family law

  • Family law

    Minors

    Guardianship and tutorship

    Power of tutor

    Councilof family

    Cvil code art. 301

    አንድ ሞግዚት አካለመጠን ያልደረሰን ልጅ በማስተዳደር ስልጣኑ ክርክር የሚደረግበት ጥቅም ከ300 ብር ያነሰ ካልሆነ በቀር ያለ ቤተዘመድ ምክር ጉባኤ ፈቃድ ምንም ግልግል መፈጸም የማይችል ስለመሆኑ፣

    የፍ/ህ/ቁ. 301

    100426

  • Family law

    Minors

    Guardianship and tutorship

    Power of tutor

    council of family

    Civil code art. 301

    አንድ ሞግዚት አካለመጠን ያልደረሰን ልጅ በማስተዳደር ስልጣኑ ክርክር የሚደረግበት ጥቅም ከ300 ብር ያነሰ ካልሆነ በቀር ያለ ቤተዘመድ ምክር ጉባኤ ፈቃድ ምንም ግልግል መፈጸም የማይችል ስለመሆኑ፣

    የፍ/ህ/ቁ. 301

    100426

  • Family law

    Divorce

    Indeminties upon divorce

    Federal family code art. Art. 81(2), 84

    በጋብቻ ፍቺ ጊዜ ለፍችው ምንክያት የሆነው በደል ተፈጽሞባታል ተብሎ ለአንደኛው ወገን ካሣ የሚከፈለው እንዲከፍለው ዳኝነት ሲጠይቅና ካሣውም የሚወሰነው ለፍትህ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ብቻ ስለመሆኑ፣ የተሻሻለው የፌደራል የቤተሰብ ህግ አዋጅ ቁጥር 213/92 አንቀጽ 81/2/፣84

    101552

  • የአንድ ድርጅት የበላይ ኃላፊ ለሠራተኞች ለጡረተኞች የክፍያ ጭማሪን በተመለከተ በስሩ ለሚገኙ እንደየገቢያቸው መጠን እያስወሠኑና እያስፀደቁ የጭማሪ ክፍያ እንዲያደረጉ ያስተላለፈው ውሣኔ በሙሉ በስር በሚገኙት ድርጅቶች ላይ ተፈፃሚ ሊሆን የሚገባው ሥለመሆኑ፣

  • ሌሎች ሰዎች በሚከራከሩበት መዝገብ ለክርክሩ መነሻ ከሆነው ንብረት ውስጥ በአንደኛው ወገን ጠያቂነት የታገደን ንብረት ሌላ ሶስተኛ ወገን ለሌላ እዳ አፈፃፀም ንብረቱን ሥለምንፈልገው በፍ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 158 መሰረት የተሰጠው የዕግድ ትዕዛዝ ይነሳልኝ ብሎ አቤቱታ አቅርቦ ዕግዱ ሊነሳ አይገባም ተብሎበሚሰጠው ብይን ላይ ይግባኝ በሚጠየቅበት ወቅት ከስረ ነገር ውሳኔ በፊት ይግባኝ የሚባልበት አይደለም ሊባልየማይቻል ስለመሆኑ፡-

     

    የፍ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ. 320(3)

     

    የሰ/መ/ቁ.101632 መጋቢት 4 ቀን 2007 ዓ.ም.

    ዳኞች፡- መድሕን ኪሮስ

     

    አልማው ወሌ ሡልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመሰል

    አመልካች፡- አቢሲኒያ ባንክ አ.ማ. - ነገረ ፈጅ ብርሃኑ አሰፋ ቀረቡ ተጠሪ፡- ወ/ሮ ዘይቱ ከማል - የቀረበ የለም

    መዝገቡ ተመርምሮ የሚከተለው ፍርድ ተሰጥቶአል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    በዚህ መዝገብ አመልካች የሰበር አቤቱታ ያቀረበው ተጠሪ እና የተጠሪ ባለቤት ናቸው የተባሉት አቶ ኑሪ ከማል እንደቅደም ተከተላቸው ከሳሽ እና ተከሳሽ በመሆን ከፍቺ ጋር ተያይዞ ክርክር እያካሄዱ በነበረበት መዘገብ የአሁኑ አመልካች በተከሳሹ ግለሰብ ላይ በሌላ መዝገብ ላስፈረደው የብድር ዕዳ በንብረቱ ላይ አፈጻጸሙን መቀጠል ያስችለው ዘንድ ከፍቺ ክርክር ጋር ተያይዞ በተከሳሹ ስም ተመዝግቦ በሚታወቀው ቤት ላይ በከሳሽ ጠያቂነት የተሰጠው የዕግድ ትዕዛዝ እንዲነሳለት በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር 158 መሰረት ያቀረበውን አቤቱታ እና በአቤቱታው ላይ የተሰጠውን መልስ የመረመረው የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ዕግዱ ሊነሳ አይገባም በማለት የሰጠው ብይን እና ብይኑ ጊዜያዊ አገልግሎት ያለው በመሆኑ ከስረ ነገሩ ፍርድ በፊት ይግባኝ የሚባልበት አይደለም በማለት ይግባኝ ሰሚው የፌዴራል ከፍተኛ  ፍርድ ቤት የሰጠው ትዕዛዝ መሰረታዊ የሕግ ስህተት የተፈጸመባቸው በመሆኑ ሊታረሙ ይገባል በማለት ሲሆን አቤቱታው ተመርምሮ ጉዳዩን በተመሳሳይ ጉዳይ በፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ችሎት አስቀድሞ በመዝገብ ቁጥር 86400 በ21/09/2005 ዓ.ም. ከተሰጠው አስገዳጅ የሕግ ትርጉም አንጻር ተጠሪዋ ባሉበት ለማጣራት ይቻል ዘንድ ጉዳዩ ለሰበር ክርክር እንዲቀርብ በመደረጉ ግራቀኙ የጽሁፍ ክርክር ተለዋውጠዋል፡፡የጉዳዩ አመጣጥ እና የክርክሩ ይዘት ከላይ የተመለከተው ሲሆን እኛም በጉዳዩ እልባት ማግኘት የሚገባው ዕግዱ ሊነሳ አይገባም በማለት በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የተሰጠው ብይንጊዜያዊ አገልግሎት ያለው በመሆኑ ከስረ ነገሩ በፍርድ በፊት ይግባኝ የሚባልበት አይደለም በማለት በይግባኝ ሰሚው ፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የተሰጠው ትዕዛዝ ሕጋዊ መሰረት ያለው ነው ወይስ አይደለም? የሚል ነጥብ መሆኑን በመገንዘብ አቤቱታ የቀረበበት ውሳኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈጸመበት መሆን አለመሆኑን ከዚሁ ነጥብ አንፃር መርምረናል፡፡


    በዚህም መሰረት በአንድ ፍርድ ቤት በተሰጠ የማገጃ ትዕዛዝ ላይ ቅሬታ የተሰማው ወይም አላግባብ ነው የሚል ወገን ለፍርድ ቤቱ አቤቱታውን ያቀረበ እንደሆነ እና የቀረበውም አቤቱታ በቂ ምክንያት የሚያስገኝ መሆኑን የተረዳው እንደሆነ ፍርድ ቤቱ ሰጥቶት የነበረውን የማገጃ ትዕዛዝ እንዲሻሻል፣እንዲነሳ ወይም ጨርሶ እንዲሰረዝ ለማድረግ እንደሚችል በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር 158 ስር ተደንግጎ የሚገኝ ሲሆን የማገጃ ትዕዛዝ ይነሳልኝ ጥያቄው በመዝገቡ ተከራካሪ በሆነ ወገን ወይም የክርክሩ አካል ባልሆነ 3ኛ ወገን ጭምር ሊቀርብ የሚችል ነው፡፡በተያዘው ጉዳይ የዕግድ ይነሳልኝ ጥያቄው የቀረበው በአመልካች ባንክ ሲሆን ተጠሪዋ ባለቤቴ ናቸው ከሚሏቸው ግለሰብ ጋር በሚከራከሩበት መዝገብ ባንኩ ተከራካሪ ወገን አይደለም፡፡ይግባኝ ሰሚው ከፍተኛ ፍርድ ቤት በትዕዛዙ ላይ እንደገለጸው በድንጋጌው  ንዑስ ቁጥር (4) ስር በተጠቀሱት ትዕዛዞች ላይ ካልሆነ በቀር ማናቸውም ፍርድ ቤት ክርክሩን በሚሰማበት ጊዜ በጉዳዩ ላይ ጊዜያዊ አገልግሎት ያለው ትዕዛዝ ሲሰጥ፣ቀነ ቀጠሮ ሲወስን፣በመጀመሪያ ደረጃ በሚቀርብ መቃወሚያ ላይ ተገቢ መስሎ የታየውን ትዕዛዝ ሲሰጥ በእንደእነዚህ ዓይነቶቹ ትዕዛዞች ላይ ከስረ ነገሩ ፍርድ በፊት ይግባኝ ማለት የማይቻል ስለመሆኑ እና ነገር ግን ለክርክሩ የመጨረሻ የፍርድ ውሳኔ ከተሰጠ በኃላ ከዚህ በላይ በተገለጹት ትዕዛዞች ላይ ቅሬታ ያለው ሰው ቅሬታውን በስረነገሩ ፍርድ ላይ ከሚያቀርበው ቅሬታ ጋር አጠቃሎ የማቅረብ መብት ያለው ስለመሆኑ በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር  320(3) ስር ተደንጓል፡፡

     

    ከድንጋጌው አነጋገር በግልጽ መገንዘብ እንደሚቻለው ድንጋጌው ጊዜያዊ አገልግሎት ባላቸው ትዕዛዞች ላይ ከስረ ነገሩ ፍርድ በፊት ይግባኝ ማቅረብን የከለከለው የስረ ነገሩ ጉዳይ ውሳኔ ባገኘ ጊዜ በስረ ነገሩ ፍርድ ላይ ቅሬታ ያለው ወገን በስረ ነገሩ ፍርድ ላይ ብቻ ሳይሆን አስቀድሞ በተሰጠበት ጊዜያዊ አገልግሎት ባለው ትዕዛዝ ላይም ቅሬታውን አጠቃሎ የማቅረብ መብት ስለተጠበቀለት ነው፡፡ በተያዘው ጉዳይ አመልካች ባንክ የስረ ነገሩ ጉዳይ ተከራካሪ ወገን ስላልሆነ የስረ ነገሩ ክርክርም ሆነ በክርክሩ መጨረሻ የሚሰጠው ውሳኔ አይመለከተውም፡፡ የዕግድ ትዕዛዙ ሊነሳ ይገባል ወይስ አይገባም? በሚለው ጭብጥ ላይ የሚሰጠው ትዕዛዝ ከአመልካች አንጻር እንደመጨረሻ ፍርድ የሚቆጠር እንጂ ጊዜያዊ አገልግሎት ያለው ትዕዛዝ ነው የሚባል አይደለም፡፡በመሆኑም ይግባኝ ሰሚው ከፍተኛ ፍርድ ቤት ጉዳዩን ከዚህ አንጻር በመገንዘብ የቀረበለትን የይግባኝ ቅሬታ መርምሮ ተገቢ ነው የሚለውን ትዕዛዝ ሊሰጥበት ሲገባ ብይኑ ጊዜያዊ አገልግሎት ያለው በመሆኑ ከስረ ነገሩ ፍርድ በፊት ይግባኝ የሚባልበት አይደለም በማለት መዝገቡን ዘግቶ መመለሱ የፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር 320(3) ድንጋጌን እና ዓላማ እና ይዘት ያገናዘበ ነው ለማለት የሚቻል ሆኖ አልተገኘም፡፡

     

    ሲጠቃለል የእግድ ትዕዛዙ ሊነሳ አይገባም በማለት በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የተሰጠው ብይን ጊዜያዊ አገልግሎት ያለው በመሆኑ ከስረ ነገሩ ፍርድ በፊት ይግባኝ የሚባልበት አይደለም በማለት የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሰጠው ትዕዛዝ መሰረታዊ የሕግ ስህተት የተፈጸመበት ሆኖ በመገኘቱ የሚከተለው ውሳኔ ተሰጥቷል፡፡

     

     ው ሳ ኔ

     

    1.የዕግድ ትዛዙ ሊነሳ አይገባም በማለት በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 206422 በ03/07/2006 ዓ.ም. የተሰጠው ብይን ጊዜያዊ አገልግሎት ያለው ስለሆነ ከስረ ነገሩ ፍርድ በፊት ይግባኝ የሚባልበት አይደለም በማለት የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ


    ቤት በመዝገብ ቁጥር 150681 በ15/08/2006 ዓ.ም. የሰጠው  ትዕዛዝ    በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር 348(1) መሰረት ተሽሮአል፡፡

    2.የዕግድ ትዛዙ ሊነሳ አይገባም በማለት በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 206422 በ03/07/2006 ዓ.ም. የተሰጠው ብይን ከአመልካች ባንክ አንጻር የመጨረሻ እንጂ ጊዜያዊ አገልግሎት ያለው ትዕዛዝ አይደለም በማለት ወስነናል፡፡

    3.ይህንኑ ተገንዝቦ የቀረበለትን ይግባኝ በፍሬ ጉዳዩ ረገድ መርምሮ ተገቢውን ውሳኔ ወይም ትዕዛዝ ይሰጥበት ዘንድ ጉዳዩ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት እንዲመለስ በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር 341(1) መሰረት ወስነናል፡፡በዚሁ መሰረት ተገቢውን መፈጸም ያስችለው ዘንድ የውሳኔው ግልባጭ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይላክ፡፡

    4. የሰበር ክርክሩን ወጪና ኪሳራ ግራ ቀኙ የየራሳቸውን ይቻሉ፡፡

    5.  ውሳኔ ያገኘ በመሆኑ መዝገቡ ተዘግቷል፡፡

     


     

    ብ/ይ


    የማይነበብ አምስት ዳኞች ፊርማ አለበት::

  • “ስለሠራተኛ ዕድገት አሰጣጥ ስርዓት” በሚል በአዋጁ የተገለፀው ሀረግ ሊተረጎም የሚገባው ከአንድ የሠራተኛ የስራ መደብ ወደ ሌላ የሠራተኛ የስራ መደብ የሚፈፀም የዕድገት አሰጣጥ ስርዓት በሚል መልኩ ስለመሆኑ፣

     

    በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጽ 142(1)(ሠ)

    የሰ/መ/ቁ. 101579

     

    ህዳር 24 ቀን 2007 ዓ.ም.

     

    ዳኞች፡-አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሱልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመስል

    አመልካቾች፡-

     

    1.  አቶ ገ/መድህን አስፋው           13. አቶ ዓለማየሁ ተሾመ

    2.  አቶ ተ/ፃዲቅ ደምሴ               14. አቶ ላቀው እርገጤ

    3.  አቶ ዳኜ አየለ                   15. አቶ ተሾመ አግዴ

    4.  አቶ ወ/ሚካኤል ዋቄ              16. አቶ አየለ ይግለጡ

    5.  አቶ አምሃ ኃ/ስላሴ17. አቶ ይትባረክ ሰሜ                              ከጠበቃ

    6.  አቶ አመሃ መላኩ ኃ/ማሪያም       18. ወ/ሮ ፀሐይ አእምሮ              መስፍን

    7.  አቶ ደምሴ ድጋፌ              19.ወ/ሮብዙነሽ ማሞ                አለማየሁ

    8.  አቶ ግዛው አስረስ               20. ወ/ሮ በቀለች ጐዳና              ጋር ቀረቡ

    9.  አቶ ታደሰ ገ/መድህን21. አቶ ኃ/ማሪያም ገና

    10. አቶ ወረደወርቅ ጥላሁን           22. አቶ ገብረ ተ/ኃይማኖት

    11. አቶ ከበደ አወቀ                 23. አቶ ፍቃደስላሴ ርዳው

    12. አቶ ይልማ ጨርቆስ              24. አቶ ሞገስ ኃ/መስቀል

     

     

    ተጠሪ፡- ትንሳኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት ነ/ፈጅ ሳህለማሪያም ወዳጆ ቀረቡ፡፡

     

    መዝገቡ ተመርምሮ ተከታዩ ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    የሰበር አቤቱታው የቀረበው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በፍ/ብ/ይ/መ/ቁጥር 128430  ታህሳስ 7 ቀን 2006 ዓ/ም የሰጠው ውሳኔ በፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በመ/ቁ.96927 ግንቦት 05 ቀን 2006 ዓ/ም በዋለው ችሎት ተሽሮ በተሰጠው ውሳኔ መሰረታዊ የሆነ የህግ ስህተት ተፈጽሟል በማለት አመልካቾች የሰበር አቤቱታ ስላቀረቡ ነው፡፡ ጉዳዩ የጡረታ ደመወዝ ማስተካከያ አስተዳደራዊ ውሳኔ ተግባራዊ ይሁንልን ጥያቄ የሚመለከት ሲሆን ክርክሩ የተጀመረው በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ነው፡፡ በዚህ ፍርድ ቤት የአሁኑ አመልካቾች ከሳሾች ተጠሪ እና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ጠቅላይ ቤተክህነት ጽ/ቤት ተከሳሾች ነበሩ፡፡


    የአመልካቾች የክስ ይዘትም፡- መንግስት ለመንግስት ሰራተኞች እና ጡረተኞች ህዳር 23 ቀን 2003 ዓ/ም በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባስተላለፈው ውሳኔ የደመወዝ ማስተካከያ ማድረጉን ተከትሎ የኢትዮጵያ ኦርተዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቅድስ ሲኖዶስም በስሩ ላሉት ሰራተኞች የደመወዝ ማስተካከያ እንዲደረግ ወስኖ ባለበት ሁኔታ የአሁኑ ተጠሪ እምቢተኛ መሆኑን ዘርዝረው የጡረታ ደመወዝ ማስተካከያ እንዲከፈል ይወሰንልን የሚል ነው፡፡ የስር ተከሳሾች ጉዳዩ በፍርድ ሊታይ የማይችልበትን ምክንያትና አመልካቾች ክሱን ለማቅረብ መብትና ጥቅም የሌላቸው መሆኑን የሚያሳዩ ነጥቦችን በመጥቀስ በመጀመሪያ ደረጃ መቃወሚያነት የተከራከሩ ሲሆን በፍሬ ነገር ደረጃም ለአመልካቾች የጡረታ ደመወዝ እንዲስተካከል የሚደረግበት የህግ ወይም የህብረት ስምምነት የሌለ መሆኑን ዘርዝረው ክሱ ውድቅ ሊሆን ይገባል በማለት ተከራክረዋል፡፡

     

