ስር ላይ "መጥሪያው በትክክል  መድረሱ"የሚለው ሐረግ መኖሩም የሚያሳየው ስለመጥሪያ አሰጣጥና አደራረስ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 94 እስከ 110 ድረስ የተመለከቱት ሁኔታዎች በአግባቡ መሟላታቸውን የሚያስገነዝብ ነው፡፡አንድ ተከሳሽ በሌለበት ጉዳዩ ታይቶ ውሳኔ ከተሰጠውም በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 78 መሰረት መፍትሔ መጠየቅ የሚችል ስለመሆኑ ተመልክቷል፡፡በዚህ ድንጋጌ መሰረት መፍትሔ ሊጠየቅ የሚችለው አቤቱታ አቅራቢው በሚያቀርበው አቤቱታ ላይ የጥሪው ትዕዛዝ "በሚገባ ያልደረሰው" መሆኑን በመጥቀስ ይህንኑ ማረጋገጥ ሲችል ነው፡፡ከእነዚህ ሁሉ ድንጋጌዎች መገንዘብ የሚቻለው አንድ ሰው የመከራከር መብቱን እንደተወው የሚቆጠረው መጥሪያው በሕጉ በተዘረጋው ሥርዓትና ቅደም ተከተል መሰረት ደርሶት ክርክር ያለው መሆኑን እያወቀሳይቀርብ ሲቀር ብቻ መሆኑን ነው፡፡ፍርድ ቤቱ በሕጉ የተዘረጋውን ስርዓት ተከትሎ አማራጭ የመጥሪያ አደራረስ ሥርዓት  ከፈጸመ መጥሪያው ለተከሳሹ እንደደረሰ እንደሚቆጠርና በቂና ሕጋዊ ምንክያት ካለው ብቻወደ ክርክሩ እንዲገባ የሚፈቀድ መሆኑን ከላይ የተጠቀሱት ድንጋጌዎች ይዘትና መንፈስ ያስገነዝባል፡፡ስለሆነም ማንኛውም ውሳኔ መሰጠት ያለበትም በሕጉ በተዘረጋው ሥርዓት መሰረት መጥሪያው መድረሱ በሚገባ የተረጋገጠና የተከሳሽ የመከራከር መብት የተጠበቀ መሆኑ ሲታወቅ ሊሆን ይገባል፡፡

     

    ወደ ተያዘው ጉዳይ ስንመለስም በወረዳው ፍርድ ቤት በነበረው ክስ ተጠሪ ለአመልካች ድርጅት መጥሪያውን እንዲያደርሱ የተደረገ ሲሆን ተጠሪ መጥሪያውን ይዘው "ለድርጅቱ ኃላፊ ልሰጥ ስል ኃላፊው አልቀበልም ብለውኛል" በማለት በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 103 መሰረት በቃለ መሃላ አረጋግጠው መጥሪያውን የመለሱ ሲሆን ለዚህም ምስክሮች ያላቸው መሆኑን ጭምር ዘርዝረው አቅርበዋል፡፡ተጠሪ ለስር ፍርድ ቤት በ18/03/2004 ዓ/ም እና በ26/03/2004 ዓ/ም የተጻፉ  ሁለት ቃላ መሃላዎችን ያቀረቡ ሲሆን አሁን በዚህ ረገድ ግራ ቀኙን እያከራከረ ያለው በየትኛው ቀን የተዘረዘሩት ምስክሮች ናቸው ስለመጥሪያው አደራረስ ሊመሰክሩ የሚገባቸው? የሚል ነጥብ ነው፡፡ከላይ እንደተገለጸው የተጠሪ የመጥሪያ አደራረስ በቃለ መሃላ ተደግፎ የቀረበ ቢሆንም መጥሪያውን ለአመልካች ድርጅት ያደረሱ መሆን ያለመሆኑን በተመለከተ ምስክሮች እንዲሰሙ በማለት በክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት በመ/ቁጥር 148159 ጥቅምት 26 ቀን 2005 ዓ/ም ተወስኖ ጉዳዩ የተመለሰለት የወረዳው ፍርድ ቤትም በ18/03/2006 ዓ/ም በተፃፈው ቃለ መሃላ የተጠቀሱትን ምስክሮች የሠማና ምስክሮቹ መጥሪያውን ተጠሪ ለአመልካች ድርጅት ማድረሳቸውንና የአመልካች ድርጅት ኃላፊ አልቀበልም ማለታቸውን ማረጋገጣቸውን ምክንያት አድርጎ የአመልካችን በሌለሁበት ታይቶ የተወሰነ ውሳኔ ይነሳልኝ ጥያቄን ሳይቀበለው የቀረ ሲሆን ይኼው የወረዳው ፍርድ ቤት ውሳኔ በክልሉ የሰበር ሰሚ ችሎትም ተቀባይነት አግኝቷል። እንግዲህ በክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት በመ/ቁጥር 148159 በ26/02/2005 ዓ/ም በተሰጠው ውሳኔ ስለመጥሪያው አደራረስ የግራ ቀኙምስክሮች እንዲሰሙ ተብሎ ለወረዳው ፍርድ ቤት ከመመለሱ ውጪ በ26/03/2004 ዓ/ም በተጠሪ ለወረዳው ፍርድ ቤት በቀረበው ቃለ መሃላ የተጠቀሱት ምስክሮች እንዲሰሙ በግልጽ የተሰጠ ውሳኔ የለም፡፡በ26/03/2004 ዓ/ም ቀረበ በተባለው ቃለ መሃላ ያሉት ምስክሮችም አመልካች የተጠሪን ደመወዝ መጠን ለማወቅ ይቻል ዘንድ መዝገቡን እንዲያቀርብ የወረዳው ፍርድ ቤት በ22/03/2004 ዓ/ም በዋለው ችሎት ትዕዛዝ ሰጥቶ ስለነበር አመልካች የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ አልፈፀምም፣የፍርድ ቤቱን መጥሪያአልወሰድም ማለቱን ለማረጋጋጥ የቀረቡ ስለመሆኑ የክርክሩ ሂደት የሚያሳይ   ሁኖ


    አግኝተናል፡፡እንዲህ ከሆነ በ26/03/2004 ዓ/ም በቀረበው ቃለ መሃላ የተጠቀሱት የተጠሪ ምስክሮች ስለመጥሪያ አደራረስ የሚሰሙበት የሕግ አግባብ የለም፡፡አንድ ማስረጃ መሰማት የሚገባው ለጉዳዩ አግባብነት ሲኖረው ስለመሆኑ ተቀባይነት ያላቸው የማስረጃ ሕግ ደንቦች የሚሳዩት ጉዳይ ነው፡፡ ስለሆነምአመልካች በዚህ ረገድ የሚያቀርበው ክርክር ተቀባይነት የሚሰጠው ሁኖ አልተገኘም፡፡በ18/03/2004 ዓ/ም በተጻፈ የተጠሪ ቃለ መሃላ የተጠቀሱት ምስክሮች መሰማታቸው ተገቢ ነው ከተባለ እነዚህ ምስክሮች አመልካች መጥሪያ ደርሶት አልቀበልምበማለት ተጠሪን የመለሳቸው መሆኑን ያረጋገጡት የፍሬ ነገር ጉዳይ በመሆኑ የተጠሪ የመከራከር መብቱ መታለፉ ከፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 97(1)፣103፣70(ሀ) እና 78 ድንጋጌዎች ይዘትና መንፈስ ተገቢ እንጂ የሚነቀፍበት አግባብ የለም፡፡

     

     ሦ ስተ ኛውን ጭብጥ በተመ ለከተ፡ -አመልካች ተጠሪን ያሰናበተበትን ሕጋዊ ምክንያት በዋናው ክርክር ያለበቂ ምክንያት ባለመቅረቡ አላስረዳም፡፡ይልቁንም ተጠሪ አመልካች ከህግ ውጪ ያሰናበታቸው መሆኑን በወረዳው ፍርድ ቤት ባቀረቡት ማስረጃ ያረጋገጡት ጉዳይ መሆኑን የክርክሩ ሂደት ያሳያል፡፡በመሆኑም የአመልካች እርምጃ ሕገ ወጥ ነው ተብሎ የተሰጠው ውሳኔ በዚህ ችሎት የሚለወጥበት አግባብ የለም፡፡በመሰረቱ አንድ ተከሳሽ በሌለበት ታይቶ በተሰጠው በዋናው ጉዳይ ላይ ለበላይ ፍ/ቤት ይግባኝ ሲያቀርብ የይግባኝ አቀራረብ አድማሱ በተወሰኑት ነጥቦች ላይ ብቻ መሆን እንዳለበት የይግባኝ አቀራረብን በተመለከተ የተደነገጉት ድንጋጌዎች መንፈስ እንደሚያስረዳና ጉዳዩ በሌለበት ታይቶ የተወሰነበት ተከሣሽ ለበላይ ፍ/ቤት ይግባኝ ሲያቀርብ በስር ፍ/ቤት በተከራካሪነት ቀርቦ ያላነሣውን ነጥብ ማንሳት እንደማይችል፣እንደዚህ ዓይነት ተከራካሪ በፍ/ቤቱ የውሣኔ አሰጣጥ ሂደት ውስጥ ክሱን፣የማስረጃዎችን አግባብነት ተቀባይነት እና ጥንካሬ ባግባቡ ያላገናዘበ ሁኔታ አለ የሚል ከሆነ ይግባኝ ሊያቀርብ እንደሚችል ይህ ሰበር ሰሚ ችሎት በመ/ቁጥር 36412  በአዋጅ ቁጥር 454/1997 አንቀጽ 2(1) በየትኛውም እርከን የሚገኝ ፍርድ ቤትን የሚያስገድድ የሕግ ትርጉም የሰጠበት ጉዳይ ነው፡፡ስለሆነም ፍ/ቤት ከሣሹ ያቀረበው ክስ አባሪ ሆነው ከቀረቡት ማስረጃዎች አግባብነት፣ተቀባይነትና ጥንካሬ አኳያ በመመርመር ተገቢውን ዳኝነት አልሰጠም በሚል ይግባኝ የማቅረብና ወደ ቀጣዩ የሰበር ደረጃም ቅሬታውን ማድረስ ጉዳዩ በሌለበት ታይቶ ውሳኔ ለተሰጠበት ወገን በሕግ የተጠበቀለት መብት መሆኑ አስገዳጅ የሕግ ትርጉም የተሰጠበት ጉዳይ ነው፡፡

     

    ወደ ተያዘው ጉዳይ ስንመለስም የወረዳው ፍርድ ቤት በ29/03/2004 ዓ/ም በዋለው ችሎት ስንብቱ ህገ ወጥ ነው ብሎ ሲወሰን በዚህ ውሳኔ ተጠሪ የሚከፈለኝ ገንዘብ በግልጽ አልተቀመጠልኝም በማለት ለዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ አቅርበው የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤትም ጉዳዩን አይቶ ለስር የተጠሪ ደመወዝ ተጣርቶ ሊታወቅ ይገባል፣ከዚህ በኋላ የማስጠንቀቂያ፣የስራ ስንብት ክፍያ እና ካሳ፣የሳምንት፣የአመት እና የበዓል ቀናት ክፍያዎች እንዲሁም ያልተከፈለው ደመወዝ ታስቦ በግልጽ መቀመጥ አለበት በማለት በመ/ቁጥር 33824 በ17/05/2004 ዓ/ም በዋለው ችሎት ለወረዳው ፍርድ ቤት መልሶለት የወረዳው ፍርድ ቤትም ተከሳሽ ግብር ሲከፍልበት የቆየበት ቦታ በደገም ወረዳ ገቢዎች ጽ/ቤት እና በተከሳሽ ድርጅት እንዲቀርብ አዝዞ ደመወዝንና የትርፍ ሰዓት ክፍያ በጠቅላላው ብር 6410.92 መሆኑ በድጋሚ እንደቀረበለት ጠቅሶ እንዲሁም ከደገም ወረዳ ገቢዎች ጽ/ቤት ከሳሽ ደመወዝ ሲበላበት የነበረው እና ወሩ ያልታወቀ ፔሮል ቀርቦ በሁለቱም ወገኖች ስምምነት መደረሱን ገልፆ ውሳኔውን ወደ ገንዘብ ለውጦ ማስቀመጥ የአፈፀጸም ክስ ቡድን እንጂ የፍርድ ቤት ተግባር አይደለም፣ግን የይግባኝ ሰሚውን ፍርድ ቤት ትዕዛዝ መከተል ተገቢ ነው ብሎ ተጠሪ በሰዓት የሚያገኘው ደመወዝ ብር 13.46.00፣በቀን ደግሞ 107.69 መሆኑን ማረጋገጡን ጠቅሶ የወር


    ደመወዙን ብር 3230.70 ይዞ ክፍያዎችን አስልቶ በጠቅላላው ብር 277,294.04 እንዲከፈለው ሲል በመ/ቁጥር 03756 የካቲት 12 ቀን 2004 ዓ/ም በዋለው ችሎት ወስኗል፡፡አመልካች በሌለበት ጉዳዩ በመታየቱ ላይ የይግባኝ ቅሬታና የሰበር አቤቱታ ለክልል ፍርድ ቤቶች ሲያቀርብ ለተጠሪ እንዲከፈሉ በተወሰኑ ክፍያዎች መጠን ላይም በሕግ አግባብ ያልተሰሉ መሆኑን ጭምር በመጥቀስ ቅሬታ ሲያቀርብ የነበረ መሆኑን የክርክር ሂደት የሚያሳይ ሲሆን ተጠሪ በዚህ ረገድ የሚያቀርቡት ክርክር አመልካች በሌለበት በታየው ውሳኔ ላይ ይግባኝና የሰበር ክርክር ማቅረብ አይችልም የሚል መሆኑን ተረድተናል፡፡ይሁን እንጂ ከላይ እንደተገለጸው አመልካች በሌለበት ጉዳዩ ቢታይም ተጠሪ ያቀረቡት ክስ አባሪ ሆነው ከቀረቡት ማስረጃዎች አግባብነት፣ተቀባይነትና ጥንካሬ ያለመመርመሩንና እንዲሁም አዋጅ ቁጥር 377/1996 ከአስቀመጠው የክፍያ ስሌት ውጪ መሆኑን በሚያሳዩት ነጥቦች ላይ በዚህ ችሎት ክርክር ከማቅረብ የሚያግደው የሥነ ስርዓት ህግ የሌለ በመሆኑ በዚህ ረገድ ተጠሪ ያቀረቡትን ክርክር የምንቀበለው ሁኖ አልተገኘም፡፡

     

