112956 labor dispute/ severance pay

አንድ ሠራተኛ ከስራ ከተሰናበተ በኋላ የአገልግሎት ክፍያ ከሚያገኝባቸው ሕጋዊ ምክንያቶች አንዱ በድርጅቱ ከ5 ዓመት በላይ አገልግሎ በገዛ ፈቃዱ ስራ መልቀቁ ሲረጋገጥ ብቻ ስለመሆኑ

አዋጅ ቁጥር 494/98 አንቀፅ 2/ሸ/

የሰ/መ/ቁ. 112956

 

ጥቅምት 22 ቀን 2008 ዓ.ም

 

ዳኞች፡- አልማው ወሌ

 

ዓሊ መሐመድ ተኽሊት ይመሰል እንዳሻው አዳነ ቀነዓ ቂጣታ

አመልካች፡- ሙስጠፋ ኑር ትዕም ቀረቡ

 

ተጠሪ፡- የኦሮሚያ መንገዶች ኮንስትራክሽን ኢንተርኘራይዝ ነ/ፈጅ ጋሻው ቡልቶ ቀረቡ መዝገቡ መርምረን ተከታዩን ፍርድ ሰጥተናል፡፡

 ፍ ር ድ

 

ጉዳዩ የአሰሪና ሰራተኛ የስራ ቅጥር ውል ማቋረጥን የሚመለከት ሲሆን ክርክሩ የተጀመረው የአሁኑ አመልካች በአሁኑ ተጠሪ በአዳማ ወረዳ ፍ/ቤት በተመሰረተው ክስ መነሻነት ነው፡፡ የክሱ ይዘትም፡- ከ1976 ዓ.ም ጀምሮ በኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን ተቀጥሮ በመስራት ላይ እያለ ወደ ኦሮሚያ መንገዶች ባለስልጣን ተለውጦ፣ ይህም ድርጅት ወደ ኢንተርኘራይዝ ተቀይሮ ብር 3666.00 በማግኘት ለ28 አመታት የሰራ ቢሆንም ከስራ ሳይቀር፣ ከስራ ለቀረበት ቀንም የሃኪም ማስረጃ አቀርቦ ሳለ ደመወዝም እየተከፈለው በነበረበት ሁኔታ በ18/12/2004 በፅሁፍ ከስራ መሰናበቱ እንደተገለፀለት፤ የተጠሪ ድርጊት ሕገ ወጥ በመሆኑ ወደ ስራ  እንዲመለስ እንዲወሰንለት ዘርዝሮ በአጠቃላይ 89‚328.20 ከወጪና ኪሳራ ከጠበቃ አበል  ጭምር እንዲከፈለው ዳኝነት መጠየቁን የሚያሳይ ነው፡፡

 

ተጠሪ በሰጠው መልስ አመልካች ከስራ የተሰናበተው ከ20/9/2004 ዓ.ም ጀምሮ በተከታታይ ለአምስት የስራ ቀናት ከስራ የጠፋ ስለሆነ ምክንያቱና ማስረጃውን በወቅቱ ባለማቅረቡ በአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀፅ 27/1//ለ/ የስራ ውል ማቋረጥ ሕጋዊ ነው፡፡ የስራ ስንብት ክፍያ አይመለከተውም በአዲሱ ድርጅትም 5 አመት አላገለገለም፡፡ የማስጠንቀቂያ ክፍያም   አይገባውም


የቀረ ደመወዝ የለውም፣ በአንፃሩ ማስጠንቀቂያ ሳይሰጥ ከስራ በመቅረቱ የአንድ ወር ደመወዝ በካሳ መልክ እንዲከፍል እንዲወሰን በማለት አቅርበዋል፡፡

 