    ጉዳዩን በመጀመሪያ ደረጃ የተመለከተው ፍርድ ቤትም የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኃላ ጉዳዩን መርምሮ የአመልካቾች ጥያቄ ተቀባይነት የለውም ሲል ወስኗል፡፡ በዚህ ውሳኔ የአሁኑ አመልካቾች ቅር በመሰኘት ይግባኛቸውን ለፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቅርበው ፍርድ ቤቱ ግራ ቀኙን ከሰማ በኃላ ጉዳዩን መርምሮ የአመልካቾች ጥያቄ በፍርድ ቤት ሊታይ እንደሚችል፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ መጋቢት 20 ቀን 2003 ዓ/ም ባደረገው ስብሰባ ማስተካከያውን ለሰራተኞችና ለጡረተኞች በወሰነው መሰረት የአሁኑ ተጠሪም ለአሁኑ አመልካቾች ማስተካከያው ሊከፍል ይገባል በማለት ደምድሞና ሊጨመር የሚገባውን ማስተካከያ በመቶኛ ገልጾና ይኼው ማስተካከያ የሚመለከተውን የጡረታ ደመወዝ መጠን ለይቶ ለአመልካቾች ተጠሪ የጡረታ ማስተካከያውን ሊከፍል ይገደዳል በማለት ወስኗል፡፡ በዚህ ውሳኔ የአሁኑ ተጠሪ ቅር በመሰኘት ይግባኙን ለፌዴራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት አቅርቦ ግራ ቀኙ ከተከራከሩ በኃላ ፍርድ ቤቱ ጉዳዩን መርምሮ ተጠሪ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ስር የሚተዳደር ነገር ግን በራሱ ገቢ ራሱን የሚያስተዳድር  ስለመሆኑ ግራ ቀኙን ያላከራከረ ጉዳይ መሆኑን፣ ለአመልካቾች ክስም ሆነ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ውሳኔ መሠረት የሆነው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ስለሠራተኞቹና ጡረተኞቹ የደሞዝ ማስተካከያ አስመልክቶ መጋቢት 20 ቀን 2003 ዓ.ም ያስተላለፈው ውሳኔ መሆኑን በዚህ ውሳኔ ጥናት ተደርጐ የቀረበውን ጉባኤው ያፀደቀላቸው ሲሆን ሌሎቹ ማለትም በትንሳኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤትና ጐፋ ጥበበ እድ ካህናት ማሰልጠኛ ለሚገኙት ሠራተኞችና ጡረተኞች እንደየገቢያቸው መጠን እየወሰኑ ለአስተዳደሩ አቅርበው  እያስፀደቁ  ተግባራዊ እንዲሆን ሲል ቋሚ ሲኖዶሱ መወሰኑን የስብሰባ ቃለ ጉባኤ ይዘት በግዴታ የማያመላክት መሆኑን ከዚህ መረዳት የሚቻለው የጉባኤው ውሳኔ የአሁኑን ተጠሪን በተመለከተ ቀጥተኛ ተፈጻሚነት እና አስገዳጅነት ያለው የደመወዝ ማስተካከያ ያለማድረጉ መሆኑን ይልቁንም ተጠሪ በራሱ ገቢ የሚተዳደር ከመሆኑ አንፃር እንደራሱ ገቢ መጠን ጥናት አድርጐ በአስተዳደሩ አፅድቆ ተግባራዊ ማድረግ የሚያስችል አቅጣጫ የተቀመጠለት መሆኑን እንጂ አስገዳጅ የሆነ ውሳኔ ያልተሰጠ መሆኑን የሚያስገነዝብ መሆኑን ደምድሞ አመልካቾች ባለው የቤተክርስቲያን መዋቅር መሰረት አቤቱታቸውን ከማቅረብ ውጪ በፍርድ ሃይል ተፈጻሚ የሚሆን ውሳኔ የላቸውም በማለት የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሰጠውን ውሳኔ ሽሮ የፌደራሉ መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የሰጠውን ውሳኔ በውጤት ደረጃ በመቀበል አፅንቶታል ፡፡ የአሁኑ  የሰበር አቤቱታ የቀረበውም ይህንኑ የይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤትን ውሳኔ በመቃወም ለማስለወጥ ነው፡፡


    የአመልካች የሰበር አቤቱታ መሰረታዊ ይዘትም፡-የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሲኖዶስ መጋቢት 20 ቀን 2003 ዓ/ም ያሳለፈው ውሳኔ ተጠሪ ገቢውን መሰረት በአደረገ መልኩ ለሰራተኞቹም ሆነ ለጡረተኞቹ በተሰራው ስኬል መሰረት ማስተካከያውን እንዲያደርግ የሚል ሁኖ እያለ ተጠሪ ለሰራተኞቹ ብቻ ማስተካከያውን አድርጐ ለጡረተኞቹ ሳያደርግ ሲቀር የቀረበውን ክስ የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ያላግባብ ተርጐሞ ተጠሪ የሚገደድበት ውሳኔ የለም በማለት መወሰኑ መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት ነው የሚል ሲሆን ለተጠሪ ጥሪ ተደርጎለት ቀርቦ ግራ ቀኙ በፅሁፍ እንዲከራከሩ ተደርጓል፡፡

     

    የጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለመልኩ ከላይ የተገለፀው ሲሆን ይህ ችሎትም የግራ ቀኙን ክርክር ለሰበር አቤቱታ መነሻ ከሆነው ውሳኔ እና አግባብነት ካላቸው ድንጋጌዎች ጋር በማገናዘብ ጉዳዩን በሚከተለው መልኩ መርምሮታል ፡፡እንደመረመረውም ጉዳዩ ለዚህ ችሎት ሲቀርብ በጭብጥነት የተያዘው ነጥብ ፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ መጋቢት 20 ቀን 2003 ዓ/ም በሰጠው ውሳኔ የአሁኑን ተጠሪ በስም ጠቅሶ ለሠራተኞቹና ጡረተኞቹ እንደየገቢያቸው መጠን እየወሰኑ ለአስተዳደሩ እያስፀደቁ ክፍያው እንዲፈፀም በማለት በሰጠው ውሳኔ መሰረት ለሰራተኞቹ የጭማሪውን ክፍያ እንደአደረገ ተጠሪ ግንቦት 27 ቀን 2005 ዓ/ም በሰጠው መልስ ማመኑ ከተረጋገጠ የሲኖዶሱ ውሳኔ ለጡረተኞች ብቻ ተፈፃሚነት የለውም በሚል የተሰጠውን ውሳኔ አግባብነት ለመመርመር ተብሎ ነው፡፡ እኛም ጉዳዩን ከዚሁ ጭብጥ አንፃር ብቻ መመርመሩን ተገቢነት ያለው ሆኖ አግኝተናል፡፡

     

    ከክርክሩ ሂደት መገንዘብ የተቻለው ተጠሪ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ሥር የሚተዳደር ነገር ግን በራሱ ገቢ ራሱን የሚያስተዳድር ስለመሆኑ ግራ ቀኙን ያላከራከ ጉዳይ መሆኑን፣ ለአመልካቾች ክስም ሆነ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ውሳኔ መሠረት የሆነው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ስለሠራተኞቹና ጡረተኞቹ የደሞዝ ማስተካከያ አስመልክቶ መጋቢት 20 ቀን 2003 ዓ.ም ያስተላለፈው ውሳኔ መሆኑን፣ በዚህ ውሳኔ ጥናት ተደርጎ የቀረበውን ጉባኤው ያፀደቀላቸው ሲሆን ሌሎቹ ማለትም በትንሳኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤትና በጎፋ ጥበብ እድ ካህናት ማሰልጠኛ ለሚገኙት ሠራተኞችና ጡረተኞች እንደየገቢያቸው መጠን እየወሰኑ ለአስተዳደሩ አቅርበው እያፀደቁ ተግባራዊ እንዲሆን ሲል ቋሚ ሲኖዶሱ መወሰኑና ይህንኑ ተከትሎም ተጠሪ ለሠራተኞቹ የጭማሪውን አስተካክሎ ክፍያውን ሲፈፅም ለአሁኑ አመልካቾች፤ የድርጅቱ ጡረተኞች ግን ማስተካከያውን ሳያደርግ የቀረ መሆኑን አምኖ የሚከራከር መሆኑን ነው፡፡ የፌዴራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ተጠሪ ለክሱ ኃላፊነት የለበትም ወደሚለው ድምዳሜ የደረሰው የሲኖዶሱ የስብሰባ ቃለ ጉባኤ ይዘት ተጠሪ ለጡረተኞች ማስተካከያ እንዲያደርግ በግዴታየሚያመላክት አይደለም የሚለውን ምክንያት በመያዝ መሆኑን ከውሳኔው ይዘት ተረድተናል፡፡

     

    በመሰረቱ ተጠሪ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስተዋህዶ ቤተክርስቲያን ስር የሚተዳደር ከሆነ የቤተክርስቲያኗ የበላይ የሆነው አካል የሰጠውን ውሳኔ ያለምንም ልዩነት ተግባራዊ ማድረግ አለበት፡፡ ተጠሪ ለአመልካቾች የጡረታ ደመወዝ የሚከፍለው በግራ ቀኙ መካከል በነበረው የአሰሪና ሰራተኛ ግንኙነት ሲሆን ይህ ክፍያ የሚፈፀመውም የአሰሪና ሰራተኛ ግንኙነቱ በጡረታ ምክንያት በመቋረጡ ምክንያት በመሆኑና ገንዘቡም ከአሰሪውና ከሠራተኞቹ ደመወዝ ተቆርጦ ሲጠራቀም ከነበረው መሆኑ ግልፅ ነው፡፡ የጡረታ ደመወዝ ሕጋዊ በሆነ የአስተዳደራዊ ውሳኔ መሰረት እንዲስተካከል ሲደረግ በሠራተኛው ስም የተቀመጠው ገንዘብ መኖሩን ብቻ በማረጋገጥ ነው ተብሎ አይታሰብም፡፡ ጡረታ አግባብነት ላላቸው የህብረተሰቡ ክፍሎች የኑሮ ዋስትና


    ለመስጠት እንዲያስችል ተብሎ ተግባራዊ የሚደረግ ማህበራዊ መድህን መሆኑ ግልፅ ነው፡፡ የኑሮ ዋስትና የመስጠት መሰረታዊ አላማው የሚሳካው ደግሞ ተጨባጭነት ያለውን ወይም የሕብረተሰቡን ነባራዊ ሁኔታ ባገናዘበ መልኩ ማስተካከያው ሲደረግ መሆኑ የሚታመን ነው፡፡ በዚህ አግባብ የጡረታም ሆነ የደመወዝ ማስተካከያም ተግባራዊ እየተደረገ ያለበት ሁኔታ መኖሩም ግንዛቤ የሚወሰድበት ነው፡፡ የተጠሪ መስሪያ ቤት ባለቤት የሆነውና የበላይ የአስተዳደር አካሉ መንግስት ለሠራተኞቹና ለጡረተኞቹ ያደረገውን ማስተካከያ መነሻ በማድረግና በራሱ ፍላጎት ለተጠሪ ሠራተኞቹና ጡረተኞች ማስተካከያውን እንዲያደርግ፣ ማስተካከያው ደግሞ የተጠሪን ገቢ መሰረት አድርጎ ሊሰራእንደሚገባና በሚመለከተው አካል  እየጸደቀ ተግባሪዊ እንዲሆን የሚገልፅ ውሳኔ መጋቢት 20 ቀን 2003 ዓ/ም መወሰኑም ይህንኑ የሚያሳይ ነው ፡፡ ተጠሪ የሲኖዶሱ ውሳኔ በተጠሪ ላይ አስገዳጅነት የለውም በማለት የሚያቀርበውና በፌዴራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ተቀባይነት ያገኘው መከራከሪያ ነጥብ ሲታይም ተጠሪው ገቢውን መሰረት ያደረገ ጥናት አደርጎ ለቋሚ እና ለኮንትራት ሰራተኞቹ ማስተካከያውን አድርጎ ክፍያውን መፈጸሙን ያመነበትን አግባብ ክፍያውን ለጡረተኞቹ ላለማድረግ ህጋዊ ምክንያት የነበረው መሆን ያለመሆኑን አጣምሮ ያላገናዘበ ሆኖ አግኝተናል፡፡ምክንያቱም የተጠሪ የበላይ አስተዳደር የሆነው አካል ለተጠሪ የሰጠው አስተዳደራዊ አቅጣጫ የማስተካከያው ክፍያ ተጠቃሚዎችን ሠራተኞች ወይም ጡረተኞች በሚል ጭምር ተለይቶ እንዲፈፀም የሚያሳይ ሳይሆን ለሠራተኞቹም ሆነ ለጡረተኞቹ ልዩነት ሳይደርግ የድርጅቱን ገቢ መሰረት አድረጎ ማስተካከያውን እንዲሰራና ተግባራዊ እንዲያደርግ የሚያስገነዝብ ነው፡፡ ስለሆነም ተጠሪ የበላይ አካልን ውሳኔ ተግባራዊ ላለማድረግ ሕጋዊ መከራከሪያ ሊሆነው የሚችለው የድርጅቱ የገቢ ሁኔታ ብቻ ነው፡፡ሆኖም ተጠሪ ለሰራተኞቹ ማስተካከያውን ያደረግው የድርጅቱን ገቢ መሰረት አድርጎ ስላለመሆኑ ያቀረበው ክርክርና ማስርጃ የለም፡፡የተጠሪ የበላይ አካል የሆነው ሲኖዶሱ ማስተካከያው ለተጠሪ ድርጅት ሰራተኞች ጡረተኞች እንዲደረግ ውሳኔ ከሰጠና ለሠራተኞቹ የተጠሪን ገቢ መሰረት ባደረግ መልኩ ማስተካከያው መደረጉ እስከተረጋገጠ ድረስ ደግሞ ተጠሪ ጡረተኞችን ብቻ በመለየት የማስተካከያው ተጠቃሚ ሊሆኑ አይችሉም የሚልበት አግባብ የለም፡፡ተጠሪ የበላይ አካሉን ውሳኔ ተቀብሎ ለሠራተኞቹ ብቻ ማስተካከያ አድርጎ ለጡረተኞቹ ብቻ ማስተካከያውን የተወበት አካሄድ ተቀባይነት እንዲኖረው ማድረግ በውጤት የጡረታ መብት ለኑሮ ዋስትና ያለው ሕጋዊ ፋይዳ ዋጋ የሚያሳጣው ነው፡፡

     

    አመልካቾች ተጠሪ ላይ በመደበኛ ፍርድ ቤት ክስ የመሰረቱት ከተጠሪ ጋር መስርተው የነበሩት ሕጋዊ የአሰሪና ሠራተኛ ግንኙነት ተቋርጦ የአመልካቾች የጡረታ መብት ተከብሮላቸው የጡረታ መብት ተካፋይ ሁነው ባሉበት ሁኔታ በአስተዳደራዊ ውሳኔ መሰረት የተከበረላቸው የጡረታ ማስተካከያ ክፍያ ተግባራዊ ሊሆን አልቻለም በሚል በመሆኑ ጉዳዩ ኃይማኖታዊ ስርዓትን ተከትሎ ትርጉም የማያስፈልገው በመሆኑ ጉዳዩ በፍርድ ቤት መታየቱ በሕገ መንግስቱ አንቀጽ 11 ስር የተደነገገውን መርህ የማይነካ መሆኑን ተገንዝበናል፡፡ሕጋዊ የሆነ አስተዳደራዊ ውሳኔ ተግባሪዊ ሳይሆን ሲቀር በፍርድ ቤት ውሳኔ አስገዳጅነትእንዲኖረውማድረግም በኢ.ፌ.ዲ.ሪፐብሊክ ሕገ-መንግስት አንቀጽ 37 እና 25 የተረጋገጡትን ፍትህ የማግኘት መብትና የእኩልት መብት ውጤታማ የሚያደረግ ነው ተብሎ ይታሰባል፡፡ስለሆነም የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት የተጠሪ የበላይ አካል የሆነው ሲኖዶስ መጋቢት 20 ቀን 2003 ዓ.ም በሰጠው ውሰኔ የአሁኑን ተጠሪ በስም ጠቅሶ ለሠራተኞቹና ጠረተኞቹ እንደየገቢያቸው መጠን እየወሱነ ለአስተዳደሩ እያስፀደቁ ክፍያው እንዲፈፀም በማለት በሰጠው ውሳኔ መሰረት ተጠሪ ለሰራተኞቹ የጭማሪው  ክፍያ  እንደ  አደረገ  ግንቦት  27  ቀን  2005  ዓ/ም  በሰጠው  መልስ  ማመኑ


    በተረጋገጠበት ሁኔታ የሲኖዶሱ ውሳኔ ለጡረተኞች ብቻ ተፈፃሚነት የለውም የሚል ትርጉም የሚያሰጥ ውሳኔ መስጠቱ በክርክሩ ሂደት የተረጋገጡትን ፍሬ ነገሮችን ያላገናዘበ  ሆኖ ስለአገኘነው በጉዳዩ ላይ የተሰጠው ውሳኔ መሰረታዊ የሆነ የህግ ስህተት ያለበት ነው በማለት ተከታዩን ወስነናል፡፡

     

     ው ሳ ኔ

     

    1.  የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በመ/ቁጥር 96927 ግንቦት 05 ቀን

    2006 ዓ/ም የሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰረት ተሽሯል፡፡

    2. የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመ/ቁጥር 128430 ታህሳስ 07 ቀን 2006 ዓ/ም የሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰረት ጸንቷል፡፡

    3. ተጠሪ ለአመልካች ጥያቄ ኃላፊ ነው ተብሎ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ሲኖዶስ መጋቢት 20 ቀን 2003 ዓ/ም በወሰነው መሰረት ከጥር ወር 2003 ዓ/ም ጀምሮ የጡረታ ማስተካከያ አበል ሊከፈላቸው ይገባል በማለት ወስነናል፡፡ ስሌቱን በተመለከተ የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ባስቀመጠው መሰረት ነው ብለናል፡፡

    4. ለክርክሩ የወጣውን ወጪና ኪሳራ የየራሳቸውን ይቻሉ ብለናል፡፡ መዝገቡ ተዘግቷል፤ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ ብለናል፡፡

     


     

    እ/እ


    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማአለበት፡፡

  • የፌዴራል ከፍተኛ ፍ/ቤት የሠራተኛ ጉዳይ ወሣኝ ቦርድ የወሰነውን ጉዳይ በይግባኝ ሲያይ የህግ ስህተት መኖሩን እና አለመኖሩን ከማረጋገጥ ባለፈ የፍሬ ጉዳይ እና የማስረጃ ምዘናን በተመለከተ የማየት እና የማረም ስልጣን የሌለው ስለመሆኑ፣

     

    አንድ አሠሪ የሠራተኛ ቅነሳ በሚል ምክንያት ሠራተኞችን ከሥራ ሲያሰናብት በአዋጁ የሠራተኛን ቅነሳ በተመለከተ የተቀመጡትን ድንጋጌዎች መሠረት ማድረግ ያለበት ስለመሆኑ፣

     

    አዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 28(2)(ሐ) ፣29፣140

     

    የሰ/መ/ቁጥር 102512

     

    ታህሳስ 10 ቀን 2007 ዓ.ም.