    አመልካች ከተጠሪ ጋር ያለውን የሥራ ውል በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ ቁጥር 377/1996 አግባብ ያለማስጠንቀቂያ ከሥራ ለማሰናበት የሚያስችል ሁኔታ ሣያጋጥመው ካቋረጠ በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀፅ 39(1/ለ) መሠረት በአንቀፅ 40 ንዑስ አንቀፅ 2፣ በአንቀፅ 44 እና በአንቀፅ 43 ንዑስ አንቀፅ 4(ለ) የተደነገጉትን ክፍያዎች ለተጠሪ የመክፈል ኃላፊነት አለበት፡፡ከዚህ አንጻር የስር ፍርድ ቤት አመልካች ለተጠሪ እንዲከፍል በማለት የዘረዘራቸው የክፍያ አይነቶች  የማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ፣ካሳ፣የስራ ስንብት ክፍያ፣የሳምንት እረፍት ክፍያ፣የአምስት አመት በዓላት ክፍያ ናቸው፡፡የማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ፣የስራ ስንብት ክፍያና የካሳ ክፍያዎች የሚሰሉበት አግባብ በሕጉ ተለይቶ የተቀመጠ ሲሆን ይህንኑ በሕጉ የተቀመጠውን ስሌት ተግባራዊ ለማድረግ ሰራተኛው በወር ሲከፈለው የነበረው ደመወዝ በሕጋዊ ማስረጃ መረጋግጥ የግድ ይላል፡፡ከዚህ አንፃር ጉዳዩን ስንመለከተው የወረዳው ፍርድ ቤት የተጠሪ የወር ደመወዝ ብር 3230.70(ሶስት ሺህ ሁለት መቶ ሰላሳ ብር ከሰባ ሳንቲም) መሆኑን በመ/ቁጥር 03756 የካቲት 12 ቀን 2004 ዓ/ም በዋለው ችሎት በሰጠው ውሳኔ አረጋግጧል፡፡በመሆኑም የተጠሪ የማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ፣የስራ ስንብትና የካሳ ክፍያዎች መሰላት ያለባቸው በዚሁ የተጠሪ ወርሃዊ ደመወዝ የተባለው መጠን መሰረት ተደርጎ በሕጉ የተቀመጠው ስሌት ባገናዘበ መልኩ ሊሆን ይገባል፡፡

     

    ይህንኑ መሰረት አድርገን እያንዳንዱን የክፍያ መጠን ስንመለከትም ተጠሪ በአመልካች ድርጅት ያላቸው የአገልግሎት ዘመን አምስት አመት ከዘጠኝ ወርበመሆኑ በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጽ 35(1)(ለ)) መሰረት ሊከፈላቸው የሚገባው የማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ የሁለት ወር ደመወዝ ብር

    6,461.40 (ስድስት ሺህ አራት መቶ ስልሳ አንድ ብር ከአርባ ሳንቲም) ሁኖ አግኝተናል፡፡የስራ ስንብት ክፍያን በተመለከተም በአዋጁ አንቀጽ 39(1(ለ)) እና 40(1)(2) ድንጋጌዎች መሰረት የሚመጣው ውጤት ብር 8,384.30 (ስምንት ሺህ ሶስት መቶ ሰማንያ አራት ከሰላሳ ሳንቲም) እንጂ ብር 47,383.60 ያለመሆኑን ተረድተናል፡፡እንዲሁም የካሳ መጠኑ በአዋጁ አንቀጽ 43(4(ሀ)) መሰረት ሲሰላ የወረዳ ፍርድ ቤት የተጠሪን አማካይ የቀን ደመወዝ ብር 107.69 ያደረገው በመሆኑ ይኼው የቀን አማካይ ደመወዝ በመቶ ሰማንያ ሲባዛ የሚመጣው ውጤት ብር 19,384.20(አስራ ዘጠኝ ሺህ ሶስትመቶ ሰማንያ አራት ብር ከሃያ ሳንቲም) እንጂ ብር  25,849.60 ያለመሆኑን ተገንዝበናል፡፡ሌላው የስር ፍርድ ቤት በአዋጁ አንቀጽ 71 እና 68 መሰረት የሳምንት እረፍት ክፍያ በማለት ያስቀመጠው ብር 188,784.57(አንድ መቶ ሰማንያ ስምንት ሺህ ሰባት መቶ ሰማንያ አራት ብር ከሃምሳ ሳንቲም) የስሌቱ መነሻ እና የመብቱ አድማስ ለጉዳዩ አግባብነትና ጥንካሬ ያላቸውን ማስረጃዎችን መሰረት ያደረገ ስለመሆኑ የክርክሩ ሂደት አያሳይም፡፡በመሆኑም በዚህ ረገድ የተሰጠው


    የውሳኔ ክፍል ሕግና ማስረጃን መሰረት ያደረገ ሁኖ አላገኘነውም፡፡የአምስት አመት በዓል ክፍያን በተመለከተ ግን አመልካች በስር ፍርድ ቤት በሌለበት የታየ በመሆኑና የይርጋ ክርክር ተነስቷል ለማለት ስለማይቻል እንዲሁም ፍርድ ቤቱ ደግሞ ይርጋውን በራሱ ሊያነሳ የሚችልበት አግባብ የሌለ በመሆኑ የገንዘቡ መጠን ብር 16,357.00(አስራ ስድስት ሸህ ሶስት መቶ ሃምሳ ሰባት ብር) ተብሎ በስር ፍርድ ቤት መቀመጡን የማንቀበልበትን አግባብ አላገኘንም፡፡ በአጠቃላይ በጉዳዩ ላይ የተሰጠው ውሳኔ በከፊል መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት ያለበት ነው በማለት ተከታዩን ወስነናል፡፡

     

     ው ሳ ኔ

     

    1.  በኦሮሚያ ብሔራዊ  ክልላዊ  መንግስት ጠቅላይ  ፍርድ  ቤት  ሰበር  ሰሚ  ችሎት በመ/ቁጥር

    163369 በ20/01/2006 ዓ/ም የተሰጠው ውሳኔ ተሻሽሏል፡፡

    2. በሂደቡ አቦቴ ወረዳ በመ/ቁጥር 03756 የካቲት 12 ቀን 2004 ዓ/ም በዋለው ችሎት የአመልካች የስንብት እርምጃ ሕገ ወጥ ነው ተብሎ የተሰጠው የውሳኔ ክፍል የፀና ሲሆን ውጤቱን በተመለከተ የሰጠው የውሳኔ ክፍል ግን በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰረት ተሻሽሏል፡፡

    3. የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ጉዳዩን የማየት ስልጣን አለው፣የአመልካች የመከራከር መብት የታለፈው ባግባቡ ነው፣የአመልካች እርምጃ ህገ ወጥ ነው በማለት መወሰኑም ተገቢ ነው በማለት ውጤቱን ግን አመልካች ለተጠሪ ሊከፍል የሚገባው በአዋጅ ቁጥር 377/1996 በተቀመጠው ስሌትና በማስረጃ በተረጋገጠው የደመወዝ መጠን በመሆኑ፡-

    3.1  የስራ ስንብት ክፍያ ብር 8,384.30፣

    3.2  የሁለት ወር ማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ ብር 6,461.40፣

    3.3  የካሳ ክፍያ ብር 19,384.20 እና

    3.4 የአምስት አመት   የበዓል   ቀናት   ክፍያ  ብር   16,357.00  ሁኖ በድምሩ   ብር

    50,586.90(ሃምሳ ሺህ አምስት መቶ ሰማንያ ስድስት ብር ከዘጠና ሳንቲም) ነው በማለት ወስነናል፡፡

    4. የሳምንት ዕረፍት ቀናት ክፍያ ብር 188,784.57 በተመለከተ ግን በሕግ እና በማስረጃ ያልተደገፈ በመሆኑ  አመልካች ለተጠሪ ሊከፍል አይገባም በማለት ወስነናል፡፡

    5. በዚህ ችሎት ለተደረገው ክርክር የወጣውን ወጪና ኪሳራ የየራሳቸውን ይቻሉ ብለናል፡፡ መዝገቡ ተዘግቷል፤ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ ብለናል፡፡

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

     

     

    ት/ጌ

     

  • ጋብቻ በሁኔታ ፈርሷል ሊባልባቸው ስለሚችሉባቸው ሁኔታዎች ጋብቻ በሁኔታ ፈርሷል ተብሎ ከሚታሰብበት ጊዜ አንስቶ በአስር ዓመት ጊዜ ውስጥ የንብረት ክፍፍል ጥያቄ ካልቀረበ በይርጋ የሚታገድ ስለመሆኑ

     

    የሰ/መ/ቁ.102662

    የካቲት 15 ቀን 2008 ዓ/ም

    ዳኞች፡-አልማው ወሌ ዓሊ መሐመድ ተኽሊት ይመሰል እንዳሻው አዳነ ቀነዓ ቂጣታ

    አመልካች፡- ወ/ሮ አልማዝ ለሼ- ጠበቃ ኤርሚያስ ደስታ ቀረቡ፡፡ ተጠሪ፡- አቶ በቀለ በላቸው- ወኪል  ትርፍነሽ በቀለ ቀረቡ

    መዝገቡ ተመርምሮ ተከታዩ ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ ጋብቻ ፈርሷል ሊባል የሚችልበትን አግባብ የሚመለከት ነው፡፡ጉዳዩ የተጀመረው በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የደብረብርሃን ወረዳ ፍርድ ቤት ሲሆን ክሱን ያቀረቡት የአሁኑ አመልካች ናቸው፡፡ የክሱ ይዘትም፡- ከአሁኑ ተጠሪ ጋር በአገር ባህል የጋብቻ አፈጻጸም ስርዓት ጋብቻ ፈጽመው ለአርባ አመታት ያህል አብረው መኖራቸውን፣ ይሁን እንጂ ከመስከረም 2006 ዓ/ም ጀምሮ ሊስማሙ ባለመቻላቸው በመካከላቸው ሰላም እንደሌለ ገልፅው ጋብቻው ፈርሶ የጋራ ንብረት እንዲካፈሉ ይወሰን ዘንድ ዳኝነት መጠየቃቸውን የሚያሳይ ነው፡፡ የአሁኑ ተጠሪ ለክሱ በሰጡት መልስም ከአመልካች ጋር ባልና ሚስት የነበሩ መሆኑን ሳይክዱ አመልካች ከአስራ ዘጠኝ አመታት በፊት ቤቱን ጥለው መሄዳቸውንና ተለያይተው የሚኖሩ መሆኑን ጠቅሰው ክሱ በይርጋ ሊታገድ ይገባል  በማለት የመጀመሪያ ደረጃ መቃወሚያ ያስቀደሙ ሲሆን በፍሬ ነገር ረገድ ደግሞ ከአመልካች ጋር ያፈሩት የጋራ ንብረት የሌለ መሆኑን ዘርዝረው ክሱ ውድቅ ሊሆን ይገባል ሲሉ ተከራክረዋል፡፡

     

    የግራ ቀኙ ክርክር በዚህ መልኩ የቀረበለት የሥር ፍ/ቤትም ጉዳዩን መርምሮ በአመልካች እና በተጠሪ መካከል የነበረው ጋብቻ ከአስር አመታት በፊት ፈርሷል የሚል ድምዳሜ ደርሶ የአመልካች ክሱ በይርጋ የታገደ ነው በማለት ውድቅ አድርጎታል፡፡ በዚህ ብይን የአሁኗ አመልካች ቅር በመሰኘት ይግባኛቸውን ለሰሜን ሸዋ አስተዳደር ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቢያቀርቡም ተቀባይነት አላገኙም፡፡


    ከዚህም በኋላ አመልካች የሰበር አቤቱታቸውን ለክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት አቅርበውም በጉዳዩ ላይ በተሠጠው ብይን መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት የለም ተብሎ መዝገቡ ተዘግቶባቸዋል፡፡ የአሁኑ የሰበር አቤቱታው የቀረበው ይህንኑ ውሳኔ በመቃወም ሲሆን ይህ ችሎት የቀረበውን አቤቱታ መርምሮ ተጠሪን በመጥራት ግራ ቀኙን በጽሑፍ አከራክሯል፡፡እንዲሁም የወረዳው ፍርድ ቤት ዋና መዝገብ እንዲመጣ አድርጓል፡፡

     

    በአጠቃላይ የክርክሩ ይዘት ከላይ የተመለከተው ሲሆን ምላሽ ማግኘት የሚገባው የጉዳዩ ጭብጥ በተጠሪና በአመልካች መካከል ጋብቻ በሁኔታ ፈርሷል ተብሎ በበታች ፍርድ ቤቶች መወሰኑ ተገቢነት አለውን? የሚለውነው፡፡

    ከክርክሩ ሂደት መገንዘብ የተቻለው የወረዳው ፍርድ ቤት የግራ ቀኙን ምስክሮች ሰምቶ በአመልካችናበተጠሪ መካከልየነበረውጋብቻ በሁኔታ ፈርሷል በማለት በአመልካች በኩል የቀረበውን ክርክር አልተቀበለውም፡፡ ፍርድ ቤቱ ወደዚህ ድምዳሜ የደረሰው በአመልካችና በተጠሪ መካከል የነበረው የጋብቻ ግንኙነታቸው ከ1987 ዓ/ም ጀምሮ ተቋርጦ ግራ ቀኙ ለየብቻ መኖር መጀመራቸው ተረጋግጧል በሚል አቢይ ምክንያት ነው፡፡ ይህ የወረዳው ፍርድ ቤት የፍሬ ነገር ማጣራትና የማስረጃ ምዘና ድምዳሜ በዚህ ረገድ ተመሳሳይ የሆነ ስልጣን ባለው የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሙሉ በሙሉ ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ አመልካች በዚህ ችሎት አጥብቀው የሚከራከሩት ግራ ቀኙ ሌላ ትዳር መስርተው የራሳቸውን ሕይወት የማይኖሩ መሆኑን፣ አልፎ አልፎ በጤና ምክንያት አመልካች ለፀበል ወደ ሌላ ቦታ ከመሄዳቸው ውጪ አመልካችና ተጠሪ ያልተለያዩና እስከ መስከረም 2006 ዓ/ም ድረስ አንድ ላይ የሚኖሩ መሆኑን ዘርዝረው ለጉዳዩ አግባብነት የሌለው አስገዳጅ ውሳኔ ተጠቅሶ መወሰኑ ያላግባብ ነው በሚል ነው፡፡ እኛም ጉዳዩን ይህ ሰበር ችሎት በመ/ቁ. 14290፣ 20983፣ 31891፣ 67924 እና በሌሎች በርካታ መዛግብት ከሰጣቸው አስገዳጅ ውሳኔዎች ጋር አገናዝበን ተመልክተናል፡፡

    በመሰረቱ የወረዳው ፍርድ ቤት ለውሳኔው መሰረት ያደረገውና ይህ ሰበር ሰሚ ችሎት በሰ/መ/ቁጥር 31891 ሌሎች ከላይ በተጠቀሱት መዛግብት በሰጣቸው አስገዳጅ ውሳኔዎች በባልና ሚስት መካከል ያለ ጋብቻ በፍ/ቤት በተሰጠ የፍቺ ውሳኔ ፈርሷል ባይባልም የተጋቢዎች ተለያይቶ ለረጅም ጊዜ መኖር፣ በዚህም ጊዜ ሌላ ትዳር መሥርቶ መገኘት የቀድሞው ጋብቻ በሕጋዊ መንገድ ተቋርጧል ሊያስብል ይችላል በማለት በአዋጅ ቁጥር 454/97 አንቀጽ 2(1) መሰረት በየትኛውም እርከን የሚገኝ ፍርድ ቤትን የሚያስገድድ የሕግ ትርጉም የሰጠበት ጉዳይ ነው፡፡ ከዚህም ውሳኔ ይዘትና መንፈስ መረዳት የሚቻለው የጋብቻ መፍረስ በተጋቢዎች የረዥም ጊዜ መለያየት ሊከናወን የሚችል መሆኑና ፍርድ ቤቱም በዚህ አግባብ የፈረሰውን ጋብቻ እንደገና እንዲፈርስ ውሳኔ የሚሰጥበት አግባብ የሌለ መሆኑን ነው፡፡ በሰ/መ/ቁጥር 67924 የተሰጠው አስገዳጅ የሕግ ትርጉም ደግሞ በቤተሰብ ሕጉ አግባብ የመተጋገዝና የመተባበር ግዴታቸውን