የስር ፍርድ ቤትም የግራ ቀኙ ክርክር እና ማስረጃ ከመረመረ በኋላ አመልካች ከስራ  የቀረበት በቂ ምክንያት የማቅረብ ሕጋዊ ግዴታ እንዳለበት የሕክምና ማስረጃ ለተጠሪ አስተዳደር የስራ ክፍል መስጠቱን፤ ከታመመ በኋላ ተመልሶ ስራ መጀመሩን የተከራከረ ቢሆንም አላረጋገጠም፤ የስራ ውሉ የተቋረጠው በሕጉ አግባብ ነው፡፡ ክፍያ በተመለከተ ከ5 አመት በላይ በማገልገሉ እንዲሁም ክፍያው በወቅቱ ባለመፈፀሙ የአገልግሎት ክፍያ 36‚660 እና ቅጣት 10‚998 በድምር 47‚658.00፣ የጠበቃ አበል 10% ወጪና ኪሳራ 500.00 ተጠሪ  ለአመልካች እንዲከፍል ወስኗል፡፡

 

የአሁኑ ተጠሪ ውሳኔውን በመቃወም የይግባኝ ቅሬታው ለአዳማ ልዩ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ያቀረበ ቢሆንም በፍ/ስ/ስ/ሕ/ቁ. 337 መሰረት ተቀባይነት አላገኘም፡፡ የአሁኑ አመልካች የስር ፍ/ቤቶች ውሳኔ በመቃወም ለክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት አቅርቦ ግራ ቀኙ ካከራከረ በኋላ አመልካች በራሱ ፍላጎት 5 አመት ካገለገለ በኋላ መልቀቁን ያልተረጋገጠ መሆኑ በስር ፍርድ ቤቶች የተሰጡት ውሳኔዎች ሽሮ አመልካች የስራ ስንብት ክፍያ  ይሁን ክፍያ ለዘገየበት ተብሎ የሚከፈለው ነገር የለም ብሎዋል፡፡ ይህ የሰበር አቤቱታ የቀረበውም የስር ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ውሳኔ በመቃወም ለማስለወጥ ነው፡፡

 

አቤቱታው ተመርምሮ በዚህ ችሎት እንዲታይ የተደረገ ሲሆን ተጠሪም ጥሪ ተደርጎለት  ቀርቦ ግራ ቀኙ የፅሁፍ ክርክር ተለዋውጧል፡፡ የአመልካች የሰበር አቤቱታ መሰረታዊ ነጥብ፡- በተጠሪ ድርጅት ለረጅም ዓመታት አገልግሎት የአገልግሎት ክፍያ አይገባውም መባሉ የአሰሪና ሰራተኛ አዋጅ ቁጥር 377/96 እና ማሻሻያው አዋጅ ቁጥር 494/98 አንቀፅ 2/ሸ/ ያላገናዘበነው የሚል ይዘት ያለው ሲሆን ተጠሪ በበኩሉ አመልካች ያለበቂ ምክንያት በተከታታይ ለ5 ቀናት ከስራ በመቅረቱ ምክንያት ከስራ በመሰናበቱ የአገልግሎት ይሁን ክፍያ ዘገየበት ለተባለው ጊዜ የሚከፈለው ነገር የለም ተብሎ መወሰኑ የአዋጁን መንፈስ የተከተለ ነው የሚል መልስ አቅርበዋል፡፡ በአመልካች የቀረበው የመልስ መልስም አቤቱታውን የሚደግፍ ነው፡፡

 

የጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለመልኩ ከላይ የተገለፀው ሲሆን ይህ ችሎትም የግራ ቀኙ የፅሁፍ ክርክር፤ ለሰበር ችሎት መነሻ ከሆነው ውሳኔ እና አግባብነት ካላቸው ድንጋጌዎች እንዲሁም ጉዳዩ በሰበር ይመርመር ተብሎ ሲቀርብ ከተያዘው ጭብጥ አንፃር በሚከተለው መልኩ መርምሮታል፡፡