     

    ዳኞች፡-አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሡልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመሰል

     

     

    አመልካቾች፡-

     


    1.አቶ ብርሃኑ ቢኔ

    2. አቶ ሞላ ደሴ

    3. አቶ ተስፋዬ ሐበና

    4. ወ/ሮ ጀማነሽ መንገሻ

    5. አቶ ጉልትነህ ታደሰ

    6. አቶ ወርቁ አይዴ

    7. አቶ መኮንን ሙሉ

    8. ወ/ሮ ክብነሽ ዋጤሮ

    9. ወ/ሮ ታየች አሰፋ

    10. አቶ አጫ አይሳሮ

    11. ወ/ሮ ፀዳለ ቸችሮ

    12. አቶ ሐይሌ አረጋዊ

    13. አቶ ጠብቀው ሳንፎ

    14. ወ/ሮ ለተብርሃን መኮንን

    15. አቶ ዘሪሁን ደግፌ

    16. አቶ በርሔ አሰፋ

    17. ወ/ሮ አቦነሽ ሳካሎ

    18. አቶ ዋህድ ካሳዬ


    19. አቶ ግዛቸው ካሳ

    20. አቶ አበራ ሐይሌ

    21.አቶ ደምመላሽ ካሳዬ        ደመነ ቱኔ

    22. ወ/ሮ መስከረም ካንኮ       የ34ቱም

    23. አቶ ሙሉጌታ መቺሶ         ጠበቃ

    24. አቶ ሱልጣን ሐሰን

    25. አቶ ጌታሁን ሐይሌ

    26. ወ/ሮ ዓለሚቱ ገብሬ

    27. ወ/ሮ ባዩሽ በቀለ

    28. አቶ ደሳለኝ ትንታግ

    29. አቶ እንግዳ እሸቱ

    30. ወ/ሮ ጀማነሽ መንገሻ

    31. ወ/ሮ አየለች ባልቻ

    32. አቶ መንበረ ጌታቸው

    33. አቶ መተኪያ ፀጋዬ

    34. አቶ አብዮት ጌታሁን


    ተጠሪ፡-የአርባ ምንጭ ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካአ/ማ- ነ/ፈጅ ሹፋያን ሱልጣን ቀረቡ

     

    መዝገቡን መርምረን የሚከተለውን ፍርድ ሰጥተናል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ የቀረበው አመልካቾች የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 139151 ግንቦት 25 ቀን 2006 ዓ/ም የሰጠው ውሳኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት ያለበት ስለሆነ በሰበር ታይቶ እንዲታረምልን በማለት ያቀረቡትን የሰበር አቤቱታ አጣርቶ ለመወሰን ነው፡፡ ጉዳዩ የስራ ውል መቋረጥን የሚመለከት ነው፡፡ ጉዳዩ በመጀመሪያ የታየው በደቡብ ክልል የሠራተኛ ጉዳይ ወሳኝ ቦርድ ነው፡፡ በክልሉ የሠራተኛ ጉዳይ ወሳኝ ቦርድ አመልካቾች ከሳሽ ተጠሪ ተከሳሽ በመሆን ተከራክረዋል፡፡

    1. አመልካቾች በተጠሪ ድርጅት ከሃያ ዓመት በላይ በታማኝነት ያገለገሉ መሆኑን ገልፀው ተከሳሽ (ተጠሪ) አዲስ መዋቅር አስጠንቻለሁ በማለት የስራ መደባችሁ ታጥፏል በሚል ሰበብ በሕግ አግባብ የሰራተኛ ድልድልና ምደባ ሳያደርግ ቅነሳ በሚል ሀሰተኛ ምክንያት መጋቢት 10 ቀን 2005 ዓ/ም እና ሚያዝያ 10 ቀን 2005 ዓ/ም በተፃፈ ደብዳቤ የስራ ውላችንን ከሕግ ውጭ ያቋረጠ በመሆኑ ስንብቱ ሕገ ወጥ ነው ተብሎ ይወሰንልን በማለት አመልክተዋል፡፡ ተጠሪ በተከሳሽነት ቀርቦ ጉዳዩ በመደበኛ ፍርድ ቤት የሚታይ ነው በማለት የመጀመሪያ የክስ መቃወሚያ ያቀረበ ሲሆን፣ በአማራጭ ሰራተኞቹ የተቀነሱት የድርጅቱ መዋቅር በገለልተኛ ባለሙያ ከተጠና በኋላ ከሳሾች መዋቅሩ የሚጠይቀውን መስፈርት ባለማሟላታቸው ያልተደለደሉ በመሆኑና ድልድሉ የሰራተኞች ተወካይ ባለበት በግልጽ መስፈርት ሰራተኞች ተወዳድረው የተመደቡ በመሆኑ ስንብቱ ሕጋዊ ነው በማለት ተከራክሯል፡፡

    2. የክልሉ ሠራተኛ ጉዳይ ወሳኝ ቦርድ የግራ ቀኙን ክርክርና ማስረጃ ከሰማ በኋላ ተጠሪ አመልካችዎችን ከስራ ያሰናበተበት አግባብ የአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጽ 29 የተደነገጉትን መስፈርቶች የማያሟላና ከሕግ ውጭ በመሆኑ ተጠሪ በሕጉ መሰረት ሁሉንም ሰራተኞች ባሳተፈ መልኩ እንደገና የሰራተኛ ድልደላ ይፈፅም፡፡ ተጠሪ እንደገና ለመደልደል ካልፈለገ ስንብቱ ሕግን ያልተከተለ በመሆኑ ከሳሾችን/ አመልካቾችን/ ወደ ስራ ይመልስ፡፡ ተጠሪ ከሳሾችን ወደ ስራ ካልመለሰ በሕግ አግባብ ካሳ በመክፈል እንዲያሰናብታቸው በማለት ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ ተጠሪ በዚህ ውሳኔ ቅር በመሰኘት ይግባኝ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቅርቧል፡፡ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኋላ ይግባኝ ባይ (ተጠሪ) ሠራተኞችን የደለደለው በትምህርት ደረጃ፣ በስራ ልምድ፣ በማህደር ጥራትና የስራ አፈፃፀም ውጤት በመሆኑ ስንብቱ በህግ አግባብ የተፈፀመ ነው በማለት የክልሉ ሰራተኛ ጉዳይ ወሳኝ ቦርድ የሰጠውን ውሳኔ ሽሮታል፡፡

    3. አመልካቾች ሰኔ 27 ቀን 2006 ዓ/ም በተፃፈ የሰበር አቤቱታ ተጠሪ ያስጠናው መዋቅር ከደረጃ 1 እስከ ደረጃ 20 የስራ መደብ ያለው ቢሆንም ሰራተኛ ድልድል የፈፀመው ከደረጃ 1 እስከ ደረጃ 12 ባለው የሥራ መደብ ላይ ብቻ መሆኑ ተረጋግጧል፡፡ ተጠሪ ካሉት 674 ሠራተኞች አስር ፐርሰንት የሚሆኑ አልቀነሰም፡፡ መዋቅሩ ሠራተኞች ቁጥር እንዲጨምር የሚያደርግ ነው፡፡ ተጠሪ እኛን በሕግ አግባብ በማወዳደር ሠራተኞችን ያልደለደለ መሆኑን በማረጋገጥ ቦርዱ የሰጠውን ውሳኔ ይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት አላግባብ መሻሩ መሰረታዊ የሕግ ስህተት ያለበት ስለሆነ በሰበር ታይቶ እንዲታረምልኝ በማለት አመልክተዋል፡፡ ተጠሪ ጥቅምት 3 ቀን 2007 ዓ/ም በተፃፈ መልስ ከደረጃ 1 እስከ ደረጃ 12 ባለው የስራ መደብ


    ሠራተኞች በአግባቡ ተወዳድረው ተመድበዋል፡፡ ከደረጃ 13 እስከ ደረጃ 20 ያለው የስራ መደብ የስራ መሪዎችን የሚመለከት ነው፡፡ ከስራ የተሰናበቱት ሰራተኞች 10% በታች መሆኑ ስንብቱን ህገ ወጥ አያደርገውም የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ  ቤት የሰጠው ውሳኔ የሕግ ስህተት የሌለበት በመሆኑ እንዲፀናልኝ በማለት ተከራክረዋል፡፡ አመልካቾች ጥቅምት 14 ቀን 2007 ዓ/ም በተፃፈ የመልስ መልስ ተጠሪ ከደረጃ 1 እስከ ደረጃ 12 ሰራተኞች ተወዳድረው ተመድበዋል ያለው ሀሰት ነው፡፡ ምክንያቱም በድርጅቱ ንብረትና ፋይናንስ ዘርፍ የሥራ መደቦች ላይ የተሰማሩ ሠራተኞች በድልድል አልተካተቱም፡፡ ተጠሪ ከደረጃ 13 እስከ ደረጃ 20 ያሉት የስራ መደቦች የስራ መሪ የስራ መደብ ነው በማለት ያቀረበው ክርክር እውነትነት የሌለው ነው፡፡ ስለዚህ ስንብቱ ሕገ ወጥ ነው ተብሎ እንዲወስንልን በማለት ተከራክረዋል፡፡

    4. ከስር የክርክሩ አመጣጥና በሰበር ግራ ቀኙ ያቀረቡት የፅሁፍ ክርክር ከላይ የተገለፀው ሲሆን እኛም የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ተጠሪ የአመልካቾችን የስራ ውል ያቋረጠው በሕግ አግባብ ነው በማለት የሰጠው ውሳኔ ሕጋዊ መሰረት አለው ወይስ የለውም? የሚለውን ጭብጥ በመያዝ ጉዳዩን መርምረናል፡፡

    5. ጉዳዩን እንደመረመርነው ከላይ የተገለፀውን ጭብጥ ለመወሰን፣ በመጀመሪያ ፍሬ ጉዳይ የማጥራትና ማስረጃ የመመዘን ስልጣን በሕግ የተሰጠው የሠራተኞች ጉዳዮች ወሳኝ ቦርድ የግራ ቀኙን የሰውና የፅሁፍ ማስረጃ ሰምቶ፣ መርምሮና መዝኖ የደረሰባቸውን የፍሬ ጉዳይ መደምደሚያዎች ከሕጉ ድንጋጌ ጋር ማገናዘብ አስፈላጊ ነው፡፡ የክልሉ ሠራተኛ ጉዳይ ወሳኝ ቦርድ ተጠሪ ምርታማነትን ለማሳደግና አሰራር ለመለወጥ አዲስ መዋቅር ያስጠና መሆኑና በአዲሱ መዋቅር መነሻ በማድረግ አመልካቾችን ከስራ የቀነሰ መሆኑን አረጋግጧል፡፡ ሆኖም ተጠሪ ካሉት 674 ሠራተኞች ቅነሳ በሚል ምክንያት ከስራ ያሰናበተው ከአስር ፐርሰንት የማይሆኑ ሠራተኞችን እንደሆነ አረጋግጧል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የስራ ምደባው ከተወዳደሩ በኋላ በውድድሩ ያላለፉ ሠራተኞችን ተጠሪ ከደረጃቸው ዝቅ አድርጎ የመደበና ያላሰናበተ መሆኑን በማስረጃ መረጋገጡንና የሥራ ድልድሉ ሁሉንም ሰራተኞች የማይመለከት በተለይ ንብረትና ፋይናንስ ክፍል የሚሰሩ ሰራተኞችን የማይመለከት መሆኑን  በማስረጃ እንደተረጋገጠ ቦርዱ በግልጽ በውሳኔው ውስጥ አስፍሯል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ከደረጃ 13 እስከ ደረጃ 20 ያሉ የስራ መደቦች ሰራተኞች በውድድር ያልተመደቡባቸው መሆኑን፣ በማስረጃ እንደተረጋገጠ በውሳኔው አስፍሯል፡፡ ይህም የሠራተኛ ቅነሳ ነው በማለት ተጠሪ ያከነወነው ተግባር የአሰሪና ሰራተኛ አዋጅ ቁጥር 377/1996 መሰረት አያሟላም በማለት የሠራተኛ ውሳኝ ቦርዱ መደምደሚያ ላይ ደርሷል፡፡

    6. ከላይ የሰራተኛ ወሳኝ ቦርዱ በማስረጃ ያረጋገጣቸው ጉዳዬች አግባብነት ካላቸው የሕግ ድንጋጌዎች አንጻር መርምረናል፡፡ በመጀመሪያ በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጽ 28 ንዑስ አንቀጽ 2(ሐ) አሰሪው የድርጅቱን አቋም ወይም የስራ እንቅስቃሴ ምክንያት በማድረግ በተለይም የድርጅቱን ምርታማነት የማሳደግ አሰራር ዘዴዎች ለመለወጥ ወይም አዲስ ቴክኖሎጂ ለመጠቀም ሲባል ሠራተኞችን የመቀነስ ውሳኔ ሊያስተላልፍ እንደሚችልና ማስጠንቀቂያ ሰጥቶ ሰራተኞችን ሊያሰናብት እንደሚችል ይደነግጋል፡፡ በዚህ መስረት የስራ መደብ መሰረዝ ሠራተኞችን የሚነካ ሲሆንና በአዋጁ አንቀጽ 29(1) መሰረት የሠራተኛ ቅነሳ የሚያስከትል ሲሆን የስራ ውሉ የሚቋረጠው በአዋጅ አንቀጽ 29 ንዑስ  አንቀጽ 3 ሁኔታዎች በማሟላት መሆን እንዳለበት በአዋጁ አንቀጽ 28 ንዑስ አንቀጽ 3 ተደንግጓል፡፡

    7. ከዚህ አንፃር ሲታይ አመልካች ባስጠናው አዲስ መዋቅር ምክንያት ካሉት ሠራተኞች አስር ፐርሰንት የሚሆኑትን የስራ ውል ያላቋረጠና ይህም በአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ  29(1)


    የተቀመጠውን መስፈርት የማያሟላ መሆኑ ተረጋግጧል፡፡ አመልካች ካሉት ሠራተኞች አምስት ፐርሰንት የማይሆኑትን የስራ ውል ለማቋረጥ በአዋጅ አንቀጽ 29 ንዑስ አንቀጽ 3 የተደነገገውን አስገዳጅ መስፈርት የመከተል ግዴታ አለበት፡፡ ሆኖም አመልካች በመጀመሪያ ደረጃ ከአመልካቾች ያነሰና ዝቅተኛ የሥራ አፈጻጸም ያላቸውን ሠራተኞች በተጠሪ ኃላፊዎች ትዕዛዝ በስራ እንዲቀጥሉ አድርጎ አመልካቾችን ያሰናበተ መሆኑ የሰራተኛ ወሳኝ ቦርድ የግራ ቀኙን ምስክሮች የሰራተኛ ደልዳይ ኮሜቴ አባላት የምስክርነት ቃል በመስማትና በመመዘን አረጋግጧል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የስራ ድልድልና ቅነሳው ተጠሪ ያሉትን ሁሉንም የስራ መደቦች የማያካትትና ሁሉንም የስራ ክፍሎች የማይመለከት መሆኑ በማስረጃ ተረጋግጧል፡፡በአጠቃላይ ተጠሪ የአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 29/3/ የተደነገጉትን መስፈርቶች በመጠቀም የአመልካቾችን የስራ ውል ያላቋረጠ መሆኑ ፍሬ ጉዳይ የማጣራት እና ማስረጃ የመመዘን ስልጣን ባለው የሠራተኛ ጉዳይ ቦርድ ተረጋግጧል፡፡

    8.  የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሠራተኛ ጉዳይ ወሳኝ ቦርድ ያረጋገጣቸውን ፍሬ  ጉዳዮች እና የደረሰበትን የፍሬ ጉዳይ እና የማስረጃ መደምደሚያ በመቀበል፤ሕጉን መሰረት ያደረገ መሆኑን ከመመዘን ያለፈ፣ የፍሬ ጉዳይና የማስረጃ ምዘና ስህተት በይግባኝ የማየትን የማረም ሥልጣን ከአዋጅ አንቀጽ 140 ንዑስ አንቀጽ 1 አልተሰጠውም፡፡ ከዚህ አንፃር ሲታይ የአሰሪና ሠራተኛ ጉዳይ ወሳኝ ቦርድ ተጠሪ ከደረጃ 1 እስከ ደረጃ 12 ሰራተኞች ለመደልደል በተጠቀማቸው አራት መስፈርት ከአመልካቾች ጋር ተወዳድረው ዝቅተኛ ነጥብ ያመጡ ሰዎች በስራ እንዲቀጥሉ ያደረገና የተሻለ ውጤት ያመጡትን አመልካቾች ያሰናበተ መሆኑን በማስረጃ እንዳረጋገጠ የገለጸውን የፍሬ ጉዳይ መደምደሚያ የሚያስከትለውን ሕጋዊ ውጤት ሳይመረምርና ሳይመዝን በማለፍ ተጠሪ ሠራተኞችን የደለደለው አራት መስፈርቶች ተጠቅሞ ነው በማለት ስንብቱ ህጋዊነው በማለት መወሰኑ በመዝገቡ የሠራተኛ ወሳኝ ቦርድ በማስረጃ ያረጋገጣቸውን ፍሬ ጉዳዮች በማለፍ የተሰጠና የአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 28 ንዑስ አንቀጽ 2(ሐ) እና ንዑስ አንቀጽ 3 እንዲሁም የአዋጁን አንቀጽ 29 ንዑስ አንቀጽ 3 እና አንቀጽ 40(1) ድንጋጌዎችን የሚጥስና መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈፀመበት ነው በማለት ወስነናል፡፡

     

     ው ሳኔ

     

    1.  የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሰጠው ውሳኔ ተሽሯል፡፡

    2. የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል የሠራተኞች ጉዳይ ወሳኝ ቦርድ የአርባ ምንጭ ቅርንጫፍ በመዝገብ ቁጥር 0002/05 መሰከረም 24 ቀን 2006 ዓ/ም የሰጠው ውሳኔ ፀንቷል፡፡

    3. በዚህ ፍርድ ቤት ያወጡትን ወጭና ኪሳራ ግራ ቀኙ ለየራሳቸው ይቻሉ፡፡ መዝገቡ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ፡፡

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

  • በጋብቻ ጊዜ የተፈራ የባልና ሚስት የጋራ የሆነ የአክስዮን ድርሻ በፍቺ ጊዜ በአይነት ሊከፋፈል የሚችል ስለመሆኑ፣

     

    የተሻሻለው የቤተሰብ ህግ አንቀፅ  91 እና 92

    የሰ/መ/ቁ.102652 መጋቢት 16 ቀን 2007 ዓ.ም.