    ሲወጡና የነበሩና ያልተለያዩ መሆኑ ከተረጋገጠ ጋብቻ በሁኔታ ፈርሷል ለማለት የማይቻል መሆኑን በመዝገቡ ከተረጋገጡ ፍሬ ነገሮች በመነሳት የተወሰነ ነው፡፡

    ወደ ተያዘው ጉዳይ ስንመለስም አመልካችና ተጠሪ በሕጉ አግባብ ጋብቻ መሰርተው ልጆችን ከወለዱ በኋላ በ1987 ዓ/ም ጀምሮ በአካል ተለያይተው ለአስራ ዘጠኝ አመታት ያህል ሳይገናኙ የኖሩ መሆኑን ከግራ ቀኙ ምስክሮች ቃል የተረጋገጠ መሆኑን የበታች ፍርድ ቤቶች ደምድመዋል፡፡ ይህ ሰበር ሰሚ ችሎት ያስቀረበው የወረዳው ፍርድ ቤት ዋና መዝገብም  የግራ ቀኙ ምስክሮች የመሰከሩት የፍሬ ነገር ነጥብ በይዘቱ የበታች ፍርድ ቤቶች ከደመደሙት ጋር ተመሳሳይነት ያለው መሆኑን ተገንዝቦአል፡፡ በመሆኑም አመልካች ከተጠሪ ጋር እስከ መስከረም 2006 ዓ/ም ድረስ አልተለያየንም በማለት የሚያቀርቡት ቅሬታ በስር ፍርደ ቤት ዋና መዝገብ ውስጥ በምስክሮች ከተነገረው የምስክርነት ቃል ይዘትና ፍሬ ነገሩን የማጣራትና ማስረጃን የመመዘን ስልጣን ያላቸው ፍርድ ቤቶች ከደረሱበት ድምዳሜ ውጪ በመሆኑ ተቀባይነት የሚሰጠው ሁኖ አልተገኘም፡፡ በዚህ ረገድ አመልካች ያቀረቡት ቅሬታ ለዚህ ችሎት በኢ.ፌ.ዲ.ሪፐብሊክ ሕገ መንግስት አንቀጽ 80(3(ሀ)) እና አዋጅ ቁጥር 25/1988 አንቀጽ 10 ድንጋጌዎች አግባብ የተሰጠውን ስልጣንም ያላገናዘበ ሁኖ አግኝተናል፡፡

    በመሰረቱ ጋብቻ በተጋቢዎች መካከል የመተጋገዝ፣ የመከባበርና መደጋገፍ እንዲሁም አብሮ የመኖር ግዴታን የሚጥል መሆኑን ከክልሉ የቤተሰብ ሕግ አዋጅ ቁጥር 213/1992 አንቀጽ 60 እና 61 ድንጋጌዎች ይዘትና መንፈስ የምንገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡ ከዚሁ  አኳያ በተጠሪና በአመልካች መካከል የነበረው ጋብቻ ይህ ሰበር ችሎት አስቀድሞ በተመሳሳይ ጉዳይ ከሰጠው ውሳኔ አንጻር ተቋርጧል? ወይንስ አልተቋረጠም? የሚለውን ለመወሰን ከፍ ብሎ በአመልካችና በተጠሪ መካከል በጋብቻ ውስጥ በግራ ቀኙ የሚጠበቁ ግዴታዎች ባግባቡ ሲተገበሩ ያልነበሩና እነዚህን ግዴታዎችን ለመወጣት ደግሞ በአመልካች በኩል ያጋጠመው ሁኔታ በሕጉ የተጣሉባቸውን ግዴታቸውን ለመወጣት የማያስችል የነበረ መሆኑ ባልተረጋገጠበት ሁኔታ አመልካች ከተጠሪ ጋር አልተለያየንም፣ በጤና ችግር ምክንያት አልፎ አልፎ ለፀበል ሌላ ቦታ እሄድ ነበር በማለት የሚያቀርቡት ክርክር በክርክሩ ሂደት በማስረጃ የተረጋገጡትን ፍሬ ነገሮችን መሰረት አድርጎ ያልቀረበ ሁኖ አግንተነዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በተያዘው መዝገብና ይህ ሰበር ችሎት አስገዳጅ የሕግ ትርጉም የሰጠባቸው መዛግብት የያዟቸው መሰረታዊ ፍሬ ነገሮች ከዚህ መዝገብ ከተረጋገጡት እውነታዎች ሙሉ በሙሉ የተመሳሳይነት ያላቸው ሁኖ እያለ አመልካችም ሆነ ተጠሪ ሌላ ትዳር መስርተው ሕይወታቸውን በመምራት ላይ አይገኙም በማለት በሰ/መ/ቁጥር 31891 የተሰጠውን አስገዳጅ የሕግ ትርጉም በመተውና ግንኙነቱ ያልተቋረጠ  ተጋቢዎችን መሰረት ተደርጎ በመ/ቁጥር 67924 የተሰጠውን ውሳኔ መሰረት በማድረግ አመልካች መከራከራቸው ከአዋጅ ቁጥር 454/1997 አንቀጽ 2 (1) አተገባበር ጋር የሚጋጭ ሁኖ አግኝተናል፡፡ ስለሆነም የአመልካችና የተጠሪ ግንኙነት ከ1987 ዓ/ም ጀምሮ በሁኔታ የፈረሰ


    በመሆኑ እና ለጉዳዩ አግባብነት በላቸው ከላይ በተጠቀሱት መዛግብት በተሰጠው ትርጉም መሰረት የጋራ ንብረት ጥያቄም በአስር አመት ያልቀረበ በመሆኑ የተጠሪ ክስ በይርጋ የታገደ ነው ተብሎ ብይን መሰጠቱ የሚነቀፍበትን የሕግ ምክንያት አላገኘንም፡፡ ሲጠቃለልም በጉዳዪ ላይ የተሰጠው ውሳኔ መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስሕተት የተፈጸመበት ሁኖ ስላላገኘነው ተከታዩን ወስነናል፡፡

     ው ሳ ኔ

    1. የደብረብርሃን ከተማ ወረዳ ፍርድ ቤት በመ/ቁጥር  0108191/06  በ22/08/2006 ተሠጥቶ በሰሜን ሸዋ መስተዳደር ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመ/ቁጥር 0114418 በ30/08/2006 ዓ/ም፣ በክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በመ/ቁጥር 030- 5041 ግንቦት 19 ቀን 2006 ዓ/ም የተሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰረት ጸንቷል፡፡

    2. በአመልካችና በተጠሪ መካከል በአገር ባህል የጋብቻ አፈፃጸም ስርዓት ተመስርቶ የነበረው ጋብቻ ለረዥም ጊዜ ተለያይቶ በመኖር ምክንያት ፈርሷል በማለት ወስነናል፡፡

    3.  በዚህ ችሎት ለተደረገው ክርክር የወጣውን ወጪና ኪሳራ የየራሳቸውን ይቻሉ ብለናል፡፡

     ት ዕ ዛ ዝ

    ከደብረብርሃን ከተማ ወረዳ ፍርደ ቤት የመጣ መዝገብ ቁጥር 0108191/06 በመጣበት አኳሀን ይመለስ ብለናል፡፡

    መዝገቡ ተዘግቷል፤ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ፡፡

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

     

    ወ/ከ

  • ሞግዚት የማይንቀሳቀስ ንብረት ሽያጭ ፈጽሞ ሲገኝ ሊወሰዱ ስለሚገቡ ዝርዝር ሁኔታዎች የሕግ ድንጋጌዎችን በመተላለፍ ሞግዚቱ ለሚፈጽማቸው ድርጊቶች፤ ወኪል የሆነ ሰው ከተሰጠው ሥልጣን በላይ በሚሠራበት ጊዜ አግባብነት ያላቸው የውክልና ሕግ ድንጋጌዎች ተፈጻሚ የሚሆኑ ስለመሆኑ የተሻሻለው የቤተሰብ ሕግ አዋጅ ቁ.213/1992 አንቀጽ 306፣277 የፍ/ብ/ሕ/ቁ.2207/1

    የሰ/መቁ.103151

    መስከረም 24 ቀን 2008 ዓ.ም

    ዳኞች፡-አልማው ወሌ

     

    ረታ ቶሎሳ ሙስጠፋ አህመድ ቀነዓ ቂጣታ

    ሌሊሴ ደሳለኝ

     

    አመልካች፡-አቶ ግርማ ብሩ አየለ - ቀረቡ

     

    ተጠሪ፡-አቶ መርዕድ ብስራት - ጠበቃ አበበ ማስረሻ ጋር ቀረቡ መዝገቡን መርምረን የሚከተለውን ፍርድ ሰጥተናል፡፡

     ፍ ር ድ

     

    ይህ ጉዳይ የቤት ሽያጭ ውል እንዲፈርስ የቀረበ ክስን መነሻ ያደረገ ክርክር ነው፡፡ የጉዳዩ አመጣጥ ሲታይ፡- የሥር ከሳሽ /የአሁን ተጠሪ/ በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት ባቀረበው ክስ የወላጅ አባቴ እና የ2ኛ ተከሳሽ የጋራ ንብረት የሆነውን በጉለሌ ክፍለ ከተማ ቀበሌ 03 የቤት ቁጥር አዲስ ካረታ ቁ.3329 የሆነውን ቤት 2ኛ ተከሳሽ ከሞግዚትነት ስልጣን ተቃራኒ ሚያዝያ 23 ቀን 2000 ዓ.ም በተደረገ ሽያጭ ውል ለ1ኛ ተከሳሽ በብር 350,000 የሸጠች ስለሆነ 1ኛ ተከሳሽም /የአሁኑ አመልካች/ የከሳሽና የሌሎች ሰዎች የጋራ ንብረት መሆኑን እያወቀ ለቅን ልቡና ተቃራኒ በሆነ መንገድ ስለገዛ የሽያጭ ውሉ እንዲፈርስልኝ፣ 1ኛ ተከሳሽ ቤቱን እንዲያስረክበኝ በማለት አመልክቷል፡፡

     

    ይህን ክስ በተመለከተ ተከሳሾች መልስ እንዲሰጡበት የታዘዘ ሲሆን የሥር 1ኛ ተከሳሽ /የአሁን አመልካች/መጥሪያ ደርሶት የጽሑፍ መልስ ስላልሰጠ ታልፏል፡፡ የሥር 2ኛ ተከሳሽ በሰጠችው መልስ ባለቤቴ ከሞተ በኋላ ልጆች ለማሳደግ የተቸገርኩ በመሆኑ የቤት ሽያጭ ውል ፈጽሜአለሁ፡፡ 1ኛ ተከሳሽም የቤቱን ሸያጭ ገንዘብ እንደውሉ አልከፈለኝም፤ እኔ ቤቱን የሸጥኩኝ ለከሳሽና ለሁለት ወንድሞቹ ጥቅም እንጂ ለግሌ ጥቅም አይደለም፤ ፍ/ቤቱ የመሰለውን ውሳኔ ቢሰጥ አልቃወምም በማለት ተከራክራለች፡፡ 1ኛ ተከሳሽ ክርክር በሚሰማበት ቀን ቀርቦ  ሲከራከር


    ሞግዚት የማይንቀሳቀስ ንብረት መሸጥ ትችላለች፣ እኔ በቤቱ ላይ ሰፊ ለውጥ ያደረኩ ስለሆነ ውሉ ሊፈርስ አይገባም በማለት ተከራክሯል፡፡

     

    ከዚህ በኋላ ፍ/ቤት ግራ ቀኙን በማከራከር፣ የከሳሽን የሰው ምስክር በመስማት በሰጠው ውሳኔ በተከሳሾች መካከል ሚያዝያ 23 ቀን 2000 ዓ.ም የተደረገው የቤት ሽያጭ ውል የልጆችን ጥቅም በሚጎዳ መልኩ ስለተፈጸመ ፈርሶ ተዋዋይ ወገኖች ወደ ነበሩበት ይመለሱ፣ 2ኛ ተከሳሽ ብር 60,000 ለ1ኛ ተከሳሽ ትመልስ፣ 1ኛ ተከሳሽ በገዙት ይዞታ ሲገለገሉበት በነበረው ቤት ላይ ያወጡት ወጪ ካለ ክስ አቅርቦ መጠየቅ ይችላል በማለት ወስኗል፡፡ የሥር 1ኛ ተከሳሽ ይህን ውሳኔ በመቃወም ይግባኝ ማመልከቻውን ለፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ያቀረበ ሲሆን ፍ/ቤቱ ግራ ቀኙን በማከራከር በሰጠው ውሳኔ፣ የቤቱ ሽያጭ ዋጋ በአብዛኛው ስላልተከፈለ 2ኛ ተከሳሽ ለግል ጥቅም አውላለች፣ የልጆች ቅጥም ላይ ጉዳት ድርሷል የሚያስብል ስላልሆነ፣የሽያጭ ውሉን ለማፍረስ በቂና አሳማኝ ምክንያት ስለሌለ ሊፈርስ አይገባም በማለት የሥር ውሳኔ በመሻር ወስኗል፡፡ የሥር ከሳሽ ይህን ውሳኔ በመቃወም ይግባኝ ማመልከቻውን ለፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ያቀረበ ሲሆን ፍ/ቤቱ ግራ ቀኙን በማከራከር በሰጠው ውሳኔ፣ የቤት ሽያጭ ውሉ የከሳሽን ጥቅም የሚጎዳ ስለሆነ ውሉ ሊፈርስ ይገባል በማለት የፌዴራል ከፍተኛ ፍ/ቤት  ውሳኔ በመሻር የፌዴራል የመጀመያ ደረጃ ፍ/ቤት ውሳኔን በማጽናት ወስኗል፡፡ የአሁን የሰበር አቤቱታም ይህን ውሳኔ በመቃወም ለማስለወጥ የቀረበ ነው፡፡

     

    የአሁን አመልካች ሐምሌ 10 ቀን 2006 ዓ.ም በተጻፈ አቤቱታ የተጠሪ ሞግዚትና አስተዳዳሪ የነበሩት ወ/ሮ ክብካብ አስፋው የቤት ሽያጭ ውሉን ያደረጉት ለተጠሪ እና ለሌሎች ሁለት ወንድሞቻቸው መልካም አስተዳደር ስለሆነ ውሉን የተደረገው ለልጆቹ ቅጥም መዋሉ በተጠሪም ሞግዚት በጽሑፍ እና በምስክሮች በስር ፍ/ቤት የተረጋገጠ ሆኖ ሳለ ውሉ ሊፈረስ  ይገባል በማለት የተሰጠ ውሳኔ መሰረታዊ የሕግ ስህተት ያለበት ነው፡፡ የተጠሪ ሞግዚት ከተቀበለችው የቤት ሽያጭ ውሉ ገንዘብ የተጠሪ ድርሻ ብር 10,000 ብቻ ስለሆነ ውሉ የሚፈርስበት ምክንያት የለም፡፡ አመልካች ቤቱን ከገዛሁ በኋላ ሌላ አዲስ ሰርቪስ ቤት ክፍሎች ብር 450,000 በላይ ወጪ በማድረግ በቤቱ ላይ ከፍተኛ የሆነ የይዘት ለውጥ አድረጎበታል፡፡ ስለዚህ የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት እና የፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ውሉ ፈርሶ ወደ ነበራችሁበት ተመለሱ በማለት የወሰኑት ውሳኔ መሰረታዊ የሕግ ስህተት ያለው ስለሆነ እንዲሻርልኝ፣ የፌዴራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ውሳኔ እንዲፀናልኝ በማለት አመልክቷል፡፡

     