እንደመረመርነውም አመልካች እና ተጠሪ እያከራከረ ያለው መሰረታዊ ጭብጥ የሰራተኛውን በተከታታይ ለ5 ቀናት ከስራ መቅረት ተከትሎ የስራ ውል በመቋረጡ ምክንያት በአመልካች የቀረበው የክፍያ ጥያቄ ሕጋዊ መሰረት ያለው መሆን ያለመሆኑን ነው፡፡ አመልካች በሕመም ምክንያት ከስራ የቀረ ቢሆንም ከሕመሙ አገግሞ ወደ ስራ እንደተመለሰ የተከራከረ ሲሆን ተጠሪ በበኩሉ ያለ በቂ ምክንያት ለተከታታይ 5 የስራ ቀናት ከስራ በመቅረቱ በሕጉ አግባብ ከስራ ተሰናብቷል የሚል መልስ አቅርበዋል፡፡ በስር ፍርድ ቤት በፍሬ ነገር ደረጃ ፍ/ቤት ያረጋገጠው ጉዳይ አመልካች ለተከታታይ 5 የስራ ቀናት ከስራ የቀረበት በቂ ምክንያት ስለመኖሩ አላስረዳም የሚል ነው፡፡ አመልካች ከስራ የቀረበት ምክንያት በጤና እክል ስለመሆኑ በቅሬታ ከመግለፅ ውጪ የስር ወረዳ ፍርድ ቤት የፍሬ ነገር መጣራትና ማስረጃ ምዘና እና ድምዳሜ ተገቢ አለመሆኑን ስልጣን ባለው ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት ይግባኝ በማስቀረብ የሻረ ስለመሆኑ ያቀረበው ክርክር የለም፡፡ የስር ፍርድ ቤት የፍሬ ነገር እና ማስረጃ ምዘና ስርዓት እና ድምዳሜ በዚህ ሰበር ሰሚ ችሎት በድጋሚ የሚመረመር ባለመሆኑ እንዳለ የምንቀበለው ነው፡፡ ምክንያቱም ይህ ሰበር ሰሚ ችሎት በሕግ ተለይቶ የተሰጠው ስልጣን መሰረታዊ የሕግ  ስህተት የተፈፀመባቸው ጉዳዮችም መርምሮ ማረም ስለመሆኑ ከሕገ መንግስቱ አንቀፅ 80/3//ሀ/ እና አዋጅ ቁጥር 25/88 አንቀፅ 10 መሰረታዊ ድንጋጌዎች ይዘት የምንረዳነው ነው፡፡ በተያዘው ጉዳይ ተጠሪ አመልካችን ያለበቂ ምክንያት ተከታታይ 5 የስራ ቀናት ከስራ መቅረቱን በማረጋገጥ ያለማስጠንቀቂያ ከስራ እንዲሰናበት መወሰኑ አዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀፅ 27/1//ለ/ መሰረት ያደረገ ነው፡፡

 