    ዳኞች፡- አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሡልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመሰል

    አመልካች፡-ወ/ሮ ሀቢባ መካ -ከጠበቃ ዘውዱ ተሾመ ጋር ቀረቡ ተጠሪዎች፡-

    1.  አቶ ደሊል ሁሴን - ቀረቡ

    2.  ኢትዮ የአሽከርካሪዎች እና መካኒኮች ማሰልጠኛ ማዕከል ኃ. የተወሰነ የግል ማህበር

    - ጠበቃ ስንታየሁ ብርሃኑ

    መዝገቡ ተመርምሮ የሚከተለው ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ የፍቺ ውሳኔን ተከትሎ በጋብቻ ውስጥ የተፈራ የአክሲዮን ድርሻ በተጋቢዎቹ መካከል የሚከፋልበትን ስርዓት አስመልክቶ የተነሳ የአፈጻጸም ክርክርን የሚመለከት ነው፡፡

     

    የጉዳዩን አመጣጥ በተመለከተ የፍቺ ውሳኔን ተከትሎ በአመልካች እና በ1ኛ ተጠሪ መካከል በነበረው የንብረት ክፍፍል ክርክር በ2ኛ ተጠሪ ማህበር ውስጥ በ1ኛ ተጠሪ ስም ተመዝግቦ የሚገኘው 162 የአክሲዮን ድርሻ በጋብቻ ውስጥ የተፈራ የጋራ ንብረት መሆኑ ተረጋግጦ እኩል እንዲካፈሉ በስረ ነገሩ ውሳኔ የተሰጠ መሆኑን፣ይህንኑ ውሳኔ ለማስፈጸም አመልካች ባቀረቡት የአፈጸጸም ክስ ላይ የአሁኑ 2ኛ ተጠሪ የፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር 418 ድንጋጌን ጠቅሶ መቃወሚያ አቅርቦ የነበረ መሆኑን፣ፍርድ ቤቱም መቃወሚያው ወደፊት የሚታይ ነው በማለት የጋራ ናቸው የተባሉትን ሌሎች ንብረቶች በተመለከተ አፈጻጸሙን መቀጠሉን፣ከዚህ በኃላ የአክሲዮን ድርሻውን በተመለከተ እንደ ፍርዱ እንዲፈጸምላቸው አመልካች አቤቱታ ማቅረባቸውን፣ፍርድ ቤቱም የአክሲዮን ድርሻው የሚገኝበት ማህበር ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር መሆኑን ታሳቢ በማድረግ ለአፈጻጸሙ ያመች ዘንድ በአፈጻጸም ጥያቄው ላይ ማህበሩ አስተያየት እንዲሰጥ ትዕዛዝ መስጠቱን ተከትሎ ከቀድሞ ተጋቢዎች መካከል  አንዳቸው ለሌላኛው ድርሻውን ለቆ አንደኛው ወገን በማህበሩ አባልነት መቀጠል የሚችል ከመሆኑ ውጪ ሁለቱን ወገኖች በአንድነት በማህበሩ ውስጥ የማይፈልጋቸው መሆኑን ገልጾ አስተያየት ማቅረቡን፣ግራ ቀኙ የዋጋ ግምቱን ተቀብለው አንዳቸው ለሌላኛው ድርሻውን ለመልቀቅ መስማማት ያልቻሉ መሆኑን እና የማህበሩ አባላት ባልተስማሙበት ሁኔታ ደግሞ ፍርድ ቤቱ ሌላ ሰው በማህበሩ ውስጥ አባል እንዲሆን መወሰን የማይችል መሆኑን ገልጾ የአክሲዮን ድርሻው


    ተሽጦ ገንዘቡን አመልካች እና 1ኛ ተጠሪ እኩል እንዲከፋፈሉ ትዕዛዝ መስጠቱን የመዝገቡ ግልባጭ ያመለክታል፡፡

     

    አመልካች አቤቱታውን ለዚህ ችሎት ያቀረቡት የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኙን ዘግቶ በማሰናበቱ ሲሆን የሰበር አቤቱታው ተመርምሮ ለክርክሩ መነሻ የሆኑት አክሲዮኖች በዓይነት መካፈል የሚችሉ ሆነው የ2ኛ ተጠሪ መተዳደሪያ ደንብም ሳይከለክል አክሲዮኖቹ በሐራጅ ተሸጠው ክፍፍሉ እንዲፈጸም የመወሰኑን አግባብነት ተጠሪዎቹ ባሉበት ለማጣራት ይቻል ዘንድ ጉዳዩ ለሰበር ክርክር እንዲቀርብ በመደረጉ ግራ ቀኙ የጽሁፍ ክርክር ተለዋውጠዋል፡፡የጉዳዩ አመጣጥ እና የክርክሩ ይዘት ከላይ የተመለከተው ሲሆን እኛም አቤቱታ የቀረበበት የስር ፍርድ ቤቶች የአፈጻጸም ትዕዛዝ መሰረታዊ የሕግ ስህተት የተፈጸመበት መሆን አለመሆኑን ለክርክሩ ከተያዘው ጭብጥ አንጻር መርምረናል፡፡

     

    በዚህም መሰረት በ2ኛ ተጠሪ ማህበር ውስጥ በ1ኛ ተጠሪ ስም ተመዝግቦ የሚገኘው 162 የአክሲዮን ድርሻ በጋብቻ ውስጥ የተፈራ የአመልካች እና የ1ኛ ተጠሪ የጋራ ንብረት መሆኑ በስረ ነገሩ ፍርድ ተረጋግጧል፡፡ጉዳዩን በመጀመሪያ ደረጃ የተመለከተው ፍርድ ቤት የአክሲዮን ድርሻው በሐራጅ ተሽጦ ክፍፍሉ በገንዘብ እንዲደረግ ውሳኔ ሊሰጥ የቻለው ከቀድሞ ተጋቢዎች መካከል አንዳቸው ለሌላኛው ድርሻውን ለቆ አንደኛው ወገን በማህበሩ  አባልነት መቀጠል የሚችል ከመሆኑ ውጪ ሁለቱን ወገኖች በአንድነት በማህበሩ ውስጥ የማይፈልጋቸው መሆኑን ገልጾ 2ኛ ተጠሪ ማህበር አስተያየት አቅርቦአል በማለት ነው፡፡አመልካች ከስር ጀምረው የሚከራከሩት ደግሞ አክሲዮኖቹ በዓይነት ሊካፋፈሉ የሚችሉ በመሆኑ ሕጻናት ልጆቻቸውን ለማሳደግ ጭምር እንዲረዳቸው የአክሲዮኖቹ ክፍፍል በዓይነት እንዲደረግ በመጠየቅ ነው፡፡በመሰረቱ የጋብቻ መፍረስን ተከትሎ የጋራ ሀብት እንዲከፋፈል የሚደረገው እያንዳንዱ ተጋቢ ከጋራ ሀብቱ የተወሰነ ንብረት እንዲደርሰው በማድረግ ስለመሆኑ እና ክፍፍሉ በሽያጭ ሊደረግ የሚችለው ንብረቱ ለክፍፍል የማያመች ወይም ለማከፋፈል የማይቻል ሆኖ ንብረቱ ከሁለት ለአንዳቸው እንዲሰጥ ባልና ሚስቱ ሳይስማሙ በቀሩ ጊዜ  ስለመሆኑ በተሻሻለው የቤተሰብ ሕግ በአንቀጽ 91 እና 92 ስር በዝርዝር ተደንግጎ ይገኛል፡፡

     

    በተያዘው ጉዳይ 2ኛ ተጠሪ ማህበር ከአመልካች እና ከ1ኛ ተጠሪ መካከል አንዳቸውን እንጂ ሁለቱን በማህበሩ ውስጥ አልፈልጋቸውም ከማለት በቀር አመልካች እና 1ኛ ተጠሪ አክሲዮኖቹን በየድርሻቸው በዓይነት በመከፋፈልየማህበሩ አባላት መሆን የማይችሉበት ሕጋዊ ምክንያት ስለመኖሩ በስር ፍርድ ቤት ያቀረበው ክርክር እና ማስረጃ የለም፡፡በሰበር ደረጃም ቢሆን አመልካች እና 1ኛ ተጠሪ አክሲዮኖቹን በዓይነት ተከፋፍለው በአባልነት ይቀጥሉ መባሉ በማህበሩ ውስጥ ብርቱ ጭቅጭቅን እና አለመግባባትን የሚያስከትል ነው ከማለት ውጪ የዚህ ዓይነት ሁኔታ ሊከሰት ስለሚችልበት ምክንያት ያቀረበው አሳማኝ መከራከሪያ የለም፡፡ የአክሲዮኖቹ በዓይነት የመከፋፈል ጉዳይ የሚመለከተው በመሰረቱ አመልካችን እና 1ኛ ተጠሪን እንጂ 2ኛ ተጠሪን ባለመሆኑ አክሲዮኖቹ ሊከፋፈሉ የሚገባቸው በሽያጭ ነው በማለት 2ኛ ተጠሪ መቃወሚያ አቅርቦ ለመከራከር የሚያስችል መብት እና ጥቅም አለው ለማለትም የሚቻል አይደለም፡፡

     

    ሲጠቃለል በ2ኛ ተጠሪ ማህበር ውስጥ በ1ኛ ተጠሪ ስም ተመዝግቦ የሚገኘው 162 የአክሲዮን ድርሻ በጋብቻ ውስጥ የተፈራ የአመልካች እና የ1ኛ ተጠሪ የጋራ ንብረት መሆኑ እስከተረጋገጠ ድረስ የአክሲዮን ድርሻውን አመልካች እና 1ኛ ተጠሪ በዓይነት እንዲከፋፈሉ ለመወሰን የሚከለክል ሕጋዊ ምክንያት ባልቀረበበት ሁኔታ 2ኛ ተጠሪ ማህበር የሰጠውን አስተያየት   ብቻ


    መሰረት በማድረግ የአክሲዮን ድርሻው ክፍፍል በሽያጭ አማካይነት እንዲፈጸም በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ተሰጥቶ በይግባኝ ሰሚው ፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በትዕዛዝ የጸናው የአፈጻጸም ትዕዛዝ የተሻሻለውን የቤተሰብ ሕግ በአንቀጽ 91 እና 92 ድንጋጌዎች መሰረት ያላደረገ እና መሰረታዊ የሕግ ስህተት የተፈጸመበት ሆኖ በመገኘቱ የሚከተለው ውሳኔ ተሰጥቷል፡፡

     

     ው ሳ ኔ

     

    1. በ2ኛ ተጠሪ ማህበር ውስጥ በ1ኛ ተጠሪ ስም ተመዝግበው የሚገኙት 162 የአክሲዮኖች ለአመልካች እና ለ1ኛ ተጠሪ ሊከፋፈል የሚገባው በሐራጅ ሽያጭ ነው በሚል በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 206322 በ25/07/2006 ዓ.ም. ተሰጥቶ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 150907 በ30/08/2006 ዓ.ም. በትዕዛዝ የጸናው የአፈጻጸም ትዕዛዝ በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር 348(1) መሰረት ተሽሯል፡፡

    2. በ2ኛ ተጠሪ ማህበር ውስጥ በ1ኛ ተጠሪ ስም ተመዝግበው የሚገኙት 162 አክሲዮኖች በዓይነት ሊከፋፈሉ የማይችሉበት ሕጋዊ ምክንያት ባለመኖሩ እነዚህን  አክሲዮኖች አመልካች እና 1ኛ ተጠሪ በተሻሻለው የቤተሰብ ሕግ በአንቀጽ 91(1) ድንጋጌ መሰረት እያንዳንዳቸው 81 አክሲዮኖችን በዓይነት ሊከፋፈሉ ይገባል በማለት ወስነናል፡፡

    3. የዚህ ውሳኔ ግልባጭ በውሳኔው መሰረት እንዲያስፈጽም ለፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት፣ እንዲያውቀው ደግሞ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይላክ፡፡

    4.  የሰበር ክርክሩ ያስከተለውን ወጪና ኪሳራ ግራ ቀኙ የየራሳቸውን ይቻሉ፡፡

    5.  ውሳኔ ያገኘ ስለሆነ መዝገቡ ተዘግቷል፡፡

     

     

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት::

  • በፍርድ የተከለለከለ ሰው የፍቺ ጥያቄ ስለሚያቀርብበት አግባብ

     

    የሰ/መ/ቁ. 103781 ቀን መጋቢት 17/2007 ዓ.ም

    ዳኞች፡- አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሱልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኸሊት ይመስል

    አመልካች ፡- ወ/ሮ አስካለ አሽኔ - ጠበቃ በርታ በቀለ ቀረቡ ተጠሪ፡- አቶ ታምራት ተስፋዬ - ጠበቃ አሸናፊ ቦሻ ቀረቡ

    መዝገቡን መርምረን የሚከተለውን ፍርድ ሰጥተናል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ የቀረበው አመልካች በመዝገብ ቁጥር 197469 ጥር 12 ቀን 2006 ዓ.ም የሰጠው ውሣኔና የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 150493 ግንቦት 5 ቀን 2006 ዓ.ም የሰጠው ትዕዛዝ መሠረታዊ የሕግ ስህተት ያለበት ስለሆነ በሰበር ታይቶ እንዲታረምልኝ በማለት ያቀረቡትን የሰበር አቤቱታ አጣርቶ ለመወሰን ነው፡፡ ጉዳዩ የፍች ውሳኔን በመቃወም የቀረበ ጥያቄን የሚመለከት ነው፡፡

    1. የክርክሩ መነሻ ተጠሪ የአባቱ የአቶ ተስፋዬ ጉልማ አሳዳሪና ሞግዚት መሆኑን ገልፆ፣የአቶ ተስፋዬ ጉልማና አመልካች 1964 ዓ.ም ጀምሮ በጋብቻ ተሣስረው ኖረዋል፡፡በትዳራቸው ልጆች አላፈሩም ፡፡ አባቴና ሞግዚት አድራጊና በእድሜ በመግፋታቸው ምክንያት የአእምሮና የጤና መታወክ አጋጥሟቸዋል፡፡ ተጠሪ ባላቸውን ሊንከባከቡዋቸው አልቻለም በዚህ ምክንያት ሁለቱ ተለያይተው መኖር ከጀመሩ ረዥም ጊዜ ሆኋቸዋል ፡፡ ስለዚህ ሞግዚት አድራጊዬ ከተጠሪ /አመልካች /ጋር ያላቸው ጋብቻ በፍች እንዲፈርስ ውሣኔ ይሰጥልኝ በማለት አመልክቷል፡፡ የአሁን አመልካች /በሥር ተጠሪ/ለፍች የሚያበቃ ምክንያት የለንም በማለት ተከራክረዋል፡፡ የሥር ፍርድ ቤት አቶ ተስፋዬ ጉልማ  በአካል በተደጋጋሚ እያስቀረበ ካነጋገረ በኃላ በአቶ ተስፋዬ ጉልማና በአመልካች መካከል በፍች እንዲፈርስ ውሣኔ ሰጥቷል፡፡ አመልካች ይግባኝ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ አቅርበዋል፡፡ ይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት የአመልካችን ይግባኝ በፍ/ሥ/ሥ/ሕግ ቁጥር 337 መሠረት ሰርዞታል፡፡

    2. አመልካች ተጠሪ ፍች እንዲወሰን የማመልከት ስልጣን የለውም ፡፡ የሥር ፍርድ ቤት የሰጠው የፍች ውሣኔ ህግን መሠረት ያደረገ አይደለም በማለት ነሐሴ 5 ቀን 2006 ዓ.ም የተፃፈ የሰበር አቤቱታ አቅርበዋል ፡፡ ተጠሪ በበኩሉ አመልካች ከሞግዚት አድራጊዬ ጋር የባልና የሚስት ግዴታ እየተወጡ አይደለም፡፡ የሥር ፍርድ ቤት ውሣኔ የሰጠው ሞግዚት አድራጊዬን በተደጋጋሚ አስቀርቦ ሁኔታውን ከተረዳ በኃላና በተሻሻለው የፌዴራል የቤተሰብ ሕግ መሠረት ነው በማለት ተከራክሯል፡፡ አመልካች የመልስ መልስ አቅርበዋል ፡፡


    3. የሥር የክርክሩ አመጣጥና በሰበር የቀረበው ክርክር ከላይ የተገለፀው ሲሆን እኛም የበታች ፍርድ ቤቶች የተጠሪን የፍች ጥያቄ በመቀበል የሰጡት የፍች ውሳኔ ሕግን መሠረት ደረገ ነው ወይስ አይደለም የሚለውን ጭብጥ በመያዝ ጉዳይን መርምረናል፡፡

    4. በመርህ ደረጃ የፍች ጥያቄ ለማቅረብ የሚችሉት ባል ወይም ሚስት ወይም ሁለቱም በጋራ ጥያቄ በማቅረብ እንደሚሆን በተሻሻለው የፌዴራል የቤተሰብ ሕግ አዋጅ ቁጥር 213/992 አንቀፅ 81 ተደንግጓል ፡፡ ሆኖም አንድ ሰው ጋብቻ ፈፅሞና በጋብቻ ተሣሥሮ ከኖረ በኃላ በፍርድ ክልከላ የተደረገበት በሆነ ጊዜ የፍች ጥያቄ የሚያቀርበው በምን ሁኔታና  እንዴት ነው የሚለው ጥያቄ ሲነሳ በፍታብሔር ሕግ በፍርድ ስለሚደረግ ክልከላና ክልከላው ስለሚያስከትለው ውጤት ከፍትሐብሔር ህግ ቁጥር 351 እስከ ፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 389 የተደረጉትን ድንጋጌዎች መመልከት አስፈላጊ ነው፡፡ በተለይም የፍትሐብሔር ህግ ቁጥር 370 ንዑስ አንቀፅ 1 ፍች ወይም ከሕግ ውጭ የሚያደርገው የግብረ ስጋ ግንኙነት እንዲቀር ጥያቄ ለማቅረብ የተከለከለው ሰው ፈቃድ የግድ አስፈላጊ እንደሆነ የአሳዳሪውም ፈቃድ የግድ አስፈላጊ ነው በማለት ይደነግጋል ፡፡

    5. ከዚህ አንፃር የአቶ ተስፋዬ ጉልማ አሳዳሪና ሞግዚት ሆኖ የተሾመው ተጠሪ ሞግዚት ሆኖ የሚያስተዳድራቸው ወላጅ አባቱ ፤በእድሜ በመግፋታቸው ምክንያት ራሳቸውን ችለው ህጋዊ ተግባራት መፈፀም እንደማይችሉ በፍርድ ተረጋግጦ ክልከላ የተደረገባቸው መሆኑንና አመልካችና አቶ ተስፋዬ ጉልማ ተለያይተው ለረጅም ጊዜ መኖራቸውን በመግለፅ ፍች እንዲወሰን ጠይቋል፡፡ ይህም ተጠሪ የፍታብሔት ህግ ቁጥር 370 ንዑስ አንቀፅ 1 መሠረት ጋብቻው በፍች አንዲፈርስ ጥያቄ ያቀረበ መሆኑን ያሳያል ፡፡ የሥር ፍርድ ቤትም ፤አቶ ተስፋዬ ጉልማ በተደጋጋሚ ቸሎት በማስቀረብና ካናገረ በኃላ አመልካችና አቶ ተስፋዬ ጉልማ በቤተሠብ ህጉ በባልና ሚስት ላይ የተጣለውን እርስ በእርስ የመተጋገዝ  የመረዳዳት

    ፣የመደጋገፍና የመተሳሰብ ግዴታ እየተወጡ አለመሆኑን በማረጋገጥ ጋብቻው በፍች እንዲፈርስ ውሣኔ ሰጥቷል፡፡ ይህ የሥር ፍርድ ቤት ውሣኔ አመልካችና አቶ ተስፋዬ ጉልማ በሕግ ፊት ባልና ሚስት ናቸው ቢባልም በዕውኑ ግን በባልና ሚስትነት የመፈፀማቸውን ተግባራትን ግዴታዎች እየፈፀሙ የማይኖሩ መሆኑንና የጋብቻው በፍች መፍረስ በፍርድ ክልከላ የተደረገባቸውን አቶ ተስፋዬ ጉልማ መብትና ጥቅም ለማስከበር አስፈላጊ መሆኑን በማረጋገጥ የሰጠው ውሳኔ መሆኑን በውሣኔ ተረድተናል ፡፡ በመሆኑም የበታች  ፍርድ ቤቶች የሰጡት ውሣኔ መሠረታዊ የሕግ ስህተት የለበትም በማለት ወስነናል፡፡

     ው ሳ ኔ

    1. የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤትና የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሰጡት ውሣኔ ፀንቷል ፡፡

    2. ይህ ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 103781 ህዳር 17 ቀን 2007 ዓ.ም የሰጠው የዕግድ ትዕዛዝ ተነስቷል ፡፡ ይፃፍ፡፡

    3. ግራቀኙ በዚህ ፍርድ ቤት ያወጡትን ወጭ ለየራሳቸው ይቻሉ፡፡ መዝገቡ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ፡፡

     

    የማይነበብ የአምስትዳኞች ፊርማ አለበት ፡፡

  • በፍርድ የተከለለከለ ሰው የፍቺ ጥያቄ ስለሚያቀርብበት አግባብ

     

    የሰ/መ/ቁ. 103781 ቀን መጋቢት 17/2007 ዓ.ም

    ዳኞች፡- አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሱልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኸሊት ይመስል

    አመልካች ፡- ወ/ሮ አስካለ አሽኔ - ጠበቃ በርታ በቀለ ቀረቡ ተጠሪ፡- አቶ ታምራት ተስፋዬ - ጠበቃ አሸናፊ ቦሻ ቀረቡ

    መዝገቡን መርምረን የሚከተለውን ፍርድ ሰጥተናል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ የቀረበው አመልካች በመዝገብ ቁጥር 197469 ጥር 12 ቀን 2006 ዓ.ም የሰጠው ውሣኔና የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 150493 ግንቦት 5 ቀን 2006 ዓ.ም የሰጠው ትዕዛዝ መሠረታዊ የሕግ ስህተት ያለበት ስለሆነ በሰበር ታይቶ እንዲታረምልኝ በማለት ያቀረቡትን የሰበር አቤቱታ አጣርቶ ለመወሰን ነው፡፡ ጉዳዩ የፍች ውሳኔን በመቃወም የቀረበ ጥያቄን የሚመለከት ነው፡፡

    1. የክርክሩ መነሻ ተጠሪ የአባቱ የአቶ ተስፋዬ ጉልማ አሳዳሪና ሞግዚት መሆኑን ገልፆ፣የአቶ ተስፋዬ ጉልማና አመልካች 1964 ዓ.ም ጀምሮ በጋብቻ ተሣስረው ኖረዋል፡፡በትዳራቸው ልጆች አላፈሩም ፡፡ አባቴና ሞግዚት አድራጊና በእድሜ በመግፋታቸው ምክንያት የአእምሮና የጤና መታወክ አጋጥሟቸዋል፡፡ ተጠሪ ባላቸውን ሊንከባከቡዋቸው አልቻለም በዚህ ምክንያት ሁለቱ ተለያይተው መኖር ከጀመሩ ረዥም ጊዜ ሆኋቸዋል ፡፡ ስለዚህ ሞግዚት አድራጊዬ ከተጠሪ /አመልካች /ጋር ያላቸው ጋብቻ በፍች እንዲፈርስ ውሣኔ ይሰጥልኝ በማለት አመልክቷል፡፡ የአሁን አመልካች /በሥር ተጠሪ/ለፍች የሚያበቃ ምክንያት የለንም በማለት ተከራክረዋል፡፡ የሥር ፍርድ ቤት አቶ ተስፋዬ ጉልማ  በአካል በተደጋጋሚ እያስቀረበ ካነጋገረ በኃላ በአቶ ተስፋዬ ጉልማና በአመልካች መካከል በፍች እንዲፈርስ ውሣኔ ሰጥቷል፡፡ አመልካች ይግባኝ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ አቅርበዋል፡፡ ይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት የአመልካችን ይግባኝ በፍ/ሥ/ሥ/ሕግ ቁጥር 337 መሠረት ሰርዞታል፡፡

    2. አመልካች ተጠሪ ፍች እንዲወሰን የማመልከት ስልጣን የለውም ፡፡ የሥር ፍርድ ቤት የሰጠው የፍች ውሣኔ ህግን መሠረት ያደረገ አይደለም በማለት ነሐሴ 5 ቀን 2006 ዓ.ም የተፃፈ የሰበር አቤቱታ አቅርበዋል ፡፡ ተጠሪ በበኩሉ አመልካች ከሞግዚት አድራጊዬ ጋር የባልና የሚስት ግዴታ እየተወጡ አይደለም፡፡ የሥር ፍርድ ቤት ውሣኔ የሰጠው ሞግዚት አድራጊዬን በተደጋጋሚ አስቀርቦ ሁኔታውን ከተረዳ በኃላና በተሻሻለው የፌዴራል የቤተሰብ ሕግ መሠረት ነው በማለት ተከራክሯል፡፡ አመልካች የመልስ መልስ አቅርበዋል ፡፡


    3. የሥር የክርክሩ አመጣጥና በሰበር የቀረበው ክርክር ከላይ የተገለፀው ሲሆን እኛም የበታች ፍርድ ቤቶች የተጠሪን የፍች ጥያቄ በመቀበል የሰጡት የፍች ውሳኔ ሕግን መሠረት ደረገ ነው ወይስ አይደለም የሚለውን ጭብጥ በመያዝ ጉዳይን መርምረናል፡፡

    4. በመርህ ደረጃ የፍች ጥያቄ ለማቅረብ የሚችሉት ባል ወይም ሚስት ወይም ሁለቱም በጋራ ጥያቄ በማቅረብ እንደሚሆን በተሻሻለው የፌዴራል የቤተሰብ ሕግ አዋጅ ቁጥር 213/992 አንቀፅ 81 ተደንግጓል ፡፡ ሆኖም አንድ ሰው ጋብቻ ፈፅሞና በጋብቻ ተሣሥሮ ከኖረ በኃላ በፍርድ ክልከላ የተደረገበት በሆነ ጊዜ የፍች ጥያቄ የሚያቀርበው በምን ሁኔታና  እንዴት ነው የሚለው ጥያቄ ሲነሳ በፍታብሔር ሕግ በፍርድ ስለሚደረግ ክልከላና ክልከላው ስለሚያስከትለው ውጤት ከፍትሐብሔር ህግ ቁጥር 351 እስከ ፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 389 የተደረጉትን ድንጋጌዎች መመልከት አስፈላጊ ነው፡፡ በተለይም የፍትሐብሔር ህግ ቁጥር 370 ንዑስ አንቀፅ 1 ፍች ወይም ከሕግ ውጭ የሚያደርገው የግብረ ስጋ ግንኙነት እንዲቀር ጥያቄ ለማቅረብ የተከለከለው ሰው ፈቃድ የግድ አስፈላጊ እንደሆነ የአሳዳሪውም ፈቃድ የግድ አስፈላጊ ነው በማለት ይደነግጋል ፡፡

    5. ከዚህ አንፃር የአቶ ተስፋዬ ጉልማ አሳዳሪና ሞግዚት ሆኖ የተሾመው ተጠሪ ሞግዚት ሆኖ የሚያስተዳድራቸው ወላጅ አባቱ ፤በእድሜ በመግፋታቸው ምክንያት ራሳቸውን ችለው ህጋዊ ተግባራት መፈፀም እንደማይችሉ በፍርድ ተረጋግጦ ክልከላ የተደረገባቸው መሆኑንና አመልካችና አቶ ተስፋዬ ጉልማ ተለያይተው ለረጅም ጊዜ መኖራቸውን በመግለፅ ፍች እንዲወሰን ጠይቋል፡፡ ይህም ተጠሪ የፍታብሔት ህግ ቁጥር 370 ንዑስ አንቀፅ 1 መሠረት ጋብቻው በፍች አንዲፈርስ ጥያቄ ያቀረበ መሆኑን ያሳያል ፡፡ የሥር ፍርድ ቤትም ፤አቶ ተስፋዬ ጉልማ በተደጋጋሚ ቸሎት በማስቀረብና ካናገረ በኃላ አመልካችና አቶ ተስፋዬ ጉልማ በቤተሠብ ህጉ በባልና ሚስት ላይ የተጣለውን እርስ በእርስ የመተጋገዝ  የመረዳዳት

    ፣የመደጋገፍና የመተሳሰብ ግዴታ እየተወጡ አለመሆኑን በማረጋገጥ ጋብቻው በፍች እንዲፈርስ ውሣኔ ሰጥቷል፡፡ ይህ የሥር ፍርድ ቤት ውሣኔ አመልካችና አቶ ተስፋዬ ጉልማ በሕግ ፊት ባልና ሚስት ናቸው ቢባልም በዕውኑ ግን በባልና ሚስትነት የመፈፀማቸውን ተግባራትን ግዴታዎች እየፈፀሙ የማይኖሩ መሆኑንና የጋብቻው በፍች መፍረስ በፍርድ ክልከላ የተደረገባቸውን አቶ ተስፋዬ ጉልማ መብትና ጥቅም ለማስከበር አስፈላጊ መሆኑን በማረጋገጥ የሰጠው ውሳኔ መሆኑን በውሣኔ ተረድተናል ፡፡ በመሆኑም የበታች  ፍርድ ቤቶች የሰጡት ውሣኔ መሠረታዊ የሕግ ስህተት የለበትም በማለት ወስነናል፡፡

     ው ሳ ኔ

    1. የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤትና የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሰጡት ውሣኔ ፀንቷል ፡፡

    2. ይህ ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 103781 ህዳር 17 ቀን 2007 ዓ.ም የሰጠው የዕግድ ትዕዛዝ ተነስቷል ፡፡ ይፃፍ፡፡

    3. ግራቀኙ በዚህ ፍርድ ቤት ያወጡትን ወጭ ለየራሳቸው ይቻሉ፡፡ መዝገቡ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ፡፡

     

    የማይነበብ የአምስትዳኞች ፊርማ አለበት ፡፡

  • አንድ ሠራተኛ የስራ ግዴታውን በአግባቡ ባለመወጣት በአሰሪው ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ላይ ጉዳት ያደረሰ ከሆነ የስራ ውሉን ያለማስጠንቀቂያ ለማቋረጥ በቂ ምክንያት ሥለመሆኑ፣

     

    አዋጅ ቁጥር 377/96 (1)(ሸ)፣ 12(2)(7)

    የሰ/መ/ቁ. 104294 ቀን 29/07/2007 ዓ/ም

    ዳኞች፡-  አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሱልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመሰል

    አመልካች፡- ሐግቤስ ኃ/የተ/የግል/ማህበር - ነ/ፈጅ ፀጋዬ መካሻ ቀረቡ ተጠሪ፡- አቶ በላይ ገ/ማሪያም - ቀረቡ

    መዝገቡን መርምረን የሚከተለውን ፍርድ ሰጥተናል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ የቀረበው በፌዴደራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የአመልካች የስንብት እርምጃ ህገ ወጥ ነው ተብሎ የተሰጠው ውሳኔ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመጽናቱ በውሳኔው ላይ መሰረታዊ የሆነ የህግ ስህተት ያለበት ስለሆነ በሰበር ታይቶ ይታረምልኝ በማለት አመልካች ያቀረበውን የሰበር አቤቱታ አጣርቶ ለመወሰን ነው፡፡ ጉዳዩ የአሰሪና ሰራተኛ አዋጅ ቁጥር 377/96 “ን” መሰረት ያደረገ የግል የስራ ክርክር ሁኖ አንድ ሰራተኛ ከአሰሪው ንብረት ላይ ጉዳት አድርሷል ተብሎ ከስራ ያለማስጠንቀቂያ የሚሰናበትበትን የህግ አግባብ ነው፡፡

    በስር ፍርድ ቤት የቀረበው የተጠሪ ክስ አመልካች ተጠሪን በጨረታ እንዳይሳተፍ የተደረገውን ጥፋት ሳይፈጽም ይህንኑ ጥፋት ፈጽመሃል በሚል ምክንያት የስራ ውል አላግባብ ያቋረጠ በመሆኑ የተለያዩ ክፍያዎችን እንዲከፍል ይወሰንልኝ የሚል ነው፡፡ የአሁኑ  አመልካች በተከሳሽነቱ ቀርቦ በሰጠው መልስ የተጠሪ የስራ መዝርዝር በግልጽ የሚያሳየው የጨረታ ሰነድ አዘጋጅተው የጨረታውን ሂደት በመከታተል ሪፖርት ማቅረብ መሆኑን ፣ ተጠሪ ይህንኑ የስራ ግዴታ በመተላለፍ የጨረታ ሰነድ ሳያስገቡ በቀሩት የማሽን ጉልበት አመልካች ድርጅት ከጨረታ እንዲሰረዝ በመደረጉ ለተጠሪ ማስጠንቀቂያ የተሰጣቸው ቢሆንም አመልካች ድርጅት ተሳታፊ እንዲሆን በወሰነበት የትግራይ የውሃስራዎች ኮንስትራክሽን መጋቢት 05 ቀን 2005 ዓ/ም ባወጣው ጨረታ ጨረታውን ሳይከታተሉ በመቅረታቸው ድርጅቱ በጨረታው እንዳይሳተፍ አድርገው የጥቅም ማጣት እንዲደርስበት ያደረጉ መሆኑን ዘርዝሮ ስንብቱ በህጉ አግባብ የተደረገ ነው በማለት ተከራክሯል፡፡

    የስር ፍ/ቤት ተጠሪ በፈጸሙት ከባድ ቸልተኝነት ምክንያት አመልካች ድርጅት በጨረታው ላይ ሳይሳተፍ የቀረ መሆኑ ቢረጋገጥም በዚህ ጥፋት ምክንያት በአመልካች ድርጅት ላይ የደረሰ ጉዳት መኖሩ አልተረጋገጠም የሚል ምክንያት አስፍሮ የአመልካች የስንብት እርምጃ ህገ ወጥ ነው በማለት አመልካች ለተጠሪ የተለያዩ ክፍያዎችን ሊከፍል ይገባል በማለት የክፍያዎችን


    አይነትና መጠን በመዘርዘር በድምሩ ብር 72,000.00 (ሰባ ሁለት ሺህ) እንዲከፍል፣ የስራ ልምድ የምስክር ወረቀት አዘጋጅቶ እንዲሰጠው ሲል ወስኗል፡፡

    አመልካች በዚህ ውሳኔ ቅር በመሰኘት ይግባኝ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቢያቀርብም ተቀባይነት አላገኘም፡፡ የአሁኑ የሰበር አቤቱታ የቀረበውም ይህንኑ ውሳኔ በመቃወም ሲሆን የአመልካች የሰበር አቤቱታ መሰረታዊ ይዘትም፡- ተጠሪ በስራ መዘርዝራቸው መሰረት ግዴታቸውን ያለመወጣታቸውና ከባድ ቸልተኝነት የነበረባቸው መሆኑን የስር ፍርድ ቤት አረጋግጦ ጉዳት ስለመድረሱ አልተረጋገጠም በሚል ምክንያት ብቻ ስንብቱ ህገ ወጥ ነው በማለት የወሰነው ከህጉ ይዘትና መንፈስ ውጪ ነው ፣ አመልካች በጨረታው ላይ ባለመሳተፉ ከብር ሃያ ሶስት ሚሊዮን በላይ የጥቅም ማጣት ደርሶበታል በማለት መከራከሩን የሚያሳይ ነው፡፡ አቤቱታው ተመርምሮም በዚህ ችሎት እንዲታይ በመደረጉ ለተጠሪ ጥሪ ተደርጎላቸው ቀርበው ግራ ቀኙ በጽሁፍ እንዲከራከሩ ተደርጓል፡፡ ተጠሪ በፅሁፍ በሰጡት መልስም በአመልካች ድርጅት ላይ ጉዳት ያለመደረሱን ፣ በስራቸው የፈጸሙት ጥፋትም የሌለ መሆኑን ዘርዝረው ተከራክረዋል፡፡

    ከስር የክርክሩ አመጣጥና በሰበር የቀረበው ክርክር ከላይ የተገለጸው ሲሆን እኛም ጉዳዩን መርምረናል፡፡ ጉዳዩን እንደመረመርነው የበታች ፍርድ ቤቶች አመልካች የተጠሪን የስራ ውል ያቋረጠው ከህግ ውጭ በመሆኑ ፣ ለተጠሪ የተለያዩ ክፍያዎችን እንዲከፍል የሰጠው ውሳኔ ተገቢ ነው? ወይስ አይደለም? የሚለው ጭብጥ መታየት ያለበት ሆኖ አግኝተነዋል፡፡

    ጉዳዩን እንደመረመርነው የተጠሪ የስራ መዝርዝር በግልጽ የሚያሳየው የጨረታ  ሰነድ አዘጋጅተው የጨረታውን ሂደት በመከታተል ሪፖርት ማቅርብ መሆኑንና ይህንኑ የስራ ግዴታ ባለመወጣታቸው አመልካች ቀድሞ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸው እንደገና አመልካች ድርጅት ተሳታፊ እንዲሆን በወሰነበት የትግራይ የውሃ ስራዎች ኮንስትራክሽን መጋቢት 05 ቀን 2005 ዓ/ም ባወጣው ጨረታ ጨረታውን ሳይከታተሉ በመቅረታቸው ድርጅቱ በጨረታው እንዳይሳተፍ ያደረጉ መሆኑ በበታች ፍርድ ቤቶች ተረጋግጧል፡፡ ተጠሪም ይህንን ጥፋት ያልፈጸሙ መሆኑን በማስረጃዎቹ ያላስረዱ መሆኑን ከስር ፍርድ ቤቶች የውሳኔ ይዘት ተገንዝበናል፡፡ ተጠሪ በዚህ የሰበር ክርክር ደረጃ ባቀረቡት መልስ በአመልካች ድርጅት ላይ በጨረታ ባለመሳተፉ የደረሰ ጉዳት የለም በማለት ከገለፁ በኋላ በአማራጭ ደግሞ ከባድ ቸልተኝነት እንዳልነበራቸውና ጥፋት እንዳልፈጸሙ ዘርዝረው በዚሁ በአማራጭ ባቀረቡት ክርክር መሰረት የስር ፍርድ ቤቶች ውሳኔ ሊጸና ይገባል በማለት ተከራክረዋል፡፡ ሆኖም ተጠሪ ከባድ ቸልተኘነት እንዳልነበራቸው ፣ ጥፋት እንዳልፈጸሙ የሚያቀርቡት ክርክር በሰበር መልሳቸው የተገለፀ እንጂ ስርዓቱን ጠብቆ  የቀረበ ነው ሊባል የሚችል ካለመሆኑም በላይ የስር ፍርድ ቤት ፍሬ ነገሩን አጣርቶና ማስረጃን መዝኖ የደረሰበት ድምዳሜ በመሆኑ በዚህ ችሎት ሊለወጥ የሚችል ሆኖ አልተገኘም፡፡ በመሆኑም ተጠሪ በከባድ ቸልተኝነት አመልካች ድርጅት በጨረታው ላይ እንዳይሳተፍ ያደረጉ መሆኑ በፍሬ ነገር ደረጃ የተረጋገጠ ነው በሚል የምንቀበለው ነጥብ ነው፡፡

    አመልካች ተጠሪን ለቀደመው ጥፋታቸው በማስጠንቀቂያ ያለፋቸው ቢሆንም መጋቢት 05 ቀን 2005 ዓ/ም በወጣው ጨረታ እንዳይሳተፍ የተደረገው በተጠሪ ጥፋት መሆኑ በመረጋገጡ ተጠሪን ከስራ ሊያስናብታቸው ችሏል፡፡ አመልካች በዚህ ጨረታ ያልተሳተፈው በተጠሪ ከባድ ቸልተኝነት መሆኑ በበታች ፍርድ ቤቶች ተረጋግጧል፡፡ ተጠሪ የሚሰሩበት የስራ ባህርይ የጨረታ ሰነድ አዘጋጅተው የጨረታውን ሂደት በመከታተል ሪፖርት ማቅረብ መሆኑንም በስር ፍርድ ቤቶች የተረጋገጠ በመሆኑ ተጠሪ አመልካች ድርጅትን ጥቅም ለማስጠበቅ ከፍተኛ ጥንቃቄና ትጋት በማድረግ ግዴታቸውን መወጣት የሚገባቸውና የድርጅቱ ኢኮኖሚ ጥቅም ጉዳት  እንዳይደርስበት  የማድረግ  የስራ  ግዴታ  አለባቸው፡፡  ተጠሪ  ይህንን  የስራ ተግባሩን


    በአግባቡና በጥንቃቄ ባለመፈጸማቸው አመልካች ድርጅት ከጨረታ መሰረዙ  በድርጅቱ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ላይ ጉዳት አላደረሰም ሊባል የሚችል አይደለም፡፡ ተጠሪ ጉዳዩን ጨረታን መሰረት ያደረገና በውድድር ላይ የተመሰረት መሆኑን ግልጸው የአመልካች ድርጅት የጨረታ ሰነድ ከሌሎች ተጫራቾች ጋር ሲነጻጸር ጨረታውን ሊያሽነፍ ይችል ያልነበረ መሆኑን ጠቅሰው ያቀረቡት ክርክር የለም፡፡ በጨረታው ውደድር በአመልካች ድርጅት ጥቅም የሚገኝበት አግባብ መኖሩ ግልጽ ከሆነና አመልካች በተጠሪ የስራ ግዴታቸውን በአግባቡ ባለመወጣት ከውድድሩ ውጪ መሆኑ ከተረጋገጠ በአመልካች ድርጅት ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ላይ ጉዳት ያለመደረሱን የማስረዳት ግዴታ የተጠሪ ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ግን ተጠሪ በአመልካች ላይ ጉዳት አልደረሰም ከማለት ውጪ ይህንኑ የሚያስረዳ ማስረጃ ያለማቅረባቸውን ከክርክሩ ሂደት ለመገንዘብ ችለናል፡፡ ተጠሪ የፈጸሙት ጥፋት በአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 27 ንዑስ አንቀጽ 1/ሸ/ የሚሽፈንና የተጠሪን የስራ ውል ያለማስጠንቀቂያ ለማቋረጥ የሚያስችል በቂ ምክንያት ሆኖ እያለ የበታች ፍርድ ቤቶች በተጠሪ ከባድ ቸልተኝነት ምክንያት በአመልካች ላይ የደረሰ ጉዳት የለም በማለት ስንብቱ ህገ ወጥ ነው በማለት የሰጡት ውሳኔ የአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 27(1)ሸ እና አንቀጽ 12(2)(7) ድንጋጌ መሰረታዊ ይዘት ፣ መንፈስና አላማ ያላገናዘብ ሆኖ አግኝተነዋል፡፡

    ከዚህ አንጻር ሲታይ አመልካች የተጠሪን ማስጠንቀቂያ ሰጥቶ በድጋሚ ጥፋት ሲፈጽሙ የስራ ውሉን ያለማስጠንቀቂያ ማቋረጡ በአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 27(1)(ሸ) እና 12(2)(7) ድንጋጌዎች መሰረት ህጋዊ እንጂ ህገ ወጥ ተግባር ሆኖ አላገኘነውም፡፡ በመሆኑም የበታች ፍርድ ቤቶች አመልካች የተጠሪን የስራ ውል ያቋረጠው ከህግ ውጭ ነው በማለት የሰጡት ውሳኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት ያለበት ሆኖ ስለአገኘነው ተከታዩን ወስነናል፡፡

     ው ሳ ኔ

    1. በፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በመ/ቁጥር 10206 ሚያዚያ 30 ቀን 2006 ዓ/ም ተሰጥቶ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመ/ቁጥር 140042 ሐምሌ 25 ቀን 2006 ዓ/ም የፀናው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ህ/ቁጥር 348(1) መሰረት ተሽሯል፡፡

    2. የአመልካች እርምጃ ህጋዊ ነው፣ አመልካች ለተጠሪ ካሳም ሆነ የሰራ ስንብት ክፍያ ሊከፍል አይገባም ብለናል፡፡ የስራ ልምድ ምስክር ወረቀት ግን ይስጣቸው ብለናል፡፡

    3.  በዚህ ችሎት ለተደረገው ክርክር የወጣውን ወጪና ኪሳራ የየራሳቸውን ይቻሉ ብለናል፡፡

     

     

    መዝገቡ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ፡፡

     

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት

  • Civil procedure

    Execution of judgment

    Family law

    partition of common property in kind

    Sale on public auction

    Administrative law

    City master plan

    Civil procedure code art. 277(1), 325, 392

    Family code of Amhara region art. 79/95 art. 73, 74, 101-103

     

    እኩል እንከፋፈል በሚል በፍ/ቤት የፀደቀን የቦታና ቤት ስምምነት እኩል ለማካፈል የከተማ አስተዳደሩ የፕላን ስታንዳርድን አያሟላም በተባለ ጊዜ የባልና ሚስትን የጋራ ሀብት በሀራጅ ተሸጦ ይካፈሉ ብሎ መወሰን የግራ ቀኙን በቤቱ የመጠቀም ፍላጎት /ነጻነት የሚገደብ ስለመሆኑ

    የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ 277/1/,325,392

    የአማ/ክልል የቤተሰብ ህግ አዋጅ 79/95 አንቀጽ 73,74 101-103

     

    104521

  • አንድን ሰው ሠራተኛ ነው ለማለት በቅጥር ላይ የተመሰረተ የሥራ ግንኙነት መኖር፣ሠራተኛው አገልግሎት የመስጠት ግዴታ ያለበት መሆኑ፣ ሊሰጥ የሚገባውን አገልግሎትመቼ ሊያከናውን እንደሚገባና እንዴት ማከናወን እንደሚኖርበት አሰሪው የመቆጣጠር ስልጣን ያለው ስለመሆኑ መረጋገጥ ያለባቸው ስለመሆኑ፣

     

    አንድን አደጋ በስራ ላይ የደረሰ ነው ለማለት ሠራተኛው ስራውን በማከናወን ላይ እያለ ወይም ከስራው ጋር ግንኙነት ባለው ሁኔታ ከራሱ ውጪ በሆነ ምክንያት ወይም በአካሉ በማንኛውም ክፍል ተፈጥሯዊ እንቅስቃሴ ላይ በድንገት የደረሰበት ጉዳት ስለመሆኑ፣

     

    አዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀፅ 2.4፣58.96፣97፣107፣110

     

    የሰበር መ/ቁ 105555

     

    መጋቢት 18 ቀን 2007 ዓ.ም

     

    ዳኞች፡- አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ

     

    ሡልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመሰል

    አመልካች፡- 1.መፍትሃ ሙሜ

     

    2.ናቶሊ መሃመድ ነጂብ       የቀረበ የለም

     

    3.ሐናን መሃመድ ነጂብ

     

    ተጠሪ፡-አቶ ዑስማን ዓሊ - ጠበቃ ይማጅ ዮኒስ ቀረቡ

     

    መዝገቡን መርምረን የሚከተለውን ፍርድ ሰጥተናል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ የአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅን መሠረት ያደረገ ሁኖ የጉዳት ካሣ ክፍያን የሚመለከት ነው፡፡ ክርክሩ የተጀመረው የአሁኑ አመልካቾች ባቀረቡት የክስ ማመልከቻ የ1ኛ አመልካች ህጋዊ ባለቤት የሌሎች አመልካቾች ወላጅ አባት የሆኑት ሟች መሃመድ ነጂብ በተጠሪ በሠራተኛነት ተቀጥረው በማገልግል ላይ እያሉ የተጠሪ ንብረት የሆነውንና የሻንሲ ቁጥር JAAKP- 34HbB7P5165፣የሞተር ቁጥሩ 4HG1-865627 የሆነና የሰሌዳ ቁጥር ያልወጣለትን አይሱዙ ተሸከርካሪ ከድሬዳዋ አዲስ አበባ ለማድረስ በማሽከርከር ላይ እንዳሉ ተጠሪ በእሩምታ ጥይት ተተኮሶባቸው ሕይወታቸው በማለፉየጉዳት ካሳ 903.000.00(ዘጠኝ መቶ ሰለሳ ሺህ) ብር እንዲከፈላቸው ይወሰንላቸው ዘንድ በፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት በተጠሪ ላይ በመሠረቱት ክስ መነሻ ነው። የአሁኑ ተጠሪም በተከሣሽነት ቀርበው ከሟች ጋር የስራ ቅጥር ውል የሌላቸው መሆኑንና ሟቹ በራሳቸው ኃላፊነትና መሪነት ለተለያዩ ሰዎች የሙያ አገልግሎት የሚሰጡ እንጂየተጠሪ ተቀጣሪ ያለመሆናቸውን፣ግንኙነቱ የሙያ አገልግሎት በመሆኑ ሊገዛ የሚገባው በፍትሐ ብሔር ሕጉ ድንጋጌዎች ነው በማለት ክሱ ውድቅ እንዲሆንላቸው ዳኝነት ጠይቀዋል፡፡

     

    የስር ፍ/ቤትም የግራ ቀኙን የቃል ክርክር እና ማስረጃዎችን ከሠማ በኋላ በተጠሪ በኩል በመጀመሪያ ደረጃ መቃወሚያነት የቀረቡትን የክርክር ነጥቦች ውድቅ በማድረግ በሟችና በተጠሪ መካከል የአሠሪና ሠራተኛ ግንኙነት የነበረ መሆኑ ተረጋግጧል የሚል ድምዳሜ ደርሶ የጉዳት ካሣውን መጠንን በተመለከተም የሟቹ የወር ደመወዝ ብር 12,000.00(አስራ ሁለት ሺህ) መሆኑን መገንዘቡን ጠቅሶ በዚሁ ወርሃዊ የደመወዝ መጠን በአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 110(3) የሞት ጉዳት ካሳው ሲሳላ ብር 720,000.00 (ሰባት መቶ ሃያ ሺህ) እንደሚሆንና


    የቀብር ማስፈጸሚያም የሁለት ወር ደመወዝ ብር 24,000.00 ሊያዝ እንደሚገባ ገልፆ በድምሩ ብር 744,000.00(ሰባት መቶ አርባ አራት ሺህ ብር) ካሳ ለአመልካቾች ሊከፈል እንደሚገባ፣ አከፋፈሉን በተመለከተም ከዚሁ ገንዘብ ውስጥ 50% የሟች ሚስት ለሆኑት ለአሁኗ 1ኛ አመልካች፣ ቀሪው 50% ደግሞ ለሟች ተወላጆች ለአሁኑ 2ኛ እና 3ኛ ተጠሪዎች ሊከፈል ይገባል በማለት ወስኗል፡፡በጉዳት ካሳ መጠኑ ላይ 10% ደግሞ ለጠበቃ አበል እንዲከፈል ሲል ወስኗል፡፡ በዚህ ውሣኔ የአሁኑ ተጠሪ ባለመስማማት ይግባኛቸውን ለፌዴራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት አቅርበው ፍርድ ቤቱ ግራ ቀኙን ከአከራከረ በኋላ ጉዳዩን መርምሮ በሟች እና በተጠሪ መካከል ያለው ግንኙነት የአሰሪና ሠራተኛ አይደለም፣ ሟች በራሳቸው ኃላፊነትና መሪነት ስራውን ሲሰሩ የነበሩ ናቸው በማለት የስር ፍርድ ቤትን ውሳኔ ሙሉ በሙሉ ሽሮታል፡፡ የአሁኑ የሠበር አቤቱታ የቀረበውም ይህንኑ የበታች ፍ/ቤቶችን ውሣኔ በመቃወም ለማስለወጥ ነው፡፡

     

    የአመልካቾች ጠበቃ መስከረም 27 ቀን 2007 ዓ.ም በፃፉት 4/አራት/ ገፅ የሠበር አቤቱታ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ውሣኔ መሠረታዊ የሆነ የህግ ስህተት ተፈፅሟል የሚሉባቸውን ምክንያቶች ዘርዝረው አቅርበዋል፡፡ ይዘቱም ባጭሩ፡-ሟች ሹፌር ሁነው ለተጠሪ ሲሰሩ የነበሩ መሆኑ በተረጋገጠበት ሁኔታ በራሳቸው ኃላፊነትና መሪነት የሙያ አገልግሎት ሲሰጡ የነበሩ ናቸው ተብሎ ግንኙነቱ በአሰሪና ሰራተኛ ጉዳይ ህግ አይገዛም ሲባል የተወሰነው ውሳኔ ስለሙያ አግባብነት ባላቸው ሕጎች የተቀመጠውን መስፈርት ያላገናዘበ በመሆኑ ሊታረም የሚገባው ነው በማለት መከራከራቸውን የሚያሳይ ነው፡፡ አቤቱታው ተመርምሮም በዚህ ችሎት እንዲታይ በመደረጉ ተጠሪ ቀርበው ግራ ቀኙ በፅሑፍ እንዲከራከሩ ተደርጓል፡፡

     

    የጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለ መልኩ ከላይ የተገለፀው ሲሆን ይህ ችሎትም የግራ ቀኙን የጽሑፍ እና የቃል ክርክር የሠበር አቤቱታው ከቀረበበት ውሣኔ እና አግባብነት ከላቸው የህግ ድንጋጌዎች ጋር አገናዝቦ በሚከተለው መልኩ መርምሮታል፡፡ እንደመረመረውም የዚህን ችሎት ምላሽ የሚያስፈልጋቸው አበይት ጭብጦች፡-

     

    1.  በተጠሪ እና በሟች መካከል የነበረው ግንኙነት በአዋጅ ቁጥር 377/96  ድንጋጌዎች አግባብ የሚገዛ ነው? ወይስ አይደለም?

    2.  ከተባለስ የጉዳት ካሳ መጠኑ ምን ያህል ሊሆን ይገባል? የሚሉት ሁነው አግኝተናል፡፡

     የ መጀ መሪያ ውን ጭ ብጥ በተመ ለከተ፡-

     

    ከክርክሩ ሂደት መገንዘብ የተቻለው ሟች ህይወታቸው ያለፈው በሹፌነታቸው የተጠሪ ንብረት የሆነውን መኪና ከድሬዳዋ ወደ አዲስ አበባ በማሽከርከር ላይ እንዳሉ በተከፈተባቸው እሩምታ ተኩስ መሆኑን፣ሟች አንድ ጊዜ መኪና ሲያደርስ ብር 800.00 (ስምንት መቶ) ብር ለመከፈል ተጠሪ መስማማታቸውን ተጠሪ ባቀረቡት ክርክርም ሆነ የአመልካቾች ምስክሮች መረጋገጡን የስር ፍርድ ቤት በውሳኔው ላይ በግልጽ ያሰፈረው ጉዳይ መሆኑን ነው፡፡ በሟችና በተጠሪ መካከል እንደዚህ አይነት ስምምነት የተደረገው ከሚያዚያ ወር 2002 ዓ/ም ጀምሮ መሆኑንና የሞት አደጋው የደረሰው ደግሞ የካቲት 08 ቀን 2003 ዓ/ም ስለመሆኑ በአመልካቾች ማስረጃዎች የተነገረ መሆኑንም ከስር ከበታች ፍርድ ቤቶች የውሳኔ ይዘት ተመልክተናል፡፡

     

    ይህንኑ ለመመለስም በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አሰሪና ሰራተኛ ማን ነው የሚለውን ጉዳይ መመልከቱ የግድ ይላል፡፡ ይህ ጥያቄ ምላሽ ሊያገኝ የሚችለውም በአዋጁ የሚገዙት የትኞቹ አሰሪዎች እና ሰራተኞች ናቸው? የሚለው ጥያቄ መሰረት በማድረግ መሆኑ ይታመናል፡፡


    በመሰረቱ አዋጅ ቁጥር 377/1996 በአንቀፅ 2/3/ ስር ሰራተኛ ማለት በዚህ አዋጅ አንቀፅ 4 ስር በተመለከተው መሰረት ከአሰሪ ጋር በቅጥር ላይ የተመሰረተ የስራ ግንኙነት ያለው ግለሰብ ነው በማለት በግልፅ ያስቀምጣል፡፡ በመሆኑም ይህ ሰራተኛ ለአሰሪው በአሰሪው ቁጥጥር ስር ሁኖ አሰሪው በሚከፍለው ደሞዝ በራሱ የጉልበት ወይም የእውቀት አገልግሎት ለተወሰነ ጊዜ ወይም ስራ ወይም ላልተወሰነ ጊዜ የሚሰጥ መሆኑን አዋጅ ያስገነዝባል፡፡ በሌላ በኩል አዋጁ በአንቀፅ 2/1/ ስር አሰሪ ማለት አንድ ወይም ከአንድ በላይ የሆኑ ሰዎችን በዚህ አዋጅ አንቀጽ 4 በተመለከተው መሰረት ቀጥሮ የሚያሰራ ግለሰብ ወይም ድርጅት ሊሆን እንደሚችል በመግለፅ ድርጅት የሆነውን አሰሪ በማየት አሰሪ ማን ነው? የሚለውን ጥያቄውን ለመፍታት የሚያስችል መሆኑ የሚያስረዳ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ጥያቄውን ስንመለከተውም አሰሪው  ግለሰብ ወይም ድርጅት ሲሆን የስራ ውሉ ግንኙነት በአዋጅ የሚገዛ መሆኑን፣ አሰሪው ከነዚህ ውጭ ከሆነ እንደሁኔታው የሌሎች ህጎች ድንጋጌዎች ተፈፃሚነት የሚኖራቸው መሆኑን ሕጉ የሚያመለክት መሆኑን መረዳት የምንችለው ጉዳይ ይሆናል፡፡ በአዋጁ ስለሰራተኛ የተቀመጠው ትርጉም የሚያሳየው በአዋጁ አንቀጽ 4 በተመለከተው መሰረት ከአሰሪ ጋር በቅጥር ላይ የተመሰረተ የስራ ግንኙነት ያለው ግለሰብ መሆኑን አንቀጽ 2(3) በግልጽ ያሳያል፡፡ በዚህ ድንጋጌ ይዘት አንድን ሰው ሰራተኛ ነው ለማለት በቅጥር ላይ የተመሰረተ የስራ ግንኙነት መኖሩና በአዋጁ አንቀጽ 4 ድንጋጌ አግባብ መሰረት ሰራተኛው አገልግሎት ለመስጠት መስማማቱ፣ሰራተኛው አገልግሎት የመስጠት ግዴታ ያለበት መሆኑንና ሰራተኛው ሊሰጥ የሚገባውን አገልግሎት አይነት፣ የት አገልግሎቱን መስጠት እንደአለበት፣አገልግሎቱን መቼ ሊያከናውነው እንደሚገባና እንዴት ማከናወን እንደሚኖርበት አሰሪው የመቆጣጣር ስልጣን ያለው መሆኑ መረጋገጥ ያለባቸው መሆኑን ነው፡፡ አሰሪው ሰራተኛውን በዚሁ በህጉ በተቀመጠው አግባብ ተቆጣጥሮ ስራውን የሚያሰራ መሆኑ መረጋገጡ አንድ ተዋዋይ ወገን ዋጋ እየተከፈለው የንግድ ስራ ወይም በራሱ የሙያ ኃላፊነት የሚሰራ ስራ ከሚያከናውን ወገን በትክክል ለመለየት የሚረዳ መሆኑም ተቀባይነት ያለው መለኪያ ነው፡፡በአዋጁ ለቅጥር ውሉ ከተሰጠው ትርጉም መካከል አንዱ የደመወዝ ጉዳይ ሲሆን ሰራተኛው ለአሰሪው በገባው ለአሰሪው ጥቅምና በአሰሪው ቁጥጥር ችሎታውንና ጊዜውን በመጠቀም ተገቢውን አገልግሎት ለአሰሪው ለመስጠት ግዴታ የሚገባው አሰሪው ለሰራተኛው ተገቢውን የድካም ዋጋ በደመወዝ መልክ የመክፈል ግዴታ ሲገባነው፡፡ ደመወዝ ደግሞ በጥሬ ገንዘብ ወይም በአይነት ሊሆን የሚችል ሁኖ የአከፋፈሉ ጊዜም አንደነገሩ ሁኔታ በየቀኑ፣በየሁለት ቀኑ፣ በየሁለት ሳምንቱ፣በየወሩ፣በተሰራው ሰራ መጠን……ወዘተ ሊሆን እንደሚችል ከአዋጁ አንቀጽ 4 እና 58 ድንጋጌዎች ይዘትና መንፈስ የምንገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡በመሆኑም በእነዚህ የአከፋፈል ጊዜያት ወይ ዘዴዎች ደመወዝ የመከፈሉ ሁኔታ በአሰሪና ሰራተኛ መካከል በተመሰረተው የቅጥር ሁኔታ ላይ በሕጉ ረገድ ለውጥ የማያስከትል መሆኑን መገንዘብ ይቻላል፡፡

     

    ወደተያዘው ጉዳይ ስንመለስም ሟች ተጠሪ ግለሰብ ከውጪ ከሚያስመጣቸው ተሽከርካሪዎች ውስጥ ከድሬዳዋ ወደ አዲስ አበባ በማመላለስ አገልግሎት ሲሰጡ እንደነበርና ስራውን የሚሰራው ጊዜና ቦታ መኖሩን፣ይህም በተጠሪው መሪነት ወይም ቁጥጥር ሲከናወን የነበረ መሆኑን የክርክሩ ሂደት ያሳያል፡፡ተጠሪ ሟቹ ሲከፈላቸው የነበረው ደወመዝ በቁርጥ መሆኑን ጠቅሰው ከመከራከራቸው ውጪ ሟቹ የሚሰጡትን አገልግሎት በራሳቸው ቁጥጥር ስር ያልነበረ መሆኑን አላስረዱም፡፡ የደመወዝ አከፋፈል በቁርጥ መሆኑ ደግሞ የቅጥር ግንኙነት ከላይ በተመለከቱት የአዋጁ ድንጋጌ ስለ ሰራተኛ ማንነት የተቀመጠውን ትርጉም ላለመቀበል የሚያስችል አይደለም፡፡ ከዚህ አንፃር  ጉዳዩን  ስንመለከተው ሟች  በተጠሪ ቁጥጥር ስር  ሁነው የሹፍርና አገልግሎት


    ሲሰጡ የነበረ መሆኑ በሚገባ የተረጋገጠ ሁኖ እያለ የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሟች በራሱ የሙያ ኃላፊነት ሲሰሩ የነበሩ ናቸው በማለት ግንኙነቱ በአዋጅ  ቁጥር  377/96 የሚገዛ አይደለም በማለት የስር ፍርድ ቤትን ውሳኔ መሻሩ በሕጉ ስለሰራተኛ ማንነት የተቀመጡ መለኪያዎችን በአግባቡ ባላገናዘበ መልኩ ሁኖ አግኝተናል፡፡ በመሆኑም ውሳኔው የአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 2(1)(2)፣3(2(ረ))፣ 4 እና 58 ድንጋጌዎችን ይዘትና መንፈስ የጣሰ በመሆኑ መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት ያለበት ሁኖ አግኝተናል፡፡

     

     ሁ ለተ ኛ ውን ነጥ ብ በተ መለከተ-ሟች የተጠሪ ሠራተኛ ናቸው ከተባለ በስራ ላይ እያሉ ሕይወታቸው ማለፉ ግራ ቀኙን ያላከራከረ ጉዳይ ነው፡፡ በስራ ምክንያት ለሚመጡ ጉዳቶች አሠሪው ሀላፊነት አለበት፡፡ ስለዚህ በስራ ምክንያት የሚመጣ ጉዳት ከሆነ አሠሪው ኃላፊነቱን እንዲወስድ የተደረገ ሲሆን በአዋጁም በስራ ላይ የሚደርስ ጉዳት ማለት በስራ ላይ የሚደርስ አደጋ ወይም በስራ ምክንያት የሚመጣ በሽታ መሆኑን በቁጥር 95(2) ደንግጓል በአዋጅ አንቀጽ 96(1) ”አሠራው ጥፋት ባይኖረውም…..” ተብሎ መመልከቱ የአሠሪው የኃላፊነት ዓይነት ጥፋት ሣይኖር ኃፊነት /Strict Liability or Liability in the absence of Fault/ መሆኑን የሚያሣይ ነው፡፡ አሠሪው ከዚህ ዓይነት ኃላፊነት የሚድነው ጉዳት የደረሠበት ሠራተኛ ሆነ ብሎ በራሡ ላይ ያደረሠው ጉዳት መሆኑን ማስረዳት ሲችል ስለመሆኑ አንቀጽ 98(2) ያስገነዝባል፡፡ሆነ ብሎ ያደረሠው ጉዳት የሚባሉት ሁኔታዎችም ሠራተኛው አስቀድሞ በግል የተሠጡትን የደህንነት መጠበቂያ መመሪያዎችን መጣስ ወይም የአደጋ መከላከያ ደንቦችን መተላለፍ ወይም አካሉን ወይም አእምሮውን በሚገባ ለመቆጣጠር በማይችልበት ሁኔታ በመጠጥ ወይም በአደንዛዥ እፅ ሠክሮ በሥራ ላይ መገኘት መሆናቸውን ህጉ በቁጥር 96(2(ሀ እና ለ)) ስር አመላክቷል፡፡

     

    የአዋጁ አንቀጽ 97(1) ድንጋጌ ሲታይም አንድን አደጋ በስራ ላይ የደረሠ ነው ለማለት ሠራተኛው ስራውን በማከናወን ላይ እያለ ወይም ከስራው ጋር ግንኙነት ባለው ሁኔታ ከራሡ ውጭ በሆነ ምክንያት ወይም ስራውን ለማከናወን ባደረገው ጥረት ምክንያት በአካሉ ወይም በአካሉ በማንኛውም ክፍል ተፈጥሯዊ እንቅስቃሴ ላይ በድንገት የደረሠበት ጉዳት ስለመሆኑ መርሁን ያስቀመጠ ሲሆን ይኽው ድንጋጌ ከፊደል (ሀ) እስከ ፊደል (መ) በተመለከቱት ንዑስ ድንጋጌዎች የተመለከቱት ምክንያቶች በስራ ላይ የደረሠ አደጋ ተብለው የሚጨመሩ ስለመሆኑ ያሣያል፡፡ ስለሆነም በመርሁ መሠረት ሠራተኛው የጉዳት ካሣ ለማግኘት ማሣየት የሚጠበቅበት አደጋው ስራውን በማከናወን ላይ እያለ የደረሠ መሆኑን፣ ወይም ደግሞ በራሡ ባልሆነ ምክንያት ግን ከሥራው ጋር ግንኙነት ባለው መልኩ የደረሠበት አደጋ መሆኑን ነው ፡፡ከላይ እንደተገለፀው ከስራ ጋር ግንኙነት ያላቸው ሁኔታዎች ምን እንደሆኑ ህጉ አስቀምጧል፡፡ ለዚህ ጉዳይ ቀጥተኛ አግባብነት ያለው ድንጋጌ በአንቀጽ 97(1(ሐ)) ስር የተመለከተው ሲሆን በዚህ ድንጋጌ መሠረት አሠሪው በመደበው የመጓጓዝ አገልግሎት ሠራተኛው ሲጠቀም ጉዳት ከደረሠ አደጋው በስራ ላይ እንደደረሠ ተቆጥሮ ኃፊነቱን ከአሠሪው ሊወሰድ የሚገባ መሆኑ ተመልክቷል፡፡ ይኽው ድንጋጌ አሠሪው የመደበው የመጓጓዝ አገልግሎት አደጋው ከደረሠበት በአሰሪው ስር ባለው ሌላ ሠራተኛ ወይም 3ኛ ወገን ከሆነ አሰሪው ለተጐጂው ሠራተኛ የጉዳት ካሣ ኃፊነት የሌለበት ስለመሆኑ አያሣይም ይልቁንም ድንጋጌው በአዋጁ አንቀጽ 96(1) ስር ከተመለከተው የአሠሪ አላፊነት ዓይነት ጋር ተዳምሮ ሲታይ አሠሪው አላፊነት ያለበት መሆኑን የሚያጠናክር ነው በሌላ አገላለፅ በሠራተኛው ላይ ጉዳት ያደረሠው ሠራተኛው ወደ ስራ ሲሄድና ከስራ ወጥቶ ወደ ቤቱ ሲመለስ አሠሪው በመደበው የመጓጓዠ አገልግሎት ሲጠቀም አደጋ የደረሠበት መሆኑ ከተረጋገጠ 3ኛ ወገኖች ለአደጋው ያደረጉት አስተዋጽኦ ለአሰሪው    መከላከያ


    ሊሆን አይችልም፡፡ በመሆኑም ሟች የተጠሪን መኪና በወቅቱ ሲያሽከረክሩ የነበሩ መሆኑ መረጋገጡ ተጠሪን ነፃ ሊያደርገው የሚችልበት ህጋዊ ምክንያት ስለሌለ ተጠሪ ለጉዳቱ ኃላፊነት ያለባቸው ናቸው፡፡

     

    ተጠሪ ለጉዳቱ ኃላፊ ናቸው ከተባለ የጉዳት ካሣ መጠኑ ምን ያህል ሊሆን ይገባል?፣ ካሳው መክፈል ያለበት ለየትኞቹ የተጐጂ ጥገኞች ነው? የሚለው ጥያቄም በህጉ አግባብ መታየት ያለበት ነው፡፡ ለዚህጥያቄ ምላሽ የሚሠጠው ድንጋጌም በአዋጅ ቁጥር 377/96  አንቀጽ 107(1(ሐ) ስር ተመልክቷል፡፡ በዚህ ድንጋጌ መሠረት ማንኛውም በስራ ላይ የሚመጣ ጉዳት የደረሠበት ሠራተኛ የሞተ እንደሆነ ለጥገኞች የጡረታ አበል ወይም ዳረጐት ወይም ካሣ የማግኘት መብት ያለው ስለመሆኑ ተመልክቷል፡፡የአዋጁ አንቀጽ 110 ድንጋጌ ሲታይም ለሟች ሠራተኛ ጥገኞች የሚከፍሉትን የክፍያ ዓይነቶችንና ጥገኛ የሚባሉትን ወገኖች በንዑስ ቁጥር አንድና ሁለት በግልፅ ዘርዝሯል፡፡ በዚህም መሠረት ማንኛውም ሠራተኛ ወይም ለማጅ ሠራተኛ በስራ ምክንያት በደረሠበት ጉዳት የተነሣ የሞተ እንደሆነ የጉዳት ካሣ ለጥገኞች፣ የቀብር ሥነ ሥርዓት ወጪ እንደሚከፈልና ጥገኞች የሚባሉትም የሟች ህጋዊ ባል ወይም ሚስት፣ ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ የሟች ልጆችና በሟች ሠራተኛ ድጋፍ ይረዱ የነበሩ የሟች ወላጆች ስለመሆናቸው ተመልክቷል፡፡

     

    ወደ ተያዘው ጉዳይ ስንመለስም 1ኛ አመልካች የሟች ሚስት፣ ሌሎች ተጠሪዎች ደግሞ ተወላጅ ናቸው፡፡ በመሆኑም አመልካቾች በህጉ አግባብም የሟች ጥገኛ መሆናቸው ስለተረጋገጠ የጉዳት ካሣ የሚገባቸው ሆኖ ተገኝቷል፡፡

     

    የጉዳት ካሳ መጠኑም በሰራተኛው በስራ ላይ እያለ የሞተ እንደሆነ የሰራተኛው የዓመት ደሞዝ በአምስት ተባዝቶ የሚከፈል እንደሆነ አንቀፅ 110(3) ተመልክቷል፡፡ይህንኑ ለመወሰን ደግሞ የሰራተኛው ደመወዝ መጠኑ በትክክል ሊታወቅ ይገባል፡፡በተያዘው ጉዳይ የፌዴራሉ መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የሟችን ደመወዝ መጠን በወር 12,000.00 ያደረገው በወር ውስጥ አስራ አምስት ቀናትን ለተጠሪ አገልግሎት ለመስጠት ይችላሉ በሚል መነሻ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በዚህ ረገድ በግልጽ የቀረበ ማስረጃ የለም፡፡በፍሬ ነገር ደረጃ በሚገባ የተረጋገጠው ሟች ከድሬዳዋ ወደ አዲስ አበባ ለሚያደርሱት አንድ ተሸከርካሪ ብር 800.00(ስምንት መቶ ) የሚከፈላቸው መሆኑ ነው፡፡ይህ ደግሞ ሟች በወር አስራ አምስት ቀናት ሙሉ ስራውን ይሰራሉ ተብሎ ስላልተረጋገጠ የወርሃዊ ደመወዝ መጠን በብር 800.00 ሊታሰብ የሚገባው ሁኖ አልተገኘም፡፡በመሆኑም ይህ ችሎት የሟች ወርሃዊ ደመወዝ ከብር 3200.00 ሊበልጥ የሚችልበትን አግባብ አላገኘም፡፡ ይኼው የደመወዝ መጠን መሰረት ተደርጎ አመታዊ ደመወዝ ሲሰላ ደግሞ ብር 38,400.00(ሰላሳ ስምንት ሺህ አራት መቶ ብር) ሁኖ በአዋጁ አንቀጽ 110(3) መሰረት የአምስት ዓመቱ ሲሰላ ብር 192,000.00(አንድ መቶ ዘጠና ሁለት ሺህ ብር) የጉዳት ካሳ ሊሆን የሚገባው ሁኖ አግኝተናል፡፡

     

    የቀብር ሥርዓት ማስፈፀሚያ ክፍያ በአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 110(1(ለ) መሠረት ሲሰላም የሁለት ወር ደመወዝ ብር 6,400.00(ስድስት ሺህ አራት መቶ ብር) መሆን ያለበት ሁኖ አግኝተናል፡፡

     

    በአጠቃላይ 198,400.00 (አንድ መቶ ዘጠና ስምንት ሺህ አራት መቶ ብር) የሟች ጥገኛ ለሆኑት ለአሁኑ አመልካቾች በአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 110(3) እና (4) ስር በተመለከተው


    አግባብ የሚከፈል የጉዳት ካሣ መጠን ሁኖ አግኝተናል፡፡ ሲጠቃለልም የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ውሳኔ ሙሉ በሙሉ፣ የፌዴራሉ መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ውሳኔ ደግሞ በከፊል መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት ያለባቸው በመሆኑ ተከታዩን ወስነናል፡፡

     

     ው ሣ ኔ

     

    1. በፌዴራሉ ከፍ/ፍ/ቤት በመ/ቁ 09770 ሐምሌ 23 ቀን 2006  ዓ/ም  ውሣኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 348(1) መሠረት ተሽሯል፡፡

    2. በፌዴራሉ መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት በኮ/መ/ቁ 38410 ጥር 26 ቀን 2006 ዓ.ም እና መጋቢት 29 ቀን 2006 ዓ.ም የተሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰረት ተሻሽሏል፡፡

    3. በሟች እና በተጠሪ መካከል የአሰሪና ሰራተኛ ግንኙነት ውል አለ፣ ሟቹ የሞቱት በስራ ላይ እያሉ በመሆኑ ለሟቹ ጥገኞች የሞት ጉዳት ካሳ የሟቹ የአምስት አመት ደመወዝና የሁለት ወር ደመወዝ ለቀብር ስነ ስርዓት ማስፈፀሚያ ተጠሪ የመክፈል ኃላፊነት አለባቸው ብለናል፡፡

    4. ተጠሪ ለአመልካቾች የሚከፍሉት የካሳ መጠንም ብር 198,400.00(አንድ መቶ ዘጠናስምንት ሺህ አራት መቶ) ሁኖ አከፋፈሉም በአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 110(3(ሀ) ((ለ)) በተመለከተው አግባብ 50% ለ1ኛ አመልካች (የሟች ሚስት) ቀሪው 50% ደግሞ ለሟች ልጆች (2ኛ እና 3ኛ አመልካቾች) ሊሆን ይገባል ብለናል፡፡ የጠበቃ አበል በዚህ ችሎት በተወሰነው የገንዘብ መጠን 10% ተጠሪ ለአመልካቾች ሊተኩ ይገባል ብለናል፡፡

    5.  ሌሎች ወጪና ኪሳራዎች የየራሳቸውን ይቻሉ ብለናል፡፡ መዝገቡ ተዘግቷል፤ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ፡፡

     

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

  • ከስራ በቅነሳ ምክንያት ለሚሰናበት ሠራተኛ የስራ ስንብት ክፍያ የሚከፈል ስለመሆኑ፡-

     

    አዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀፅ 39(1)(ሐ)፣40(1)(3)፣28(2)(ሀ)(3)

    የሰ.መ.ቁ. 105620

     

    ሚያዝያ 13 ቀን 2007 ዓ.ም

     

    ዳኞች፡- አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሱልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመሰል

    አመልካቾች፡-1. አቶ ሀብቴ ብርሃኔ

     

    2. አቶ በየነ ለሜቻ

     

    3. አቶ ግርማ አንጉራ

     

    4. አቶ ጌትነት ዘውዴ               ጠበቃ አቶ ሣሙኤል ሽፈራው - ቀረቡ

     

    5. አቶ ጥላሁን ተክለመድህን

     

    6. አቶ ተመስገን ግርማ

     

    ተጠሪ፡- አቶ ሙሉነህ ቡና ላኪ ትራንስፖርትና ትሪንዚት አገልግሎት - ጠበቃ ፈጠነ ደረሰ ቀረቡ መዝገቡን መርምረን የሚከተለውን ፍርድ ሰጥተናል።

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ የቀረበው አመልካቾች መዝገብ ቁጥር 140043 ሐምሌ 3 ቀን 2006 ዓ.ም የሰጠው ውሣኔ መሠረታዊ የሕግ ስህተት ያለበት ስለሆነ በሰበር ታይቶ እንዲታረምልን በማለት ያቀረቡትን የሰበር አቤቱታ አጣርቶ ለመወሰን ነው፡፡ ጉዳዩ የሥራ ስንብት የሁለት ወር ደመወዝ ይከፈለን በማለት የቀረበ ጥያቄ የሚመለከት ነው፡፡ ጉዳዩ በመጀመሪያ የታየው በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ነው፡፡ በሥር ፍርድ ቤት አመልካቾች ከሳሽ ተጠሪ ተከሳሽ በመሆን ተከራክረዋል፡፡

     

    1. የክርክሩ መነሻ አመልካቾች ያቀረቡት ክስ ነው፡፡ ከሳሾች ተከሳሽ በሹፌርነት ተመድባችሁ የምታሽከረክሩት መኪና ተሸጧል በሚል ምክንያት የሁለት ወር ማስጠንቀቂያ ከሰጠን በኃላ የሥራ ውላችን አቋርጧል፡፡ ተከሳሽ የሥራ ውሉን በቅነሳ ምክንያት ማቋረጥ ሲገባው አላግባብ የሥራ መደብ ተሰርዟል በማለት ያቋረጠው በመሆኑ በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ ህግ መሠረት ሊከፍል የሚገባውን የሁለት ወር ደመወዝ የሥራ ስንብት ክፍያ ያልከፈለ በመሆኑ እንዲከፍል ውሣኔ ይስጥልን በማለት ክስ አቅርበዋል፡፡ ተጠሪ በሥር ፍርድ ቤት ተከሳሽ


    ሆኖ ቀርቦ ከሳሾች የሚያሽከረክሯቸው መኪኖች በመሸጣቸው የሥራ መደቡ ተሰርዟል፡፡ ስለዚህ ተከሳሾች የስራ ስንብት ክፍያ የምንከፍልበት ምክንያት የለም በማለት ተከራክሯል፡፡

    2. የሥር ፍርድ ቤት የግራ ቀኙን ክርክርና ማስረጃ ከመረመረ በኃላ ተከሳሽ ኪሣራ አልደረሰበትም፡፡ ኪሳራ የደረሰበት ራሱን የቻለ የህግ ሰውነት ያለው የቡና ላኪ ድርጅት ላይ ነው፡፡ ከሳሾች የሚያሽከረክሯቸው መኪኖች የተሸጡትም የቡና ላኪ ድርጅት ዕዳ መክፈያነት ነው፡፡ ተከሳሽ የሥራ ውሉን ከሳሾች የሚያሽከረክሯቸው መኪኖች በቡና ላኪ ድርጅት ላይ በደረሰው ኪሣራ ምክንያት በዕዳ መክፈያነት በመሸጣቸው የሥራ ውሉን ያቋረጠ በመሆኑ፣የሥራ ውሉ የተቋረጠው በቅነሳ እንጂ የሥራ መደብ በመሠረዙ ምክንያት አይደለም፡፡ ይህም በመሆኑ ከሳሽ በተከሳሾች የሁለት ወር ደመወዝና አገልግሎት ጊዜአቸውን አስልቶ የሥራ ስንብት ክፍያ የመክፈል ኃላፊነት አለበት በማለት ውሣኔ ሰጥቷል፡፡

    3. አመልካች በዚህ ውሣኔ ቅር በመሰኘት ይግባኝ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቅርቧል፡፡ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኃላ መልስ ሰጭዎች ያሽከረከሯቸውየነበሩት መኪናዎች መሸጣቸው ተረጋግጧል፡፡ መልስሰጭዎች ያሽከረክሯቸው የነበሩ መኪናዎች መሸጣቸው ከተረጋገጠ ይግባኝ ባይ ሌላ መኪና ገዝቶ እስኪተካ ድረስ የሹፌርነት የሥራ መደብ ተሰርዟል ለማለት ይቻላል፡፡ ይግባኝ ባይ መልስ ሰጭዎችን የሥራ መደብ በመሰረዙ ምክንያት ከሥራ ያሰናብታቸው በመሆኑ የሥራ ስንብት ክፍያ ሊከፍል አይገባም በማለት የሥር ፍርድ ቤት የሰጠውን ውሣኔ ሽሮታል፡፡

    4. አመልካቾች መስከረም 27 ቀን 2007 ዓ.ም በተፃፈ የሰበር አቤቱታ ተጠሪ ካሉት ከመቶ በላይ ከሚሆኑ ሹፌሮች ዝቅተኛ አገልግሎትና የሥራ ልምድ በመምረጥ ቀንሶ ከሥራ አሰናብቶናል፡፡ ከዚህ አንፃር የተጠሪ አድራጎት ቅነሳ እንጂ የሥራ መደብ መሠረዝ ነው ሊባል አይገባውም፡፡ ከዚህ በተጨማሪ አሰሪው ሠራተኛውን ከሥራ ሲያሰናብት የአገልግሎት ክፍያ የመክፈል ሃላፊነት አለበት፡፡ በመሆኑም ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት የስራ ስንብት ክፍያ አይገባችሁም በማለት የሰጠው ውሣኔ መሠረታዊ የሕግ ስህተት ያለበት ስለሆነ በሰበር እንዲታይልን በማለት አመልክተዋል፡፡ ተጠሪ ጥር 28 ቀን 2007 ዓ.ም በተፃፈ መልስ አመልካቾች የተሰናበቱት የሥራ መደቡ የተሠረዘ በመሆኑ ምክንያት ነው፡፡ ይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት ይህንን በማገናዘብ የሥራ ስንብት ክፍያ ተጠሪ የመክፈል ኃላፊነት የለበትም በማለት የሰጠው ውሣኔ የሕግ ስህተት የለበትም በማለት ተከራክሯል፡፡ አመልካችዎች የካቲት 14 ቀን 2007 ዓ.ም የተፃፈ የመልስ መልስ አቅርበዋል፡፡

    5. ከሥር የክርክሩ አመጣጥና በሰበር ግራ ቀኙ ያቀረቡት ክርክር ከላይ የተገለፀው ሲሆን እኛም ይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት ተጠሪ ለአመልካቾች የሥራ ስንብት ክፍያ ሊከፍል አይገባም በማለት የሰጠው ውሣኔ የሕግ መሠረት አለው ወይስ የለውም? የሚለውን ጭብጥ በመያዝ ጉዳዩን መርምረናል፡፡

    6. አሠሪው ማስጠንቀቂያ በመስጠት የሥራ ውል ለማቋረጥ የሚችልባቸውን መሠረታዊ ምክንያቶች አዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 28 በሁለት ከፍሎ አስቀምጧቸዋል፡፡ የመጀመሪያው ከሠራተኛው ችሎታ ማጣት ወይም ሁኔታ የሚመለከቱ ምክንያቶችም ሲሆኑ በአዋጅ አንቀፅ 28 ንዑስ አንቀጽ 1 ከ’’ሀ’’ እስከ ‘’መ’’ በዝርዝር ደንግጓል፡፡ ሁለተኛው ከአሠሪው ድርጅታዊ አቋም ወይም የሥራ እንቅስቃሴ የሚመለከቱ ምክንያቶች የሥራ ውል ሲቋረጥ መሆኑ በአዋጅ አንቀጽ 28 ንዑስ አንቀጽ 2 ተመልክቷል፡፡ ተጠሪ አመልካቾች የሚያሽከረክሯቸው መኪኖች በዕዳ ምክንያት በመሸጣቸው የአመልካችዎች የሥራ መደብ በአዋጅ አንቀጽ 28 ንዑስ አንቀጽ 1 (መ) መሠረት ተሰርዟል በማለት የሚያቀርበው ክርክር ተጠሪ ከፈፀመው ተግባር አግባብነት ያለው ሆኖ አላገኘነውም፡፡


    7. አመልካችዎች የሚያሽከረክሯቸው መኪኖች የተሸጡት በተጠሪ ድርጅታዊ አቋምና የሥራ እንቅስቃሴ ምክንያት በመሆኑና በተለይም ቡና የሚልከው የንግድ ድርጅት  ኪሣራ ስለደረሰበት መኪኖቹ ተሸጠው ዕዳ መክፈያነት የዋሉ መሆኑ በሥር ፍርድ ቤት ተረጋግጧል፡፡ አንድ ድርጅት ሠራተኞች የተሰማሩባቸው ሥራዎች በከፊልም ሆነ በሙሉ በቀጥታና በሌላ ቦታው የሚያስቆምና የሠራተኞች ቅነሳ የሚያስከትል ሁኔታ ሲያጋጥመው ማስጠንቀቂያ በመስጠት የሥራ ውሉን ሊያቋርጥ እንደሚችል በአዋጅ አንቀጽ 28 ንዑስ አንቀጽ 2(ሀ) ተደንግጓል፡፡ የተጠሪም አድራጎት በዚህ ድንጋጌ ሥር የሚሸፈን ሆኖ አግኝተነዋል፡፡

    8. ሰለ ሥራ ስንብት ክፍያ የሚደነግገው የአዋጅ ቁጥር 377/96 ምዕራፍ ሶስት በክፍል ሁለት የሙከራ ጊዜውን የጨረሰ ሰራተኛ በዚህ አዋጅ በተመለከቱት ሁኔታዎች መሠረት ከሥራ ሲቀነስ የሥራ ስንብት ክፍያ የማግኘት መብት ያለው መሆኑ በአንቀጽ 39 ንዑስ አንቀጽ 1(ሐ) በግልፅ ይደነግጋል፡፡ ከዚህ አንፃር ሲታይ በተጠሪ ድርጅታዊ አቋምና የሥራ እንቅስቃሴ ምክንያት ከሥራ የተቀነሱት አመልካቾች በአዋጁ አንቀጽ 40 ንዑስ አንቀጽ  1 እና ንዑስ አንቀጽ 3 የተመለከቱትን የሥራ ስንብት ክፍያዎች የማግኘት መብት ያላቸው መሆኑ ከድንጋጌዎቹ ይዘት መንፈስና ዓላማ የምንረዳው ጉዳይ ሆኖ እያለ ይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት አመልካችዎች የሚያሽከረክሯቸው መኪናዎች በዕዳ ምክንያት መሸጥ ከተጠሪ ድርጅታዊ አቋምና የሥራ እንቅስቃሴ ነጥሎ በማየት ተጠሪ ለአመልካችዎች የሥራ ስንብት ክፍያ የመክፈል ግዴታ የለበትም በማለት የሰጠው ውሣኔ የአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 28 ንዑስ አንቀጽ 2(ሀ) ና ንዑስ አንቀጽ 3 አንቀጽ 39 ንዑስ አንቀጽ 1 (ሐ) እና የአዋጁን አንቀጽ 40 ንዑስ አንቀጽ 1 እና ንዑስ አንቀጽ 3 ያላገናዘበና መሠረታዊ የሕግ ስህተት ያለበት ነው በማለት ወስነናል፡፡

     

     ው ሳ ኔ

    1.  የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሰጠው ውሣኔ ተሽሯል፡፡

    2. ተጠሪ ለአመልካችዎች የሥራ ስንብት ክፍያ የመክፈል ኃላፊነት አለበት በማለት ወስነናል፡፡

    3. ተጠሪ ለአመልካችዎች በአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጽ 40 ንዑስ አንቀጽ 1 ንዑስ አንቀጽ 2 እና ንዑስ አንቀጽ 3 መሠረት በማስላት የሥራ ስንብት ክፍያ ይክፈላቸው በማለት ወስነናል፡፡

    4. በዚህ ፍርድ ቤት ያወጡትን ወጭና ኪሣራ ግራቀኙ ለየራሳቸው ይቻሉ መዝገቡ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ፡፡


     

    የ/ማ


    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

  • Family law

    Rural land law

    Pecuniary effect of marriage

    Common property

    Rural land proclamation no. 110/1999 art. 5(5) and 2(7) of southern Regional state

     

    ባል እና ሚስቶች ሲጋቡ ለጎጆ መውጫ ተብሎ በቤተሰባቸው ፍቃድ የተሰጣቸው መሬት ሲገለገሉበት የቆዩ በሆነ ጊዜ ንብረቱ የጋራ ሀብት ሀኖ በፍቺ ጊዜ እኩል ሊካፈሉት የሚገባ ስለመሆኑ፣

    የደ/ብ/ብ/ሕ/ክ/መ/ የመሬት አዋጅ ቁጥር 110/1999 አንቀጽ 5/5/,2/7/

    107840

  • Family law

    Divorce

    Divorce based on mutual agreement

    Power of court

    Federal family code art. 76(1)

    አንድ ጋብቻ በተጋቢዎቹ ስምምነት ፈርሶአል ሊባል የሚችለው የፍቺ ስምምነቱ ተደርጎአል በተባለበት ቀን ሳይሆን የፍቺ ስምምነቱ ለፍርድ ቤት ቀርቦ ተቀባይነት ባገኘበት እና በጸደቀበት ጊዜ ስለመሆኑ፡-

    የተሸሻለው የፌድራል የቤተሰብ ህግ አዋጅ ቁጥር 213/92 አንቀፅ 76(1)

    109731

  •  

    ጋብቻ በአንደኛው ተጋቢ ሞት ምክንያት በፈረሰ ጊዜ የጋራም ሆነ የግል ንብረት በምን ያህል ጊዜ ውስጥ መጠየቅ እንዳለበት በፍ/ብ/ህ/ቁ. 1677 መሠረት በቁ. 1845 ላይ የተቀመጠው ይርጋ ተፈፃሚ ስለመሆኑ

    የፍ/ብ/ህ/ቁ. 1768 1ዐዐ16771845

     

    Cassation 17937

  • Family law

    proof of marriage

    possession of status

    evidence to prove possession of status

    ጋብቻ የትዳር ሁኔታ መኖሩን በማስረዳት ለማሳየት /ለማረጋገጥ/ የሚቻል ስለመሆኑና ይህንንም ለማስረዳት ማንኛውም ዓይነት ማስረጃ ሊቀርብ ስለመቻሉ

    የተሻሻለው የቤተሰብ ህግ አንቀፅ 9596 እና 97

    Cassation Decision no. 20036

  •  

    ስለ ጋብቻ መፍረስ

    Cassation 20938

  • Family law

    proof of marriage

    certificate of marriage

    possession of status

    የጋብቻ ጽሁፍ በሌለ ጊዜ ጋብቻ መኖሩን ለማስረዳት የሚቻለው የባልና ሚስትነት ሁኔታ መኖሩን በማስረዳት ስለመሆኑ

    የፍ/ብ/ህ/ቁ. 699(1) (2)

    Cassation Decision no. 21740