    የሰበር አጣሪ ችሎትም መዝገቡን በመመርመር "በአመልካች እና በተጠሪ ሞግዚት መካከል የተደረገው የቤት ሸያጭ ውል ይፍረስ ተብሎ በሥር ፍ/ቤቶች የመወሰኑን አግባብነት ከመዝገብ ቁ.46490 አንጻር ለመርመር ሲባል አቤቱታው ለሰበር ያስቀርባል በማለት ተጠሪ መልስ እንዲሰጥ


    በታዘዘው መሰረት መስከረም 7 ቀን 2007 ዓ.ም የተጻፈ መልስ አቅርቧል፡፡ የመልሱ ይዘትም፡- የተጠሪ ሞግዚት የማይንቀሳቀስ ንብረት መሸጥ አትችልም፡፡ እኔ ከቤቱ ድርሻ እያለኝ ያለ እኔ ፈቃድ ሸጣለች፡፡ የተጠሪ መብት መጣስ እና መጎዳት የሚጀምረው ከዚህ መሰረታዊ ከሆነው የባለቤትነት መብቶች አኳያ ስንነሳ ነው፡፡ እኔ በቤቱ ሽያጭ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰብኝ አስረድቼአለሁ፣ አመልካች ግን ከሽያጩ ጥቅም ያገኘሁት መሆኑን አላስረዳም፡፡ አመልካች ከቤቱ ሽያጭ ገንዘብ የከፈለው ብር 60,000 ብቻ ሲሆን ቤቱን ተረክቦ እያኖረበት ነው፣ ከጉዳት በቀር ጥቅም ሊኖር አይችልም፡፡ ተጠሪው በሽያጩ ጉዳት እንጂ ያገኘሁት ጥቅም ስለሌለ ለሰበር መዝገብ ቁ.46490 ከሰጠው ውሳኔ ጋር የማይቃረን ስለሆነ ውሳኔው እንዲፀናልኝ፣ የቀረበው አቤቱታ ውድቅ እንዲደረግልኝ፡፡ አመልካች ከቤቱ ድርሻ የተጠሪ ድርሻ 10,000 ብር ብቻ ስለሆነ ሊፈርስ አይገባም በማለት ያቀረበው ክርክር የባለቤትነት መብትን የጣሰ እና ሕጉ ተቃራኒ ስለሆነ ተቀባይነት የለውም፡፡ አመልካቹ በቤቱ ላይ ግንባታ ስለመካሄዱ ያቀረበው ማስረጃም የለም፣ በቤቱም ላይ የይዘትም ሆነ የቅርጽ ለውጥ አላደረገም፣ የተጠሪ ሞግዚት የቤት ሽያጩን ገንዘብ ማባከናቸውን እንጂ ለልጆች ጥቅም ያወሉት መሆኑን ያረጋገጠ ማስረጃ  የለም፡፡ ስለዚህ አመልካች ያቀረበው አቤቱታ ውድቅ ሆኖ የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት እና የፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ውሳኔ መሠረታዊ የሕግ ስህተት የለበትም ተብሎ እንዲፀናልኝ፣ ወጪና ኪሳራ እንዲወሰንልኝ በማለት ተከራክሯል፡፡ አመልካች ጥቅምት 04 ቀን 2007 ዓ.ም በተጻፈ የመልስ መልስ አቤቱታውን በማጠናከር ተከራክሯል፡፡

     

    የጉዳዩ አመጣጥ ከላይ እንደተመለከተ ሲሆን፤ ይህ ሰበር ሰሚ ችሎትም የግራ ቀኙ  ክርክር ለሰበር አቤቱታው መነሻ ከሆነው ውሳኔ እና አግባብነት ካላቸው  የሕግ  ድንጋጌዎች ጋር በማገናዘብ አቤቱታው ያስቀርባል ሲባል ከተያዘው ጭብጥ አንጻር እንደሚከተለው መርምሮታል፡፡ መዝገቡን እንደመረመርነው ተጠሪ ባቀረበው ክስ የሽያጭ ውል የተፈጸመበት ቤት ላይ ድረሻ እያለኝ የእኔን ጥቅም በሚጎዳ መልክ ሞግዚት የሆነችው ወ/ሮ ክብካብ ሣህሉ ወልደማርያም በሽጨጭ ውል ለአመልካች የሸጠች ስለሆነ ውሉ እንዲፈርስልኝ በማለት አልክቷል፡፡ የተጠሪ ሞግዚት /የሥር 2ኛ ተከሳሽ/ በጽሑፍ ባቀረበችው መልስ ቤቱን የሸጥኩት ለተጠሪ እና ለሌሎች ወንድሞቹ ቅጥም ነው በማለት የተከራከረች ቢሆንም እንደምስክር ሆነ በሰጠችው ቃል ደግሞ ከቤቱ ሽያጭ ገንዘብ ውስጥ ብር 60,000 ብቻ የተቀበለች እንደሆነና ለራሷ ትምህርት ክፍያ እንደከፈለችና ቀሪውን ለወንድሟ እንዳበደረች ገልጻለች፡፡ አመልካች በበኩሉ መጥሪያ ደርሶት የፍሑፍ መልስ ባለመስጠቱ የታለፈ ስለሆነ የጽሑፍ መልስ እና ማስረጃ በማቅረብ በማስረዳት መከራከር የነበረበትን ክርክር በተመለከተ መብት አጥቷል፡፡ ስለዚህ አልካች በጽሑፍ መከራከር የነበረበትና ማስረጃ በማቅረብ ማስረዳት የነበረበትን ፍሬ ነገር በተመለከተ አሁን ለማንሳት የሚችልበት የሕግ መሰረት የለውም፡፡ ተጠሪ ባቀረበው ክርክር አመልካች ከተጠሪ ሞግዚት  ጋር


    የቤት ሽያጭ ውሉን ሲፈጽም በቤቱ ላይ ልጆች ድርሻ ያላቸው መሆኑን ውሉ እያመለከተ ነው ቤቱን የገዛው የሚለውን፣ አመልካች ይህን ፍሬ ነገር ክዶ እየተከራከረ አይደለም፡፡ አመልካች አጥብቆ የሚከራከረው በሞግዚቱ በኩል የተደረገው የቤቱ ሽያጭ ለልጆች ጥቅም ነው እንጂ ጥቅማቸውን የሚጎዳ አይደለም የሚል ነው፡፡ የተጠሪ እናት የሆነችው የሥር 2ኛ ተከሳሽ የተሻሻለው የቤተሰብበ ሕግ አዋጅ ቁ.213/1992 አንቀጽ 220/1/ መሰረት ሕጋዊ የሞግዚትነት ስልጣን እንደተሰጣቸው ከመዝገቡ መረዳት ይቻላል፡፡ ይህ ማለት የሥር 2ኛ ተከሳሽ ተጠሪን በመወከል ሕጋዊ ተግባሮችን ለተጠሪ ጥቅም ለመፈጸም ስልጣን የተሰጣቸው መሆኑን ያመለክታል፡፡ በዚሁ የተሻሻለው የቤተሰብ ሕግ አንቀጽ 277 የሞግዚት ስልጣን በተመለከተ የማይንቀሳቀስ ንብረት ከመሸጥ ጋር ተያይዞ የሚለው ነገር የለውም፡፡ ነገር ግን ሕጉ ሞግዚት መሸጥ የሚችላቸውን የንብረት ዓይነቶች በመዘርዘር በማስቀመጡ፣ ከዚህ ዝርዝር ወጭ ያሉትን ንብርቶች በተመለከተ ሞግዚት መሸጥ አይችልም ቢባል እንኳን ሞግዚት የማይንቀሳቀስ ንብረት ሽያጭ ፈጽሞ ከተገኘ ግን ምላሸ ለማግኘት ሌላ ሕግ መፈተሽ አስፈላጊ ሆኖ ይታያል፡፡ ከዚህ አንጻር የተሻሻለው የቤተሰብ ሕግ አዋጅ ቁ.213/1992 አንቀጽ 306 እንደሚደነግገው "የሕግ ድንጋጌዎችን በመተላለፍ ሞግዚቱ ለሚፈጽማቸው ድርጊቶች፤ ወኪል የሆነ ሰው ከተሰጠው ሥልጣን በላይ በሚሠራበት ጊዜ አግባብነት ያላቸው የውክልና ሕግ ድንጋጌዎች ተፈጻሚ ይሆናሉ" የሚል ነው ፡፡ በዚህ መሰረት ተወካዩ ከተሰጠው ስልጣን ውጭ በመውጣት የሰራውን ስራ በተመለከተ የፍ/ብ/ሕ/ቁ.2207/1/ እንደሚያመለክተው "ተወካዩ ከስልጣኑ ውጭ የሠራው ስራ በቅን ልቡና ሆኖ ሲገኝ ሥራውን ወካዩ እንዲያጸድቅለት ይገደዳል" የሚል ነው፡፡ በዚህ አግባብ የሞግዚቱ "ቅን ልቡና" መታየት ያለበት የተሰራ ስራ የልጁን ጥቅም የሚጎዳ ነው ወይስ አይደለም? ከሚል አንጻር መሆን እንዳለበት ነው፡፡

     

    የፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በሰበር መዝገብ ቁ.46490 መጋቢት 21 ቀን 2002 ዓ.ም በሰጠው አስገዳጅ የሕግ ትርጉም ሞግዚት የማይንቀሳቀስ ንብረት ለልጆች መልካም አስተዳደግና ጥቅም የሸጠ መሆኑ ከተረጋገጠ የሽያጭ ውል ለማፍረስ የሚያስችል በቂ ምክንያት አይደለም በማለት ወስኗል፡፡ ይህ ማለት የማይንቀሳቀስ ንብረት ሽያጭን በተመለከተ የሽያጭ ውሉ ሊፈርስ ይገባል ወይስ አይገባም የሚል ጭብጥ መታየት ያለበት ለልጆች ቅጥም መሆን አለመሆኑን በማጣራት ነው፡፡ ከዚህ አንጻር በተጠሪ ሞግዚት እና በአልመካች መካከል የተደረገውን የቤት ሽያጭ ውል ለተጠሪ እና ለሌሎች ወንድሞቹ ጥቅም የዋለ ነው ወይስ አይደለም? የሚለው ጭብጥ ሲታይ ለተጠሪ ጥቅም መዋሉን የሚያመለክት ምንም ነገር የለም፡፡ የተጠሪ ሞግዚት ከቤቱ ሽያጭ አመልካች የከፈላት ገንዘብ ብር 60,000 እንደሆነ ከዚህ ውስጥ ብር 10,000 ለትምህርት እንደከፈለች፣ ቀሪውን ለወንድሟ እንዳበደረች አረጋግጣለች፡፡  ይህ ማለት ከቤት ሽያጭ የተገኘው ገንዘብ ለተጠሪም ሆነ ለሌሎች ልጆች አለመዋሉን   ያመለክታል፡፡


    እንዲሁም ከቤቱ ሽያጭ የተገኘ ገንዘብ ለልጆቹ ጥቅም መዋሉን የሚያመለክት ማስረጃ መቅረቡን የሥር ፍ/ቤቶች ያረጋገጡት ነገር የለም፡፡ አመልካች ራሱ ከቤቱ ሽያጭ ብር 350,000 ውስጥ እስካሁን የከፈለው ብር 60,000 ብቻ ሲሆን ቀሪውን ገንዘብ ያለመክፈሉ ግራ ቀኙ የሚካከዱት ጉዳይ ስላልሆነ፣ የቤቱ ሽያጭ ውል ለተጠሪ እና ለሌሎች ልጆች ጥቅም የዋለ ነው ለማለት የሚያችል አንድም ነገር የለም፡፡ አመልካች ቤቱ የተሸጠበትን ገንዘብ አብዛኛውን ሳይከፍል እንዲያውም አነስተኛ ገንዘብ ብቻ ከፍሎ በዚህ ሽያጭ የልጆቹ ጥቅም ተጠብቆላቸዋል፣ የሽያጭ ውሉም ለልጆች ጥቅም የተደረገ ነው፤ ለተጠሪና ለሌሎች ወንድሞቹ መልካም  አስተዳደግ ውሏል በማለት የሚያቀርበው ክርክር ሚዛን የሚደፋ ሆኖ አይታይም፡፡ ስለዚህ የሚያዝያ 23 ቀን 2000 ዓ.ም በተጠሪ ሞግዚትና በመአልካች መካከል የተደረገው የቤት ሽያጭ ውል ለተጠሪና ለሌሎች ወንድሞቹ ማለትም ለልጆች ጥቅም እና መልካም አስተዳደግ ያልዋለ መሆኑ ስለተረጋገጠ፣ የሸያጭ ውሉ ሌፈርስ አይገባም በማለት አመልካች ያቀረበው ክርክር በየትኛውም የሕግ መመዘኛ ተቀባይነት ያለው ሆኖ አልተገኘም፡፡

     

    ሌላው አመልካች ባቀረበው ክርክር ተጠሪ ከቤቱ ያለው ድርሻ አነስተኛ መሆኑን በመግለጽ ለውሉ መፍረስ መክንያት ሊሆን አይችልም የሚለው ሲታይ ተጠሪ ከቤቱ ድርሻ እስካለው ድረስ የጋራ ንብረቱ ከሱ ፈቃድ ውጭ መሸጥ የሌለበት መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ ከልጆች መብት አንጻር የአመልካች ክርክር ተቀባይነት የለውም፡፡ በሌላ በኩል አመልካች ቤቱን ከገዘሁ በኋላ በቤቱ ላይ ግንባታ አካሄጃለሁ ያለውን በተመለከተ ተጠሪ ምንም ዓይነት ግንባታ አልተደረገም በማለት ክዶ የተከራከረ ሲሆን፣ አመልካች ደግሞ የጽሑፍ ክርክር በማቅረብ በማስረጃ ስላላስረዳ፣ በሥር ፍ/ቤት በማስረጃ ያላስረዳውን ክርክር ለዚህ ሰበር ሰሚ ችሎት እንደቅሬታ ነጥብ ማቅረቡ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ.329/1/ መሰረት ተቀባይነት የለውም፡፡ በአጠቃላይ የሥር ፍ/ቤቶች የሽያጭ ውሉ የልጆችን ጥቅም የሚጎዳ ስለሆነ ውሉ ፈርሶ ግራ ቀኙ ወደ ነበሩበት ሊመለሱ ይገባል፣ አመልካች በቤቱ ላይ ያወጣ ወጪ ካለ ከሶ መጠየቅ ይችላል በማለት የሰጡት ውሳኔ መሰረታዊ የሕግ ስህተተ የሌለው በመሆኑ የሚከተለው ውሳኔ ተሰጥቷል፡፡

     

     ው ሳ ኔ

     

    1. የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት በመዝገብ ቁ.201566 በ07/08/2005 ዓ.ም የሰጠው ውሳኔ፣ እንዲሁም የፌዴራል ከፍተኛ ፍ/ቤት በመዝገብ ቁ.137501 ታህሳስ 22 ቀን2006 ዓ.ም የሰጠውን ውሳኔ መሰረታዊ የሕግ ስህተት ያለው  በመሆኑ በመሻር የፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት በመዝገብ ቁ.98101 በ22/09/2006 ዓ.ም የሰጠው ውሳኔ መሰረታዊ የሕግ ስህተት የሌለው በመሆኑ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ.348/1/ መሰረት ጸንቷል፡፡


     

    2.  የዚህ ውሳኔ ግልባጭ ለስር ፍ/ቤቶች ይድረስ ብለናል፡፡

    3. ግራ ቀኙ በዚህ ችሎት የደረሰባቸውን ወጪና ኪሳራ የየራሳቸውን ይቻሉ ብለናል፡፡ መዝገቡ በውሳኔ ስለተዘጋ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ ብለናል፡፡

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

     

    ማ/አ

  • በተሻሻለው የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የቤተሰብ ህግ መሰረት ባልና ሚስት የጋራ ንብረታቸውን እኩል የማስተዳደር መብት ያላቸውና የጋራ ስምምነት ሳይኖር ንብረትን ለሌላ 3ኛ ወገን በአንደኛው ተጋቢ ፍቃድ ብቻ የተላለፈ ከሆነና ይህንን ስምምነቱን ያልሰጠው ተጋቢ በህጉ በተፈቀደለት ጊዜ ገደብ ውስጥ የይፍረስልኝ ጥያቄውን ካላቀረበ የተፈፀመው ተግባር እንደፀና የሚቆይ ስለመሆኑ አዋጅ ቁ.213/92 አንቀፅ 68፣69

     

    የሰ/መ/ቁ. 103721

    የካቲት 03 ቀን 2008 ዓ.ም

     

     

    ዳኞች፡- ተሻገር ገ/ስላሴ

    ሙስጠፋ አህመድ ተፈሪ ገብሩ

    ሸምሱ ሲርጋጋ አብርሃ መሰለ

     

    አመልካች፡-  ወ/ሮ ሰሚራ ጀማል ከጠበቃ ሰለሞን ታደሰ ቀረቡ ተጠሪ፡- 1ኛ. አቶ ጀማል እንዲሪስ ከጠበቃ መሰረት ስዩም ጋር ቀረቡ

    2ኛ. ወ/ሮ ሉላ አረፈ አልቀረቡም

    3ኛ.አቶ ሀጎስ አብዱራህማን በመዝገብ ቤት በኩል እንዲሰሙ ተናግሯል፡፡

    መዝገቡ ተመርምሮ ተገቢውን ዳኝነት ለመስጠት ለየካቲት 01 ቀን 2008 ዓ/ም ቀጠሮ የያዘ ሲሆን በዚህም መሰረት መዝገቡን መርምረን በአዳሪ በዚሁ እለት የሚከተለውን  ፍርድ ሰጥተናል፡፡

     ፍ ር ድ

    ይህ የሰበር ጉዳይ በአሁን አመልካችና 1ኛ ተጠሪ መካከል የነበረው ጋብቻ በፍ/ቤት የፍቺ ውሳኔ መሰረት መፍረሱን ተከትሉ በአሁን አመልካች የጋራ ንብረት ድርሻ ጥያቄ መነሻ የስር ፍ/ቤቶች የጋብቻ ውጤት በሆነው የንብረት ክርክር ላይ የሰጡትን ዳኝነት በዚህ ሰበር ሰሚ ችሎት ክርክር ካስነሳው የውሳኔ ክፍል አንፃር ተመልክቶ የውሳኔውን አግባብነት ከግራ ቀኙና ክርክሩ የሚመለከተው ሆኖ የተገኘው 3ኛ ተጠሪም ካቀረቡት ክርክር ጋር በማገናዘብ አስፈላጊውን ዳኝነት ለመስጠት በሚል የቀረበ ነው፡፡

     

    የጉዳዩም አመጣጥ ባጭሩ እንደሚከተለው ነው በአሁን አመልካች እና 1ኛ ተጠሪ መካከል ሚያዚያ 21  ቀን 1987 ዓ/ም ተደርጎ የነበረው ጋብቻ ግንቦት 24 ቀን 2003 ዓ/ም  በፍ/ቤት የፍቺ ውሳኔ መፍረሱን ተክትሎ የአሁን ተጠሪ ሀምሌ 27 ቀን 2003 ዓ/ም ተሻሽሎ ባቀረቡ ማመልከቻ የጋራ ንብረት ናቸው ያሏቸውን ናቸው የሚንቀሳቀስና የማይንቀሳቀስ ንብረቶች በመዘርዘር ድርሻቸው ተለይቶ ይወሰንላቸው ዘንድ ተገቢ የነበሩትን የአሁን 1ኛ ተጠሪን እና የ1ኛ ተጠሪ ሌላ ሚስት የሆነችን የአሁን 2ኛ ተጠሪን በተከሳሽነት ላይ ደመወዝ በዚሁ የጋብቻ ውጤት በሆነው የንብረት ድርሻ ጥያቄ ላይ፣ እንደዚህም 1ኛ ተጠሪ የጋራ ንብረትን ሲያስተዳድር የደረሰው፣  ጉዳት ሲታወቅ በኃላ ተገቢውን የካሳ ለአመልካች እንዳይከፍል ይወሰንልኝ   በማለት


    ዳኝነት ጠይቀዋል፡፡ እንደክርክራቸው ያስረዳልናል ያሏቸውን የሰውና የሰነድ ማስረጃም አያይዘው አቀርበናል፡፡

     

    የአሁን 1ኛ እና 2ኛ ተጠሪዎች የጋራ ንብረት ናቸው በሚል በአሁን አመልካች የክስ ማመልከቻ ላይ ከተዘረዘሩት ንብረቶች የጋራ ንብረት የሆኑትን በማመን፣ በጋራ ሀብትነት የማይታወቁትን፤ የሚያገኙትን ደግሞ በመካድ በአመልካች ክስ በተዘረዘረው የንብረት ዝርዝር አንፃር መልስ የሰጡ ሲሆን፤ በንብረት አስተዳደር ረገድ ያደረስኩት ጉዳት የሌላ በመሆኑ የሰጠው  ጥያቄ አይመለከተኝም በማለት ክርክራቸውን አቅርቧዋል፡፡ ለክርክሩም ድጋፍ ያላቸውን ማስረጃዎች አያይዘው አቅርበዋል፡፡

     

    የአሁን 3ኛ ተጠሪም የጋራ ንብረት ነው በሚል በአሁን አመልካች ከተጠቀሱት ንብረቶችና መካከል በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍል ከተማ ወረዳ 3 ክልል በቤት  ቁጥር 2545  የሚታወቀውን ቤት በውል አዋዋዩ ክፍል ዘንድ ጂ. ኤስ. ኤ.ጄኔራል ትሬድንግ ኃ/የተ/የግል ማህበር ከተባለው ድርጅት የገዙት ስለሆነ የአመልካችን ጥያቄ ውድቅ ለማድረግ ይወሰንልኝ በማለት በጉዳዩ ላይ ጣልቃ ገብተውም ተከራክረዋል፡፡ ለዚህም ክርክራቸው ለማስረጃነት ሰነዶችን እንዳቀረበም የመዝገቡ መልሰን ያስረዳል፡፡

     

    እኚሁ ጣልቃ ገብ ያቀረቡትን ክርክር አስመልክቶ የአሁን አመልካች ጣልቃገብ ፍ/ቤቱ በንብረቱ ላይ የእግድ ትእዛዝ በሰጠበት ንብረት ላይ ግዥ የፈጸሙ ስለሆነ የሽያጭ ውሉ ከጅምሩ ፈራሽ ስለሆነ ጥያቄው ተቀባይነት የለውም በማለት ተከራክረዋል፡፡

     

    የአሁን 1ኛ እና 2ኛ ተጠሪዎች ይህንኑ በቁጥር 2545 ተመዝግቦ የሚታወቀውን ቤት አስመልክቶ ንብረቱ በማናቸውም ስም ተመዝግቦ የሚታወቅ የጋራ ንብረት ባለመሆኑ እንጂ የጋራ ንብረት ተቆጥሮ መቅረቡ ተገቢ አይደለም በማለት አመልካች ባቀረቡት ክስ ቀጥተኛ መልስ የሰጡ ከመሆኑም በላይ በጣልቃ ገብ በኩል የቀረበው ክርክር አስመልክቶ ደግሞ ተቃውሞ የሌለባቸው መሆኑን ገልጸናል፡፡

     

    ሁሉም ወገኖች ከላይ ባጭሩ ለይዞታ ደረጃ የተገለጸውን የጹሁፍ ክርክር ካደረጉ በኋላ ለጉዳዩም ላይ የቃል ክርክር እንዳደረጉ መዝገቡ ያስረዳል፡፡

     

    የስር ፍ/ቤትም ከግራ ቀኙ ክርክር በመነሳት በአከራካሪነታቸው በጭብጥነት ተይዘው ከማስረጃ አንፃር ለማየት ዳኝነት ያስፈልጋቸዋል፡፡ በማለት ከሙግት ደረጃ ደርሶ ለማስረጃ ሰምቶ ዳኝነት ካሳረፈባቸው ንብረቶች መካከል በአከራካሪያቸው ከዚህ ሰበር ደረጃ ዘልቀው ከደረሱት መካከል አንዱ በቤት ቁጥር 2545 የተመዘገበውን ቤት አስመልክቶ


    የአሁን አመልካች በጋብቻ ዘንድ የተፈራውን ይህንኑ ንብረት ከእኔ ለማሸሽ ሲል ያለ እኔ ፈቃድ ጀ. ኤስ.ኤ አጄኔራል ትሬድንግ ኃ/የተ/የግል ማህበር ወደ ተባለው ድርጅት በመዋጨነት አስገምቶ አሽሽቶ የሰጠ በመሆኑ፤ እንዲሁም ይህን ንብረት የአሁን 3ኛ ተጠሪ ፍ/ቤቱ በንብረቱ ላይ የእግድ ትእዛዝ ከተሰጠበት በኋላ እንዲገዙት የተደረገ ስለሆነ ንብረቱ የጋራ ሀብት መሆኑ ታውቆ በድርሻዬ ልከፍል ይገባል በማለት የተከራከሩ ቢሆንም በኢፊድሪ የፍትህ ሚንስተር የሰነዶች ማረጋገጫና ከዘገባ ጽ/ቤት በቀን 10/3/2002 ዓ/ም በተፈረመ የጂ ኤስ ኤ ጄነራል ትሬድንግ ኃ/የተ/የግል ማህበር የመመስረቻ ጽሁፍ ይዘው በቤት ቁጥር 2545 ተመዝግቦ የሚታወቀው  በ1ኛ ተጠሪ  አማካኝነት በመጭነት  የተመዘገበ መሆኑ ተረጋግጧል፡፡

     

    ሚያዚያ 16 ቀን 2002 ዓ/ም በተካሄደ የጂ ኤስ ኤ.ኤጀኔራል ትሬድንግ ኃ/የተ/የግል ማህበር ለሂሳብ 1ኛ ተጠሪ በማህበሩ የየራሳቸውን አክስዮን በብር 240,000.00 /ሁለት መቶ አርባ ሺህ ብር/ ሽጠው የተሰራበት መሆኑ በኢፈደሪ የፍትህ ሚኒስቴር ማስረጃ ማረጋገጫ ምዝገባ ጽ/ቤት ማህተም በተረጋጠ ሰነድ ተረጋግጧል ጂ. ኤስ ጄኔራል ትሬድንግ ኃ/የተ/ የግል ማህበር ግንቦት 17 ቀን 2003 ዓ/ም በተፃፈና በሰነዶች ማረጋገጫና መዝገብ ጽ/ቤት በተመዘገበ የሽያጭ ውል ይህንኑ የቤት ቁጥር 2545 የሆነው በብር 240,000.00 /ሁለት መቶ አርባ ሺህ ብር/ ለጣልቃ ገብ ለአሁን 3ኛ ተጠሪ አብዱራህማን አህመድ የተሸጠ ስለመሆኑም በጣልቃ ገብ አማካኝነት በቀረበው የጽሁፍ ማስረጃ ተረጋግጧ በመሆኑም ይኸው ቤት ከ1ኛ ተጠሪ እጅ ሙሉ በሙሉ ወጥቶ በጂ ኤስ. ኤ.ተራ ደንብ ኃ/የተ/የግል ማህበር ተጠቃሎ ተላልፏል የተስፋፋውም የአመልካችና 1ኛ ተጠሪ ጋብቻ እንዳይፈርስ የፍቺ ጥያቄ ለመቅረቡ በፊት እና ለፍ/ቤት የእግድ ትእዛዝ በፊት ስለመሆኑ በማስረጃ ተረጋግጧል፡፡

     

    የጋራ የሆነውን ንብረት ያለ ሁለተኛው ተጋቢ ፈቃድ በአንደኛው ተጋቢ አማካኝነት ተላልፎ የተገኘ እንደሆነ በአዋጅ ቁጥር 213/92 አንቀፅ 68/ሀ/ እና 69 እንደተደነገገው ፈቅደን ባልሰጠው ተጋቢ ጥያቄ መሰረት ንብረቱ የተላለፈበት ግዴታ እንዲፈርስ ካልተደረገ በቀር በተፈጸፀመው የንብረት ማስተላለፍ ስምምነት ውስጥ ተጋቢዎች እንደታሰበው ግምት እንደሚሰጡ ተደንግጓል፡፡ በዚህ መሰረት አመልካች በዚህ በመ/ቁ 2545 የተደረገውን የሽያጭ ስምምነት  በመቃወም በፍ/ቤት ጥያቄ አቅርበው ያስወሰኑት የለም፡፡ ስለሆነም ንብረቱን ከእኔ ለማሸሽ ሲል ለኢኤስኤ ትሬድንግ ኃ/የተወሰነ የግል ማህበር በመውጫ ሰጥቷል የፍ/ቤቱን ዕግድ በመጣስ  ሸጦታል በማለት ያቀረቡት ክርክር ራሱ ችሎ መቅረብ የነበረበት ክርክር እንጅ በዚህ አሁን በቀረበው ክርክር ሊታይ የማይችል ከመሆኑም በላይ ንብረቱ ወደ ማህበሩ የተዛወረው በአመልካች በኩል የፍቺ ጥያቄ ለመቅረብና የዕግድ ትዕዛዝ ከመተላለፉ በፊት ስለሆነ የመ/ቁጥር  2545 የሚታወቀው ቤት የአመልካችና የተጠሪዎች የጋራ ሀብት ሳይሆን ጣልቃ ገብ በግዥ ያገኙት ንብረት ነው በማለት ወስኗል፡፡ እንዲሁም በዘምዘም ባንክ አ/ማህበር በተጠሪዎች ስም  የአከሲዮን


    ድርሻ የለም፣ በባንክ ስማችን የተቀመጠ ገንዘብ የለም በማለት ተጠሪዎች ቢከራከሩም ፍ/ቤቱ ስላቀረበው ማስረጃ ጭምር የተረጋገጠ ሆኖ ተገኝቷል በማለት ተረጋግጧል ባለው የገንዘብ መጠን መሰረት የአሁን አመልካች ድርሻ እንዳላቸው ገልፆ ዳኝነት ሰጥቶበታል በሌላ በኩል ጋብቻው ፀንቶ በነበረበት ወቅት ንብረት በማስተዳደር በኩል የፈፀሙት ጉድለት ያለመሆኑ ያለ መሆኑ ተጣርቶ ከተረጋገጠ በኋላ ለማ እንዲከፈላቸው ጠይቀዋል፡፡ ይሁን እንጅ ተጋቢዎች በጋብቻቸው ዘመን የጋራ ንብረታቸውን በጋራ እንዲያስተዳድሩ በሕጉ ግምት የሚወስድ ሲሆን ይህን ግምት ማፍረስ የሚቻለው አንደኛው ተጋቢ የሌለውን መብት የሚጎዳ ተግባር ፈፅሞ ስለመገኘቱ የማረጋገጥ ማስረጃ የቀረበ እንደሆነ በሕጉ አንቀፅ 87 ተደንግጓል 1ኛ ተጠሪ  ንብረት ሲያስተዳድሩ ፈፀሙ በሚል በማስረጃ የተረጋገጠና ተለይቶ የታወቀ ጉድለት ያልተገኘ በመሆኑ ፍ/ቤቱ ጥያቄውን አልተቀበለውም የሚለውን ውሳኔ ሰጥቶበታል፡፡ፍ/ቤቱ ለሰጠው ዳኝነት በምክንያትነት ያሰፈረውን ሐተታ እና የሰጠውን የዳኝነት ዓይነት ከዚህ በላይ ባሰፈረው አኳኋን በሰጠው የፍርድ ክፍል ላይ ከገለፀው በኋላ በፍርድ መሰረት የተረጋገጠውንና ሊረጋገጥ ያልቻለውን ምስክር አስመልክቶ የፍርድ ተከታይ በሆነው የውሳኔ ክፍል ላይ

     

    በቂርቆስ ክ/ከተማ በቀሌ 02/03 ክልል በቤት ቁጥር 297 ተመዝግቦ የሚገኘውን ቤት በትግራይ ክልል መቀሌ ከተማ የሚገኘውን ቤት አመልካችና ተጠሪዎች በጋራ ያፈሩት ንብረቶች ስለሆነ የክፍፍሉንም መንገድና ስልት ከመጥቀስ ጋር ሶስቱም እኩል እንዲከፈሉ በን/ስ/ላፍ/ክፍለ ከተማ በመ/ቁጥር 2545 የግልግል ሀብት ነው፤

     

    1ኛ ተጠሪ በቴክኖሎጅ ሲስተም ኃ/የተ/የግ/ማህበር ያላቸውን ሸር፣ በፒስ ደልለን ኃ/የተ/የማህበር ውስጥ ያለው ሸር 2ኛ ተጠሪ በዘምዘም ባንክ አ/ማህበር ያላቸው በሁለተኛ ተጠሪ ስም በዳሽን ባንክ ስለ አካባቢ ቅርንጫፍ በ1ኛ ተጠሪ ስም በወጋገን ባንክ ተ/ኃይማኖት ቅርንጫፍ በ1ኛ ተጠሪ ስም በዳሽን ባንክ ስለ አካባቢ ያስቀመጠውን ገንዘብ ከእነ መጠኑ በመግለፅ ሶስቱም እኩል እንዲካፈሉ በማለት በኮ/መ/ቁ 61875 በቀን 13/10/2004 ዓ.ም ወስኖ ግራ ቀኙን አሰናብቷል፡፡

     

    በዚህ ውሳኔ የአሁን አመልካች ቅር ተሰኝተው ባቀረቡት የይግባኝ ቅሬታ መነሻ ይግባኝ ሰሚው ከፍተኛ ፍ/ቤት በኮ/መ/ቁ 125893 ሁሉንም ወገኖች ከክርክር በኋላ

     

    የቤት ቁጥር 2545 አስመልክቶ የቀረበውን ጉዳይ በሚመለከት በዚሁ ቤት ላይ የስር ፍ/ቤት የካቲት 16/2003 ዓ.ም የዕግድ ትዕዛዝ ከመስጠቱ በፊት ቤቱ በ1ኛ አማካኝነት በመውጫነት ወደ ጅ.ኤስ.ኤ ጀኔራል ትሬድግግ ኃ/የተ/የግል ማህበር ገብቶ የነበረ እና 1ኛ ተጠሪ በማህበሩ ውስጥ የነበራቸውን 4127/4/ለ/2002 በቀን 12/9/2002 መተላለፉን የሰነዶች ማረጋገጫ ፅ/ቤት ለስር ፍ/ቤት በቀን 20/4/2004 ዓ.ም ከላከው ማስረጃ አረጋግጧል፡፡ እንዲሁም የዚሁ ቤት ስመ-


    ሀብትነት ወደ ጅኤስኤ ጀኔራል ትሬድንግ ኃ/የተ/የግ/ማህበር በቀን 04/8/2002 በቁጥር ን/ስ/ቀ/05/83/3805/02 የተላለፈ ስለመሆኑ የን/ስ/ላ/ክ/ከተማ መሬት አስተደደርና ግንባታ ፅ/ቤት የካቲት 14 ቀን 2003 ዓ.ም በተፃፈና ለስር ፍ/ቤት ከላከው ሰነድ ተረጋግጧል፡፡

     

    ቤቱ ወደ ሶስተኛ ወገን በተላለፈበት ጊዜ ግንቦት 1/2002 ዓ.ም ግራ ቀኙ በጋብቻ ውስጥ የነበሩ ስለመሆኑ የስር ፍ/ቤት ግንቦት 24 ቀን 2002 ዓ.ም የሰጠው የፍቺ ውሳኔ ያረጋግጣል፡፡ በመሆኑም ይኽው ንብረት በጋብቻ ጊዜ ወደ ሶስተኛ ወገን ሲተላለፍ መተላለፉን አላወቀም ነበር የሚሉ ሲሆን አሁን ለዚህ ችሎት ውሉ እንዲፈርስ ስልጣን ባለው ፍ/ቤት ጥያቄ አቅርበው እየተከራከሩ እንደሚገኙ በገለፁት መልኩ ይኽው ውል በማስፈረስ መብታቸውን ከሚያስከብሩ በቀር በጠየቁት ዳኝነት አኳኋን ሊስተናገድ የሚችል አይደለም በማለት የስር ፍ/ቤትን ውሳኔ ሲያፀናው በ1ኛ ተጠሪ እና በ2ኛ ተጠሪ ስም የሚገኘውን የሼር ሀብት መጠንን በሚመለከት ማህበሮቹ ለስራ ተሰማርተው ያገኙትን ትርፍ ሁሉ አጠቃሎ መወሰን ሲገባው ማህበሮች በተቋቋሙበት ጊዜ በተደረገው መነሻ ይካተታል መጠን ላይ መወሰኑ አግባብ አለመሆኑን እንዲሁም በልዩ ልዩ በባንኮች በእነዚሁ ተጠሪዎች ስም አንፃር ይገኛል የተባለውን ሀብት መጠን አስመልክቶ ፍ/ቤቱ ገንዘብ ስለመኖሩ በጠየቀበት ጊዜ በባንኮች ተቀምጦ ተገኝቷል የተባለውን የገንዘብ መጠን ሳይሆን በትዳር በነበሩበት ጊዜ አንደኛዉ ወገን ብቻ በማውጣት ለግል ጥቅም ተጠቅሞበታል ከሚያሰኝ በቀር ለጋራ ጥቅም እንደዋለ አያስቀጥርም በማለት መነሻ ሊሆን ከሚችለው ጊዜ ጋር በማስተያየት በባንኮች ካላቸው ሂሳብ እንቅስቃሴ  በመነሳት መሠረት የሚገባዉ መሆኑን ጠቅሰን በዚሁ መሠረት እራሱ ይግባኝ በከካሽ ፍርድ ቤት ጉዳዮን ተመልክተ የገንዘቡን መጠን በፍርዱ የውሣኔ ክፍፍል በተገለፀው አኳኋን ከፍ አድርጎ በሚሻሻል መወሰን ፤

     

    በሸር ድርሻ ላይ የተወሰነውን የድርሻ መጠንን ከላይ በተመለከተው መሠረት ከውሳነ በኃላ የክፍፍል ማስረጃን በሚመለከት 1ኛ መልሰ ሰጭ በሀብቱም ማህበሮች የተወሰነላቸውን የአክስዮን ድርሻ ለተቻለ እና ተጠሪዎች የሚስማሙ ከሆነ በአባልነት እንዲቀጥሉ ይህ ካልተቻለ ተሽጦ የሽያጩን ድርሻ ይከፈላቸው የአከስዮኖች አሻሻጭም በንግድ ህግ አንቀጽ 523 እና ተከታዮች ድንጋጌዎች እንደዚሁም የሰበር ሰሚ ችሎት በመ/ቁ.57288 በሰጠው የህግ ትርጉም መሠረት ሆኖ ድርሻቸው እንዲሰጣቸውና እንዲሁም በቤት ቁጥር 2545 ውስጥ/ የተሰጠውን ዕቃ በሚመለከት ቀርቧል በተባለው የወንጀል ክስ ምርመራ ውጠት መሠረት የአሁኑ አመልካች ጥያቄ የማቅርብ መብታቸው የተጠበቀ መሆኑን ከዚህ በላይ ከተገለፁት በቀር ሥማቸው በሥር ፍ/ቤቶች የተሰጠው ውሳኔ የፀና መሆኑን ለመግለፅ በሥር ፍ/ቤት የተሰጠውን ውሣኔ በማሻሻል የወሰነ መሆኑን ከፍርዱ ግልባጭ ተረድተናል ፡፡


    የአሁን አመልካች በዚህ የሰበር ሰሚ ችሎት ሊታረም ይገባል በማለት ለቅሬታቸው መሠረት ያደረጉት የቤት ቁጥር 2545 የሆነው ቤት የባልና ሚስት የጋራ ሀብት ነው ወይስ የአሁን 3ኛ ተጠሪ የሚለውን ለይቶ በመወሰን ረገድ፤እንዲሁም በሥር ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤት ውሣኔ የተረጋገጠባቸውን የአክስዮን ድርሻዎ የክፍፍሉን መንገድ በሚመለከት የአክስዮን ድርሻዎች በሚገኙበት ማህበር በአባልነት እንድቀጥል በማድረግ መወሰን ስገባው ማህበሩ ለተስማማ በሚል ተገልፆ የህግ መሠረት የለውም ለሚሉት መወሰኑ ነጥቦች ላይ ፡፡

     

    ተጠሪዎችም በበኩላቸው ክርክር በሚመለከታቸው ክርከር አንፃር በሥር ፍ/ቤቶች የተሰጠው ዳኝነት መሠረታዊ የህግ ስህተት የተፈፀመበት አይደለም የሚሉበትን ምክንያት በመጥቀስ ተከራክረዋል፡፡

     

    እንግዲህ የጉዳዮ አነሳስ፤የክርክሩ ይዘትና የሥር ፍ/ቤቶች በየደረጃው የሰጡት ዳኝነት ፤የዚህን ዳኝነት አግባብነት በሚመለከት ወገኖች በዚህ ሰበር ችሎት ያቀረቡት ክርክር በይዘት ደረጃ ከላይ ከፍ ሲል ባጭር ባጭሩ የተመለከተው ሲሆን ፤እኛም ጉዳዮን እንደሚከተለው መርምረናል ፡፡ ተመልክተናል ፡፡

     

    ጉዳዮን እንደመረመርነውም በቤት ቁጥር 2545 የተመለከተውን ቤት አስመልከቶ የአሁን አመልካች ከሥር ፍ/ቤት ጀምሮ ለክርክራቸው መሠረት ያደረጉት ንብረቱ በሽያጭ ወደ አሁን 3ኛ ተጠሪ የተላለፈው ፍ/ቤቱ በዚሁ ንብረት ላይ ዕግድ ከሰጡበት በኃላ የፍ/ቤቱ ዕግድ ተጥሶ ስለሆነ የሽያጭ ተግባሩ ዋጋ አልባ ስለሆነ ሊፈርስ ይገባል የሚለውን አንደኛው የክርክር ነጥብ ሲሆን የዚህኑ ክርክር አግባብነት ለዚሁ ጉዳዮ በሥር ፍ/ቤቶች በነበረው የክርክር ሂደት በማስረጃ ከተረጋገጠው የፍሬ ነገር ጉዳይ በመነሳት ተመልክተናል ፡፡

     

    የአሁን አመልካች ለዚህ የሰበር ጉዳይ መነሻ የሆነውን ክስ ከቀረቡ በኃላ የክርክሩ ውጤት እስክታወቅ በሚል ይኽው ቤት በማናቸውም መንገድ ቢሆን ወደ ሶስተኛ ወገን እንዳይተላለፍ የዕግድ ትእዛዝ የሰጡት የካቲት 16 ቀን 2003 ዓ.ም መሆኑና ይኽው ቤት በአሁን 1ኛ ተጠሪ አማካኝነት በዓይነት በመወጫነት ወደ ጂ.ኤስ.ኤ ጀኔራል ትሬድንግ ኃ/የተ/የግ/ማህበር የገባውና ስመ ሀብትነቱም ወደ ዚሁ ማህበር ስም የተላለፈው ይኽው የወሰነበት የዕግድ ትእዛዝ ከመስጠቱ በፊት ስለመሆኑ በሥር ፍ/ቤት የተረጋገጠ ጉዳይ ነው፡፡ የአንድ ንብረት ባለሀብት ማን ነው የሚለው የሚወሰነው ደግሞ ንብረት ከአንዱ ወደ ሌላው ለማስተላለፍ የሚያስችለው እንደ ሽያጭ ስጦታ ወዘተ የመሳሰሉት ህጋዊ ተግባሮች በህግ ፊት በሚፀና አኳኋን ተፈፅመው እንደሆነ እና በዚሁ አኳኋን በተፈፀመው ህጋዊ ተግባር የተነሣ በንብረቱ ላይ የባለቤትነት መብት ያገኘ ሰው ንብረቱን ካስተላለፈዉ ተፈጥሯዊም ሆነ የህግ ሰው ባሻገር ማናቸውንም 3ኛ ወገን ለመመለስ የሚያስችለውን የስመ ሀብት ዝውውር ሥርዓት ሁሉ ታከናውኖ እንደሆነ በፍ/ብ/ህግ ቁጥር


    1678 ፣1731፣1184፣1195 ተደንግጓል፡፡ አሁን የተያዘውን ጉዳይ ከእነዚህ ድንጋጌዎች አንፃር ስነየው ክርክር ያስነሰው ንብረት በ1ኛ ተጠሪ እና ጀ አስ ኤ ጀኔራል ትሬዲንግ መካከል በተደረገ ስምምነት መሠረት ይኽው ንብረት በዓይነት በመወሰኑ ወደ ከማህበሩ ገብቶ፤ ማህበሩ በዚሁ ንብነት ላይ መብትና ግዴታ ያቋቋመ ሲሆን ከዚሁ ንብረት ወደ ማህበሩ መግበት የተነሰ ለአስተላለፈውም ግዴታ ፈጥሮለታል ይህ በህግ የተፈቀደ ንብረት ሊተላለፍ የሚችለበት አንዱ ህጋዊ ተግበር ሲሆን ማህበሩ በዚሁ ንብረት ላይ የእኔ በይ በመጣ ለመመለስ ዋስትና የሆነውን የስመ ሀብት ዝውውር ሥርዓት ሁሉ ፈፅሟ፡፡ በዚህም መሠረት የዚሁ ንብረት የበላቤትነት መብት ያለው ይኽው ማህበር እንጂ ሌላ ማናቸውም ወገን ሊሆን አይችልም ይህን በንብረት ላይ ያለን የበለሀብትነት መብት ማህበሩ ያቋቋመው ፍ/ቤቱ በንብረቱ ላይ የዕግድ ትዕዛዝ ከመስጠቱ በፊት ነው ከዚህ በንብረቱ ላይ የበለቤትነት መብት ከቋቋመ በኃላ በዚህ በህግ ከቋቋመው ላይ የበለቤትናት መብቱ ተጠብቆም በንብረቱ ላይ የማዘዝ ወደ ሌላ 3ኛ ወገን የመስተልለፍ መብት ያለው ሲሆን ሌላ ማየናቸውም 3ኛ ወገን ይህንኑ ንብረት ለሚመለከት ከመህበሩ ጋር በሚያደረገው ህጋዊ ተግበር ወደ እራሱ ያዛወረው ከሆነ ንብረቱን ለማዘወር መብትና ስልጣን ከለው ወገን ያገኘ ነው ወይስ አይደለም የሚለውን ለመለየት ማህበር ንብረቱን በሸጠበት ጊዜ በንብረቱ ላይ የተመለከተውን ስመ ሀብትነት ምዝገባ የሚከተል እንጂ 3ኛ ወገን ከማህበሩ ጋር ግብይት የፈፀመበት ጊዜ ሊሆን አይችልም ከዚህ በላይ ንብረት ከንደኛው ወገን ወደ ሌላው ሊተላለፍ የሚችልበትን መንገድ በሚመለከት በተጠቀሱት ድንጋጌዎች የተቀመጡት ሁለት ቋሚ መሟያዎች ማናቸውም በንብረት ላይ ሊኖር የሚችለው ግብዓት በህግ ዋስትና ተሰጥቶት በህ/ሰብ ደረጃ ያለስጋት የሠለጠ ኢኮኒሚያዊ ግንኙት ለመፍጠር እንዲያስችል ነው፡፡ ከዚህ አንፃር የአሁን አመልካች የፍ/ቤቱ የዕግድ ትዕዛዝ ከተለለፈ በኃላ 3ኛው ተጠሪ ከማህበሩ ጋር የሽያጭ ውል ያደረገበትን ጊዜ ተንተርሰው የሚያቀረቡት ክርክር የህግ መሠረት ያለው ሆኖ አላገኘነውም ፡፡

     

    ከዚህም በቀር የማይንቀሳቀስ ንብረት በዓይነት ለመውጫ ወደ አክሲሆን ማህበር ወይም ወደ ኩባንያ ስለመዘወሩ በመመስረቻ ፅሑፍ ሰፍሮና በዚህ መስረጃ መዝገብ ጽ/ቤት ተመዝግቦ በማንቀሰቀስ ንብረት በመዝገብ ውስጥ መመዝገቡ ከተረጋገጠ የ3ኛ ወገኖችን ላይ ለመመለስ የሚያስችለው ሥርዓት መሟለቱን እንደሚያመለክት ይህ ለሰበር ሰሚ ችሎት ከዚህ ቀርቦ ተመሰሰይ በሆነው በሰበር መ/ቁ.. 27869 ትርጉም የሰጠበት ጉዳይ በመሆኑም ጭምር ከዕግድ ትዕዛዝ ጋር በተያየዘ የአሁን አመልካች የሚያቀርብበት ክርክር በስር ፍ/ቤቶች የተሰጠው ዳኝነት መሠረተዊ የህግ ስህተት የተፈፀመበት መሆኑን የሚያመለክት ህጋዊ መሰረት የለው ክርክር አይደለም ሌላውና ይህንኑ በቤት ቁጥር 2545 የተመለከተውን ቤት  አስመልክቶ የአሁን አመልካች ያቀረቡት ክርክር በዋጅ ቁጥር 2/3/92 ስለጋራ የበልና ሚስት ሀብት አስተዳደርና ጥበቃ በህጉ የተቀመጠውን  የተጋቢዎች የጋራ ስምምነትን አስፈላጊነት በመጥቀስ ነው፡፡


    የጋራ ሃብት የሆነን ንብረት አንደኛው ተጋቢ ያለ ሌላኛው ተጋቢ ስምምነት ለሌላ ሶስተኛ ወገን በሽያጭ ማስተላለፍ እንደማይችል በዚሁ የቤተሰብ ሕግ አንቀጽ 68 የተደነገገ ሲሆን፤ ይህ ድንጋጌ በይዘቱ የጋራ በሆነ ንብረት ላይ ተጋቢዎች እኩል መብት ያላቸው መሆኑን በህገ- መንግስቱ አንቀጽ 34(1) የተመለከተውን ህገ-መግስታዊ ድንጋጌ ተከትሎ የተደነገገ ሲሆን፤ በሌላ በኩል በአገር በማህበረሰብ ውስጥ ንብረትን አስመልክቶ የሚደረገው ግብይት ያለማነቆ በሰለጠ አኳኋን እንዲፈጸም ካልተደረገ በአገር የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ላይ ሊያደርስ የሚችለውን እንቅፋት በማየት ይህ ከላይ የተመከተው የጋራ ስምምነት አስፈላጊነት በሁኔታ ላይ እንዲመረኮዝ በማስፈለጉ ተከታይ በሆነው አንቀጽ 69 እንደተመለከተው አንደኛው ተጋቢ ያለፈቃዱ ንብረቱ በአንደኛው ተጋቢ ብቻ መሸጡን በተረዳ ጊዜ ይህ የሽያጭ ተግባር በህጉ የተሰጠውን መብት የጣሰ መሆኑን መነሻ አድርጎ በክስ አማካኝነት ማስፈረስ እንደሚቻል፤ ይህንኑ የማስፈረስ ተግባሩን ካልተጠቀመ፤ ወይም በህጉ በተቀመጠው የጊዜ ገደብ የማስፈረስ ጥያቄው ስልጣን ባለው ፍ/ቤት ካልቀረበ ግን አንደኛው ተጋቢ ብቻውን የፈጸመው ህጋዊ ተግባር እንደጸና እንደሚቀር እንጂ የጋራ ስምምነት ባለመኖሩ ምክንያት ብቻ ንብረቱ የተላለፈበትን ግብይት ወይም የሽያጭ ውል በዘፈቀደ በማናቸውም ጊዜ መቃወም እንደማይቻል ተደንግጓል፡፡ ስለሆነም የስር ፍ/ቤቶች በዚህ ረገድ የሰጡት ዳኝነት የህጉን ትክክለኛ አፈጻጸም የተከተለ እንጂ መሰረታዊ የሕግ ስህተት የተፈጸመ አይደለም፡፡

     

    የአሁን አመልካችም ይህንኑ ተገንዝበው ክርክራቸው በይግባኝ ደረጃ ለደረሰበት ጊዜ በዚሁ ስርዓት መሰረት በንብረት ላይ ያላቸውን መብታቸውን ለማስከበር ስልጣን ባለው ፍ/ቤት ክስ አቅርበው በክርክር ላይ የሚገኙ መሆኑን የገለጹ በመሆኑና ይህ ችሎም ለትክክለኛ ፍርድ አሰጣጥ ይህንኑ የተባለውን በመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት የቀረበውን የኮ/መ/ቁ. 194776 የሆነውን መዝገብም አስቀርበን እንደተመከትነው ጥያቄውን በዚያው አግባብ ማቅረባቸውን ተገንዝበናል፡፡ ይኸው ፍ/ቤትም ጉዳዩን ለጊዜው የዘጋው የፌዴራል ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤት በኮ/መ/ቁ. 125895 የቀረበለትን የይግባኝ ጉዳይ መርምሮ የመጨረሻ ዳኝነት እስኪሰጥበት ጊዜ  ድረስ በማገዱ ምክንያት በመሆኑና ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤት በጉዳዩ ላይ የመጨረሻ ዳኝነት የሰጠበት ጉዳይ ስለሆነ የስር ፍ/ቤቶች በፍርዳቸው ላይ እንደገለጹት መብታቸውን ከሚያስከብሩ በቀር በዚህ የጋራ ንብረት መሆኑ ተረጋግጦ የጋራ ሃብትን ለማከፋፈል እንዲቻል በቀረበው መዝገብ ላይ ወደ ሶስተኛ ወገን በሽያጭ አማካኝነት ተላልፎ የባልና ሚስት የጋራ ሃብት መሆኑ ያልተረጋገጠውን የቤት ቁጥር 2545 እንደጋራ ሃብት ሊቆጠር ይገባል በማለት የሚያቀ ርቡት ክርክር ተቀባይነት ያለውም አይደለም፡፡

     

    ሌላውና ለዚህ የሰበር ጉዳይ የክርክር ምክንያት የሆነው ለአሁን አመልካች ይግባኝ ሰሚ ከፍተኛው  ፍ/ቤት  አሻሽሎ  በወሰነላቸው  የአክሲዮን  ሼር  ድርሻ  ላይ  ያላቸውን     ሀብት


    የሚያገኙበትን ተጠቃሚ የሚሆንቨትን መንገድ ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤት የሚስማማ ከሆነ በአባልነት እንዲቀጥሉ ይህ ካልሆነም ተሽጦ የሸያጭ ድርሻ እንዲያገኙ በማለት በንግድ ህግ ቁጥር 523 እና ተከታዮቹ የተመለከተውን መሠረት በማድረግና በሰበር ሰሚው ችሎት በሰበር መ/ቁ.57288 የተሰጠውን ትዕዛዝ በመከተል የሰጠውን ዳኝነት አግባብነቱን አስመልክቶ ግራ ቀኙ ክርክር ያደረጉበት ጉዳይ ነው፡፡

     

    ይህንንም ጉዳይ እንደተመለከትነው በማናቸውም ምክንያት በፍ/ቤት በሚሰጥ  ፍርድ የሚረጋገጠው መብት ከተብ ወይም ከውል የመነጨውን መብት መኖርና አለመኖር አስመልክቶ እንዲህጉ አነጋገር ለማስረዳት የቀረበውን ክርክርና ክርክሩን አነጋገር ለማስረዳት የቀረበውን ክርክርና ክርክርን ለማስረዳት የቀረበውን መብት ወደ ተግባር ይህንኑ ከህግ እንዲያስችል ለመብት ምንጭ የሆነውን ህግ መሠረት በማድረግ ነው፡፡

     

    ከዚህም አንፃር ጉዳዩን አግባብነት ካለው ህግ ጋር ተገናዝቦ ሊታይ የሚገባው ነው፡፡

     

    አግባብነት ካላቸው ህጎች አንዱ ይኸው የአክቢዮን ድርሻ ግራ ቀኙ በጋብቻ ዘን በነበሩበት ጊዜ የተፈራ የጋራ ሀብት እንደመሆኑ መጠን በሀብቱ የባለእኩልነት ድርሻቸውን የሚቃረጋግጠው አዋጅ ቁጥር 213/92 አንቀጽ 62 አንዱ ሲሆን እንዲሁም ከዚሁ የጋራ ሀብት ነው፡፡ ከተባለው የሀብት ዓይነት አንፃር ሲታይ ደግሞ የዚህ የጋራ ሀብት የክፍፍል ሁኔታ የሀብቱን ጉዳይ ምክንያት በማድረግ በሚደነግገው በንግድ ህጉ አንቀጽ 523 የተመለከተው ድንጋጌ ደግሞ ሌላው ነው፡፡ ስለሆነም የዚህኑ ክፍፍል ሥርዓት የሚደረግበትን መንገድ በሚመለከት የሥር ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤት በንግድ ህጉ አንቀጽ 523 ሥር የተመለከተውን ድንጋጌ መሠረት ማድረግ የሚያነቀፍ አይደለም፡፡ ሆኖም ይህንኑ ድንጋጌ እንደሙሉ ይዘቱ አይነት ተፈፃሚ በማድረግ ስለሆነም የአሁኑ አመልካች በፍርድ በተረጋገጠላቸው የአክሲዮን ድርሻ ቫት መብት ላይ ከንግድ ህጉ አንቀጽ 523 አንፃር አየቶ መብቱን ለማረጋገጥ መነሻ ለሆኑ ከሚገባቸው የህጉ ክልሎች መካከል በንግድ ህጉ አንቀጽ 523/2/ እንደተመለከተው የአክሲዮን ማህበር መመሥረቻ ፅሑፍ የይዙቱ የአሁን አመልካች በማህበሩ አባልነት ተካተው በአባልነት ይህንኑ ለፍርድ በተረጋገጡባቸው የአክሲዮን ድርሻ ሀብት መገልገል የሚቻሉ መሆኑንና አለመሆኑን አስመልክቶ ምን እንደሚል ከመመስረቻ ፅሑፍ ጋር አገናዝቦ ከታየ በኋላ ሊታይ የሚገባው እንጂ ሆና እያለ ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤት የሰጠው ዳኝነት በዚህ ረገድ የተባለ ሆኖ አላገኘነውም ስለሆነም በዚሁ የነግድ ህግ ቁጥር 523/2/ ድንጋጌ ተትክከለኛ አፈፃፀሙን ተከትሎ ፍርድ በመስጠት  ረገድ የታየው ጉድለት ሊታረም የሚገባው ሆኖ አግኝተነዋል፡፡

     

    በዚህ ሁሉ ምክንያት የሚከተለውን ውሣኔ ሰጥተናል፡


     ው ሣ ኔ

     

    1. የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በኮ/መ/ቁ.61875በቀን 13/10/2004 ዓ5ም የሰጠውን ፍርድ እንዲሁም ይግባኝ ሰሚው ከፍተኛ ፍ/ቤት በኮ/መ/ቁ12559 ሰኔ 30 ቀን 2006 ዓ.ም የሰጠውን ፍርድ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ. 325/1/ መሠረት አሻሽለን ወስነናል፡፡

    2. በን/ስ/ላ/ከተማ ወረዳ 03 ክልል ውስጥ በመ/ቁጥር 2545 ተመዝገቦ የሚታወቀው  ቤት ላይ የባለቤትነት መብት ያለው የአሁን 3ኛ ተጠሪ አቶ ሐገስ አብዱራህማን ናቸው መባሉ በአግባቡ ነው ብለናል፡፡

    3. ለአሁን አመልካች በፍርድ በተረጋገጡላቸው የአክሲዮን ድርሻና መጠን ላይ ባላዠው የሀብት መብት ላይ መገልገል የሚቻልበት ማበህበሩ አባልነት ተካተው በአባልነት ነው ወይስ በአባልነት መገልገሉ የሚቻሉበት ህጋዊ ምክንያት ታይቶ በሐራጁ ተሽጦ ይህንኑ ሀብት እንደያገኙት ነው?የሚባለው ጭብጥ ከማህበሩ መመስረቻ ፅሑፍ ይዘት እና ከንግድ ህጉ አንቀጽ 523/2/ አንፃር ታይቶ ይወሰልን ዘንድ ብቻ መዝገቡን በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ቁ.343/1/ መሠረት ወደ ሥር ፈ/ቤት መልሰናል፡፡

    4. የዚህ ክርከር ውጤት እሰኪታወቅ ድረስ በሚል በዚህ የስር መዝገብ ቁጥር 103721 ተሰጥቶ የነበረው የዕግድ ትዕዛዝ ተነስቷል ይፃፍ፡፡

    5. የዚህ የሰበር ክርክር ጉዳይ ስላስከተው ወጪና ኪሣራ ግራ ቀኙ የየራሳቸው ይቻሉ፡፡ ብለናል፡፡

    መዝገቡ ተዘግቷል ወደ መዝገብ ቤት መልሰናል፡፡

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

     

     

    መ/ተ

  • አንድ ጋብቻ ሲፈርስ ንብረት ክፍፍልን በሚመለከት በእርቅ ውል ስምምነት በሽማግሌ የተደረገው እርቅ በፍ/ቤት ተመዝግቦ ከተዘጋ በኋላ እንደገና እንደ ባልና ሚስት አብረን እየኖርን ስለነበር በድጋሚ የንብረት ክፍፍል ይደረግ የሚል ጥያቄ አግባብነት ያለው ስላለመሆኑ፣

     

    የሰ/መ/ቁ. 105054

    ታህሳስ 22 ቀን 2008ዓ/ም

    ዳኞች፡- ተሻገር ገ/ስላሴ

     

    ሙስጠፋ  አህመድ ተፈሪ ገብሩ

    ሸምሱ ሲርጋጋ አብርሃ መሰለ

    አመልካች፡- ወ/ሮ ጌጤ እጅጉ -ቀርበዋል ተጠሪ፡-አቶ ብርሃኑ ተሰማ   -ቀርቧል

    መዝገቡን መርምረን የሚከተለውን ፍርድ ሰጥተናል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ የባልና ሚስት አፈፃፀም የሚመለከት ነው፡፡ ክርክሩ የተጀመረው በሌሙና ቢልቢሎ ወረዳ ፍርድ ቤት ተጠሪ ባቀረቡት የአፈፃፀም ክስ ነው፡፡ የአቤቱታውን ይዘትም ባጭሩ በመ/ቁ.343/96 በቀን 21/8/1996 ዓ/ም የነበረው ጋብቻ ሲፈርስ ንብረት ክፍፍል በሚመለከት በእርቅ ውል ስምምነት በሽማግሌ የተደረገው እርቅ በፍርድ ቤት ተመዝግቦ ተዘግተዋል፡፡ በዚሁ መሰረትም አንድ ወፍጮ ቤት፤ አንድ የዘይት መጭመቂያ ቤት እና አንድ ፒፒሻ ሽጉጥ የተጠሪው እንደሆነ ፍርድ ቤት በውሳኔው አረጋግጠዋል፡፡ ከውሳኔ በኃላ ታርቀን በባልና ሚስት ሆነን ስንኖር የዲገሉና ጢጆ ወረዳ ፍርድ ቤት መ/ቁ.19963 በቀን 9/8/ 2005ዓ/ም እና የአርሲ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመ/ቁ.6054 በቀን 19/10/05ዓ/ም በመ/ቁ. 343/96 በሆነው መዝገብ ላይ የተሰጠ የንብረት ክፍፍል እንዳይነካ ሲል ተወስነዋል፡፡ ስለዚህ የወፍጮ ቤት የነበረው አሁን የእንጨት መሰንጠቂያ የሆነው እና የዘይት መጭመቂያ ቤት ስም ይዛወርልኝ ፒፒሻ ሽጉጥ ታስረክበኝ ወይም ግምቱ 26,000 ብር እንዲከፈለኝ ሲሉ አፈፃፀም መጠየቃቸውን የሚያሳይ ነው፡፡ የአሁኑ አመልካችም በሰጡት መልስ በ1996 ዓ/ም ባልና ሚስት መሆናችን የማይካድ እውነት ነው፡፡ ትዳር ሲፈርስ ለኔ የተሰጠኝ የያዝኩት እንጂ የተጠሪ አይደለም፡፡ ያልተወሰነበት የሚፈፅምበት ነገር የለም፡፡ በእጄ የሌለውን ነገር ለመፈፀም አልገደድም፡፡ ጋብቻ ከፈረሰ የሰራሁት በስሜ ካርታ አውጥቼ የሚሰራበት ነው በማለት መልሳቸውን አቅርበዋል፡፡


    የስር ፍርድ ቤትም የግራቀኙን ማስረጃ በመመዘን በውላቸው መሰረት መፈፀም አለበት በማለት የዘይት መጨመቂያና የወፍጮ ቤት የነበረ ወደ እንጨት መሰንጠቂያ የተቀየረው ወደ ተጠሪ ስም እንዲዛወር እና ሽጉጥ እንዲያስረክቡ ትእዛዝ ሰጥተዋል፡፡

     

    በዚሁ ትእዛዝ ላይ ከአሁኑ አመልካች ይግባኝ የቀረበለት የአርሲ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤትም በሽጉጥ የተሰጠው ትእዛዝ በማሻሻል በሌሎቹ ንብረቶች ላይ የስር ፍርድ ቤት በማፅናት ትእዛዝ ሰጥተዋል፡፡ በመቀጠል ለኦሮሚያ ጠ/ፍ/ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ቅሬታ በአመልካች በመቅረቡ የግራ ቀኙ ክርክር ከሰማ በኃላ የዘይት መጭመቂያ በተመለከተ የተሰጠው ትእዛዝ በማፅናት፤ ወፍጮ ቤት የነበረው ወደ እንጨት መሰንጠቂያ ቤቱ የተጠሪ ነው፡፡ ነገር ግን ወደ እንጨት ድርጅት ሲቀየር ማሽኖቹና መሳሪያዎቹ የተገዙት እንደ ባልና ሚስት በአንድ ቤት  በሚኖርበት ጊዜ ስለሆነ ማሽኖቹና ዕቃዎቹ በባለሙያ ተገምቶ ግምቱ ወይም በጨረታ በመሸጥ እኩል እንዲካፈሉ በማለት በመሻሻል ውሳኔ ሰጥተዋል፡፡ የሰበር አቤቱታ የቀረበለት የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት የተፈፀመ መሰረታዊ የሕግ ስሕተት የለበትም ሲል አቤቱታው ሳይቀበለው በትእዛዝ ዘግቶታል፡፡

     

    የሰበር አቤቱታ የቀረበውም የስር ፍርድ ቤቶች በጉዳዩ ላይ የሰጡት ዳኝነት መሰረታዊ የሕግ ስሕተት የተፈጸመበት ስለሆነ ሊታረም ይገባል በማለት ነው፡፡ አቤቱታው  በሰበር ችሎት እንዲታይ የተያዘው ጭብጥ የእንጨት ድርጅት የተቋቋመው ወፍጮ ቤት የነበረው በ1996ዓ/ም በስምምነት ከተካፈሉ በኃላ እንደገና እንደባልና ሚስት አብረው ሲኖሩ መሆኑ ባልተካደበት በተደረገው የንብረት ከፍፍል ስምምነት መሰረት ቤቱ የተጠሪ ነው ተብሏል በሚል መነሻ አመልካች በአፈፃፀም መዝገብ ላይ ለተጠሪ እንድትለቅ የተሰጠው ትእዛዝ ህጋዊ የክርክር አካሄድና አመራርን የተከተለ መሆን አለመሆኑን ለመመርመር ነው፡፡ አቤቱታው ተመርምሮ ለሰበር ችሎቱ ሊታይ የሚገባ ነው ተብሎ በመታዘዙ ለተጠሪ ጥሪ ተደርጎላቸው መልሳቸውን ሰጥተዋል፡፡ አመልካችም የመልስ መልስ አቅርበዋል፡፡

     

    የጉዳዩ አመጣጥ ባጭሩ ከላይ እንደተገለፀው ሲሆን በዚህ መሰረትም በጭብጥነት በተያዘው ነጥብ ከግራ ቀኝ ወገኖች ክርክር፤ አቤቱታ ከቀረበበት ውሳኔ እና ከሕጉ ጋር አገናዝበን መርምረናል፡፡ ጉዳዩ የአፈፃፀም ከስ ስለሆነ በዋናው ጉዳይ የተሰጠው ውሳኔ መሰረት እንዲፈፀም መደረግ አለበት፡፡ በግራ ቀኙ የተማመኑበት ጉዳይ በመሐከላቸው የነበረው ጋብቻ በፍቺ ሲፈርስ የንብረት ክፍፍል በስምምነት በማድረግ በፍርድ ቤት ተቀባይነት አግኝቶ የፀደቀ ነው፡፡ ከፍቺ በኃላም እንደባልና ሚስት አብረው እየኖሩ እንደነበር በስር ፍርድ ቤቶች ያረጋገጡት ፍሬ ነገር ነው፡፡ በ2005ዓ/ም የአሁኑ ተጠሪ የፍቺ ክስ ለፍርድ ቤት አቅርበው ነገር ግን ጋብቻ የለም ግንኙታቸው


    እንደ ባልና ሚስት አብረው እንደሚኖሩ ሰዎች የሚባል ነው፡፡ በዚህ ጊዜ አብረው ያፈሩት ንብረት የጋራ እንዲሆንና በ1996 ዓ/ም የተደረገው ክፍፍል የተጠበቀ መሆኑን ውሳኔ ተሰጥተዋል፡፡

     

    ውሳኔው ይህ ከሆነ አፈፃፀሙን የዘይት መጭመቂያና የወፍጮ ቤት ለተጠሪ የደረሰው መሆኑን አመልካችም የራስዋ ድርሻ እንደያዘች ከስር መዝገብ መገንዘብ ይቻላል፡፡ ከፍቺ በኃላ አብረው መኖር ከጀመሩ ያፈሩት ንብረት መኖር አለመኖሩን ለማጣራትና ማስረጃ የመመዘን ስልጣን ባለቸው የስር ፍርድ ቤቶች ያረጋገጡት ወፍጮ ቤት የነበረው ወደ የእንጨት ድርጅት ሲቀየር የተለያዩ ማሽኖችና ዕቃዎች አብረው ያፈሯቸው እንደሆነ ነው፡፡ በዚህ መሰረትም አብረው ያፈሩት ማሽኖችና እቃዎች እኩል አንዲካፈሉ፤ ቤቱ ደግሞ ለተጠሪ እንዲሆን በማለት የተሰጠው ውሳኔ መሰረታዊ የሕግ ስሕተት ያለበት ሆኖ አልተገኘም፡፡ በዚሁ መሰረትም የሚከተለውን ውሳኔ ሰጥተናል፡፡

     

     ው ሳ ኔ

     

    1. የኦሮሚያ ጠ/ ፍ/ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በመ/ቁ.181913 በቀን 12/10/2006 ዓ/ም የስር

     

    ፍርድ ቤቶች ውሳኔ በማሻሻል ሰጠው ውሳኔ እና የኦሮሚያ ጠ/ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በመ/ቁ.185727 በቀን 22/11/2006ዓ/ም የሰጠው ትእዛዝ በፍ/ብ/ስ/ስ/ሕ/ቁ.348/1/ መሰረት አጽንተናል፡፡

     

    2. በዚህ ችሎት ተሰጥቶ የነበረው የእግድ ትእዛዝ ተነሰተዋል ለሚመለከተው አካል ይተላለፍ፡፡

     

    3. በዚህ ችሎት ለተደረገው ወጭና ኪሳራ የግራ ቀኙ ወገኖች የየራሳቸውን ይቻሉ፡፡ መዝገብ ተዘግተዋል፤ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ፡፡

     

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

     

     

    መ/ይ

  • የጋብቻ የምስክር ወረቀት ተገቢውን ስርዓት ተከትሎ የተሰጠ አይደለም ተብሎ መሰረዝ ጋብቻ አልነበረም ለማለት የሚያስችል ስላለመሆኑ፣

    Download Cassation Decision

  • ባል ወይም ሚስት የጡረታ አበል ተጠቃሚ ሆነው ባሉበት ፍቺ ቢከሰት የጡረታ መብት ተጠቃሚ የሆነው ባል ወይም ሚስት የጡረታ አበል ለባል ወይም ለሚስት ሊያካፍል የሚገባ ስላለመሆኑ ፣ የመንግስት ሠራተኞች ጡረታ አዋጅ ቁጥር 345/95 አንቀጽ 35

    Download Cassation Decision

  • የገጠር መሬት እንደሌላው ንብረት በመቁጠር ከቤተሰብ ህጉ አንጻር የሚታይ ስላለመሆኑ ፣ በአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ደብተር በአንድ ተጋቢ ስም ተዘጋጅቶ ከተሰጠ በኋላ ጋብቻ ቢፈፀምና ተጋቢዎቹ መሬቱን የጋራ ለማድረግ ሊስማሙ የሚችሉ ስለመሆኑ፣ የአማራ ክልል የገጠር መሬት አጠቃቀም አዋጅ ቁ. 133/1999 አንቀጽ 24/3/ ደንብ ቁ. 151/1999 አንቀጽ 20/6/

    Download Cassation Decision

  • በአባት በኩል ያለን መወለድ መቃወም የሚቻለው የልጁ አባት ነው ተብሎ በህግ ግምት የሚሰጠው ሰው እሱ የሞተ ወይም ችሎታ ያጣ እንደሆነ ከተወላጆቹ አንዱ የመካድ ክስ በማቅረብ መቃወም የሚችል ስለመሆኑ፣ የተሻሻለው የቤተሰብ ህግ አዋጅ ቁ. 213/1992/አንቀጽ 167፣174 እና 179

    Download Cassation Decision

  • እድሜው ያልደረሰ ልጅ የማይንቀሳቀስ ንብረት ለመሸጥ የሚያስችል የሞግዚት ስልጣን ይሰጠኝ ጥያቄ ፍ/ቤቶች የህፃንን መብትና ድህንነት ቅድሚያ እንዲሰጠው በማደረግ ሲወሰኑ ከዚሁ ጋር ተያይዞ የቀረበውን መሰረታዊ ጥያቄ እና አማራጭ መፍትሔ መኖሩን አለመኖሩን በማጣራት መወሰን ያለበት ሰለመሆኑ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ መንግሰት 36 (2) ፣ ፍ/ብ/ሕ/ቁ 280 እና 289(1) የቤተሰብ ህግ አዋጅ 213/1992 አንቀፅ 43

    Download Cassation Decision

  • የመጀመሪያ ሚስት በንብረትዋ ላይ ስምምነት ባላደረገችበት ፤ባል ሁለተኛ ሚስት ሲያገባ መቃወሚያ አላቀረበችም በማለት በንብረትዋ ላይም ስምምነት አድርጋለች በማለት በመደምደም ፤ሁለተኛ ሚስት እኩል እንድትካፈል በማለት የሚሰጥ ውሳኔ ህጋዊ ስላለመሆኑ

    Download Cassation Decision

  • የባልና ሚስት የጋራ ንብረት ነው የተባለ ንብረትን አፈፃፀምን በተመለከተ የንብረቱ ሕጋዊነት ላይ የሚመለከተው አስተዳደር አካል አግባብ ያለው ውሣኔ እስኪሰጥ ድረስ መሸጥ መለወጥ ባይቻልም ባለበት ሁኔታ የግራ ቀኙን እኩል ተጠቃሚነት በሚያረጋግጥ አግባብ በጋራ የሚያስተዳድሩበት ወይም ተከፋፍለው የሚጠቀሙበት ወይም አከራይተው ጥቅሙን እኩል የሚከፋፈሉበት ሁኔታ መመቻቸት ያለበት ስለመሆኑ የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕግ 386/2/

    Download Cassation Decision

  • ባ ል እና ሚስት በጋራ ሲጠቀሙበት የነበረ መሬት ጋብቻው በአንደኛው ተጋቢ ሞት የተቋረጠ ቢሆንም ሌላኛው ተጋቢ በሌላ ህጋዊ ምክንያት መብቱ እስካልተቋረጠ ድረስ ይዞታው በስሙ ተመዝግቦ ደብተር ለማግኘት እና በይዞታው ለመጠቀም የሚችል ስለመሆኑ፣ ሴቶች መሬትን በመጠቀም፤በማስተላለፍ፤በማስተዳደርና በመቆጣጠር ረገድ ከወንዶች ጋር እኩል መብት ያላቸዉ ስለመሆኑ የኢ.ፌ.ድ.ሪ ሕ/መ አንቀጽ 35/7/፣ የኦሮሚያ የገጠር መሬት አዋጅ ቁ. 130/99 አንቀጽ 6/3/ እና ደንብ ቁጥር 151/2005 አንቀጽ 15

    Download Cassation Decision

  • በመርህ ዯረጃ ጋብቻ በፌቺ እንዱፇርስ መጠየቅ የሚገባው ከባሌና ሚስቱ አንዯኛው ተጋቢ ወይም ሁሇቱም ቢሆንም በህግ አግባብ ተቀባይነት ያሇው ውክሌና ማስረጃ ጋር የሚቀርብ የፌቺ ጥያቄ ተቀባይነት ያሇው ስሇመሆኑ
    በፌ/ብ/ስ/ስ/ህ/ቁ.58፤ በፌ/ብ/ህ/ቁ.2199

    Download here