የአመልካች የስራ ስንብት በሕጉ አግባብ የተደረገ መሆኑ ከተረጋገጠ ቀጥሎ መታየት ያለበት ጉዳይ ያለማስጠንቀቂያ ከስራ ለተሰናበተ ሰራተኛ የአገልግሎት ክፍያ እና ክፍያ ለዘገየበት በቅጣት መልክ የ3 ወር ደመወዝ ሊከፈል ይገባል ወይስ አይገባም? የሚለው ነው፡፡  በአመልካች እና በተጠሪ መካከል የነበረው የስራ ውል የተቋረጠው አመልካች ለተከታታይ 5 የስራ ቀናት በስራ ገበታው ባለመገኘቱ ያለማስጠንቀቂያ ነው፡፡ አመልካች ያለማሰጠንቀቂያ ከስራ ቢሰናበትም የአገልግሎት ክፍያ የማግኝት መብት እንዳለው አጥብቆ እየተከራከረ ነው፡፡ አንድ ሰራተኛ ከስራ ከተሰናበተ በኋላ የአገልግሎት ክፍያ ከሚያገኝባቸው ሕጋዊ ምክንያቶች አንዱ በድርጅቱ ከ5 አመት በላይ አገልግሎት በገዛ ፈቃዱ ስራ መልቀቁን ሲረጋገጥ ብቻ ነው፡፡ የአዋጅ ቁጥር 494/98 አንቀፅ 2/ሸ/ “ቢያንስ አምስት አመት በአሰሪው ዘንድ የስራ አገልግሎት ኖሮት በሕመም ወይም በሞት የስራ ውሉ ሲቋረጥ ወይም ስራው ከስልጠና ጋር የተያያዘ ለአሰሪው የውል ግዴታ ሳይኖርበት ስራው በገዛ ፈቃዱ” የለቀቀ የአገልግሎት ክፍያ እንደሚያገኝ ደንግጎአል፡፡ በተያዘው ጉዳይ አመልካች ከስራ የለቀቀው በገዛ ፈቃዱ /on his own initiative/ ሳይሆን አሰሪው ያለማሰጠንቀቂያ ከስራ ስለአሰናበተው ነው፡፡ አመልካች ከስራው በገዛ ፈቃዱ የለቀቀ መሆኑ ካልተረጋገጠ ደግሞ የስንብት ክፍያ የሚያገኝበት ሕጋዊ ምክንያት አይኖርም፡፡ በተያያዘ    ጉዳይ


ይህ ሰበር ሰሚ ችሎትም በሰ/መ/ቁ 25511 እና ሌሎች መዝገቦች አስገዳጅ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ የስር ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎትም አመልካች ስራውን በገዛ ፈቃዱ አለመልቀቁን በማረጋገጥ የስራ ስንብት ክፍያ እና ክፍያ ለዘገየበት የ3 ወር ደመወዝ አይገባም በማለት የስር ፍርድ ቤቶች ውሳኔ መሻሩ ሕጉን በአግባቡ ተርጉሟል ከሚባል በስተቀር በጉዳዩ መሰረታዊ የሕግ ስህተት መፈፀሙን አያሳይም፡፡ በእነዚህ ሁሉ ምክንያት የስር ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የበታች ፍርድ ቤቶች የፈፀሙት ሰህተት ማረሙ በአግባቡ በመሆኑ ጉዳዩ መሰረታዊ የሕግ ስህተት ያልተፈፀመበት ነው ለማለት የሚችል ሆኖ ስላልተገኘ ተከታዩን  ውሳኔ ተሰጥቷል፡፡

 

 ው ሳ ኔ

 

1. የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በሰ/መ/ቁ 181962 በ2/06/2007 ዓ.ም የስር የአዳማ ልዩን ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመ/ቁ 18244 በ08/09/2006 ዓ.ም የሰጠው ትዕዛዝ በመሻር፤ የአዳማ ወረዳ ፍርድ ቤት በመ/ቁ 73239 በ30/07/2006 ዓ.ም የሰጠው ውሳኔ በመሻር የሰጠው ፍርድ በድምፅ ብልጫ ፀንቷል፡፡

2.  የአመልካች የስራ ውል የተቋረጠው ያለማስጠንቀቂያ መሆኑ በመረጋገጡ በአዋጅ  ቁጥር

494/98 አንቀፅ 2/ሸ/ የተመለከተው ክፍያ እና ክፍያ ለዘገየበት አይመለከተውም ተብሎ መወሰኑ በሕጉ አግባብነት ነው ብለናል፡፡

3. ግራ ቀኙ በዚህ ፍ/ቤት ያወጡት ወጪና ኪሳራ የየራሳቸውን ይቻሉ ብለናል፡፡ መዝገቡ ውሳኔ ያገኘ በመሆኑ ወደ መ/ቤት ይመለስ ብለናል፡፡

 


 

 

ብ/ይ


የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት